ሐምሌ 7 ፤ 2008 ዓ ም
ከወልቃይት ጉዳይ ጋር በተያያዘ በጎንደር በተነሳ ህዝባዊ አመጽ ቢያንስ አምስት ያህል የጸጥታ ኃይሎች መገደላቸውን እና ባላታጠቁ ሲቪሎችም ላይ ጎዳት መድረሱ በማህበራዊ ድረ ገጽ ከሚወጡ ዘገባዎች ለማወቅ ተችሏል።
ህዝባዊ አመጹ የተጀመረው ከትግራይ ክልል መጡ የተባሉ የጸጥታ ኃይሎች የወልቃይትን ጉዳይ ለማስፈጸም ከተመረጡት ኮሚቴዎች አራት ያህሉን በተጭበረበረ የፍርድ ቤት ማዘዣ አፍነው ከወሰዱ በኋላ ነው። ኮሎኔል ደመቀ የተባለውን አምስተኛውን የኮሚቴ አባል ለመውሰድ ሲሞክሩ ኮሎኔል ደመቀ እጄን አልሰጥም በማለቱ የተኩስ ልውውጥ እንደተደረገም ታውቋል።
የኮሎኔል ደመቀ ወንድ ልጂ በህወሃት ታጣቂዎች እንደተገደለም የማህበራዊ ድረገጽ መረጃዎች ይጠቁማሉ።
ህዝባዊ አመጹ የተቀጣጠለው ኮሌኔል ደመቀን አሳልፎ ላለመስጠት ከተደረገ ትግል ጋር ተያይዞ እንደሆነ ታውቋል። እንደ ኢሳት ዘገባም ኮሎኔሉ ሳይያዝ በህዝባዊ አመጹ ድፋፍም ጭምር ከህወሃት ታጣቂዎች ከበባ ለማምለጥ ችሏል። መንግስት ካሰማራቸው የጸጥታ ኃይሎች ጋር ለመፋለም ከሁመራ እና ሌሎች የጎንደር አካባቢዎች ህዝብ ወደ ጎንደር እንደተመመ ተጠቁሟል።
በህዝባዊ አመጹም ከህዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ ጋር ንክኪ ያላቸው ባለንብረቶች ንብረት ወድሟል እንደዘገባው።
የችግሩ ምንጭ ቀደም ሲል የጎንደር አካል ሆኖ የኖረውን ወልቃይትን በህገወጥ መንገድ ወደ ትግራይ ክልል በመከለሉ ምክንያት የተነሳ ነው። የወልቃይት ትግል በታሪኬ የጎንደር አካል ሆኘ ኖሬያለሁ ፤ አሁንም ጎንደሬ እንጂ ትግሬ አይደለሁም የሚል ነው። ህጋዊ እና ታሪካዊ መሰረት ያለውን ተገቢ ጥያቂ ፤ የህወሃት ባለስልጣናት በእብሪት ጉዳዮን አላስፈላጊ ወደሆነ የፖለቲካ ውጥንቅጥ ወስደውታል።
______