ነሃሴ 16 2008 ዓ ም

ምንጭ : ማህበራዊ ድረ ገጽ
እሁድ ነሃሴ 15 2008 ዓ ም በአዲስ አበባ ግዙፍ የተቃውሞ ሰልፍ ለማድረግ በማህበራዊ ድረ ገጾች ዘመቻ ተደርጎ ሰልፉን ለማካሄድ ዝግጂት ተደርጎም ነበር። ከሰልፉ ጋር በተያያዘ መረጃ ያላቸው እንደ አሜሪካ ያሉ የውጭ መንግስታት በአዲስ አበባ ከታቀደው ሰላማዊ ሰልፍ ጋር በተያያዘ ለዜጎቻቸው የጉዞ ማስጠንቀቂያ እስከማውጣት ደርሰው ነበር።
በተጨማሪም ዲፕሎማቶች የሰልፉን ሂደት ለመከታተል ዕቅድ እንደነበራቸውም በማህበራዊ ደረ ገጾች በጭምጭምታ መልክ መረጃ ሲዘዋወር ነበር።
የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቭዥን እንደዘገበው የመንግስት ባለስልጣናት አየር ኃይሉ በተጠንቀቅ እንዲሆን ትዕዛዝ እስከመተላለፉም ደርሶ ነበር።
ሰልፉ ለምን ተስተጓጎለ?
ከአዲስ አበባ ምንጮች እንደሚሉት ቅዳሜ ለእሁድ ሌሊት በአዲስ አበባ ግዙፍ የአጋዚ ሰራዊት እና የፌደራል ፖሊስ እንዲሰማራ ተደርጎ ሰልፉ ሳይጀመር በፊት በየሰፈሩ የቤት ለቤት አሰሳ በማድረጉ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ወጣቶች ታፍሰዋል። መንገዶች በየቦታው በፌደራል እና በአጋዚ ሰራዊት ተዘግተዋል።
እሁድ እንደመሆኑ ወደ ቤተ ክርስቲያን የሚሄዱ ሰዎች ሳይቀሩ በየመንገዱ እንዲቆሙ ተደርጎ ፍተሻ ተደርጎባቸዋል። ተዋክበዋል። እንደዛም ሆኖ ሌሊቱን መረጃ ከአዲስ አበባ ሲያካፍሉ የነበሩ እንደገለጹት ወደ አብዮት አደባባይ ለመሄድ እንቅስቃሴ ያደረጉ የነበሩ ሲሆን በፌደራል ፖሊስ ጥቃት ደርሶባቸዋል።
የሰልፉ መስተጓጎል ያለው አንድምታ
መንግስት ወደ ፖለቲካ ነቀርሳነት እየተቀየረ ያለ የተቀባይነት (legitimacy) ችግር እያለበት ፤ መሰረታዊ እና በጥገናዊ ለውጦች ሊፈቱ የማይችሉ የፖለቲካ ጥያቄዎች ባሉበት እና በመላው ኢትዮጵያ ህዝባዊ አመጽ እየተስፋፋ ባለበት ሁኔታ በግዙፍ ሰራዊት እንቅስቃሴውን ለማፈን መሞከር የለውጥ እንቅስቃሴው አቅጣጫ እንዲቀየር ራሱን ወደ መከላከል ደረጃ ከፍ እንዲል በማድረግ እልቂትን ሊጋብዝ ይችላል የሚሉ ወገኖች ጥቂት አይባሉም።