‹‹ዙቤይዳ››መጣች! ጌቱ ተመስገን እንደጻፈው
‹‹አገር ማለት ሰው ነው እያሉ በትውልድህ እንቅልፍ ላይ ብርድ ልብስ ይደርባሉ፡፡ አገር ማለት አፈር ነው፡፡ ሰውም ማለት አፈር ነው፡፡ ኢትዮጵያ ከተፈጠረች ጀምሮ የሞቱት ሰዎቻችን ስጋና አጥንት አፈር ሆኖ ይሄው›› አሉና መሬቱን በጎራዴው ጫፍ ጫር አደረጉት፡፡
‹‹አየህ አሁን አፈር አይደለም የጫርኩት፣ የሰው ስጋ ነው! ሲጫር የሚያመው፣ ሲወጋ የሚያቃስት ሰው ነው አፈሩ!! ይሄንን ነው ቆርሰው የሚወስዱት፡፡ አገር ማለት ሰው ከሆነ፣ ሰው አፈር ነውና አፈርህን ሲነኩ እንቢ ልትል ይገባል! ልጄ፣ ሕንፃ እና መንገድ አይግረምህ፣ የሰው እጅ የሚሠራው የእጅ ጥበብ ሁሉ አይድነቅህ፤ ነገም ልጆችህ ከአንተ በተሻለ ይሠሩታልና! ልጆችህ መቼም ለማያገኙት ስንዝር መሬት ግን ያለህን ሁሉ ክፈል…››
ይህ ኃይለቃል የተገኘው በአሌክስ አብርሃም በተጻፈው ‹‹ዙቤይዳ›› በተሰኘው አዲስ መጽሐፍ ውስጥ ነው፡፡ 22 ታሪኮችን የያዘው ዙቤይዳ፣ 251 ገጾች ያሉት ሲሆን የመሸጪያ ዋጋው 59 ብር ነው፡፡
አሌክስ አብርሃም ከዚህ በፊት ‹‹ዶ/ር አሸብር እና ሌሎችም›› የተሰኘ እንዲሁም ‹‹እናት ፍቅር ሐገር›› የተባለ የግጥም መድበል ለንባብ ማብቃቱ ይታወሳል፡፡
***
ባሳለፍነው ሳምንት የወራሃዊ ረዕቡ – የራስ ሆቴል ፕሮግራም አንጋፋው ተዋናይ ፍቃዱ ተ/ማሪያም ‹‹የአባዬ ስልክና ባዮሎጂ››ን ለታዳሚው ሲያቀርብ ሳቁን መቆጣጠር አልቻለም ነበር፡፡ አዳራሹ ሙሉ እድምተኛ በአሌክስ አብርሃም ሥራ እንዲሁም በጋሽ ፍቄ ትረካና ሳቅ ረስርሰናል፡፡ አቦ አዘጋጆቹን እናመሰግናለን!
ይህች የጋሽ ፍቄ ፎቶ በፎቶግራፈር ሙሉቀን አስራት #Muluken Asrat የተወሰደችው በዚያው ቅጽበት ይመስለኛል። ብራቮ – ሙሉቀን አስራት፡፡
በነገራችን ላይ ‹‹ዶ/ር አሸብር እና ሌሎችም›› እየተነበበ ነው፡፡ ሰባተኛ እትሟ ገበያ ላይ ውሏል፡፡ መጽሐፍት አዟሪ ላይ አየኋት፡፡
_____
የመጽሃፉን ደራሲ በፌስ ቡክ በየጊዜው በማህበራዊ እና ሌሎች ጉዳዮች ላይ ይጽፋል