spot_img
Wednesday, October 4, 2023
Homeነፃ አስተያየትያቺ “ባነር”..... ! ከመስከረም አበራ

ያቺ “ባነር”….. ! ከመስከረም አበራ

advertisement

የጎንደሩ ጥሎሽ …

ህወሃት ሁለቱን ህዝቦች እርቅ ሊጎበኘው በማይችል የጠላትነት አዘቅት ውስጥ ለመክተት የተጠቀመው መንገድ መገናኛ ብዙሃን፣የራሳቸውን ሃላፊነት አልቦ አንደበት እና ከሁለቱም ብሄር የወጡ ግዙ ባለስልጣን እና ካድሬዎችን ብቻ አይደለም፡፡ የነመለስ ዜናዊ የጥፋት መንገድ እጅግ ረቂቅ ነውና የተስፋየ ገብረአብን ውብ ብዕርም ለዚሁ እንቅልፋቸውን ለሚነሳቸው የሁለቱ ህዝቦች አብሮነት ማፍረሻ በደንብ አድርገው ተጠቅመውበታል፡፡ ተስፋየም ሃፍረት እና ይሉኝታ ባለፈበት ያለፈ ሰው ስላልሆነ ‘ነቅተንብሃል’ እየተባለም በልጅነቱ እንደማተብ የታሰረለትን የጥላቻ ክታብ ሊያወልቅ አልቻለም፤ ከቀድሞ አልባሽ አጉራሾቹ ጋር ከተጣላ በኋላም የጥላቻ ብዕሩ መርዝ መትፋቱን አላቆመም፡፡ ህወሃት ይህን ሁሉ ከንቱ ድካም ሲደክም የኖረው በአሽዋ ላይ የቆመ ቤት ለመስራት ነበርና የአንድ ቀን የህዝብ ድምፅ የሃያ አምስት አመት ድካሙን ገደል ከተተው፡፡ ከወደ ጎንደር በፍቅር ብዕር፣ በመተሳሰብ ሸማ ላይ የተከተበች አንድ ባነር ታሪክ ለወጠች፡፡ “በጎዳና ላይ የሚፈሰው የኦሮሞ ወንድምና እህቶቻችን ደም የእኛም ደም ነው” የምትል የአቶ በቀለ ገርባን ምስል የያዘችው ባነር ስንቱ ፊደል ጠገብ አጥብቆ የፈተለውን የጥላቻ ገመድ በጣጠሰች፤በምትኩ ሁለቱን ታላላቅ ህዝቦች በፍቅር እንባ አራጨች፤ ያች ባነር!!! መብቱን ከማስከበር ጎን ለጎን የጠፋ ወንድማማች/እህትማማችነትን ፍለጋ የወጣው የጎንደር ህዝብ በፍቅር ፊት መቆም የማይችለውን የህወሃት በአሸዋ ላይ የተገነባ የጥላቻ ቤት በፍቅር አውሎ ንፋስ ከስሩ ነቀነቀው፡፡የጥላቻ መንገድ አይቀናም፡፡ የሴራ ወንበር አይፀናምና ይህ የሚጠበቅ ነው፡፡የጥላቻ ሰባኪዎች ግን ይህን ይረዱ ዘንድ ብቁ አይደሉም፡፡ በወርቅ የማይገዛውን የወንድማማችነት ፍቅር “ያልተቀደሰ ጋብቻ” ሲሉ ያልተቀደሰ ጭንቅላታቸው ያቀበላቸውን ዘባረቁ፤ ፍርሃት ያራደው ከንፈራቸው ላይ የሞላውን ስድብ ሁሉ በሰፊው ህዝብ ላይ አወረዱ፡፡

yachin-banner

ኢህአዴጎች ጥሩ የተናገሩ እየመሰላቸው ከአንደበታቸው የሚወረውሯቸው ቃላት እና ሃረጋት በመንግስት መንበር ላይ መሰየማቸውን አይመጥኑም፡፡ ሌሎቹ ቀርተው የአንደበታቸው ርቱዕነት ወፍ ያረግፋል ይባሉ የነበሩት የአቶ መለስ አንደበት እንኳን በግሌ ጨዋነት የጎደለው፣ማናለብኝነት ያሸነፈው፣ አንዳንዴም ግልብ እንደነበረ ይሰማኝ ነበር፡፡በተከበረው ፓርላማ ፊት ‘ጣትህን እቆርጣለሁ፣ ምላስ እዘለዝላለሁ’ ይሉ ነበር፡፡ የሁለት አካላትን ሰላማዊ ግንኙነትም ከዕቁባታዊ ግንኙነት ጋር እየመሰሉ ማስረዳቱ ይቀናቸው ነበር፡፡ በ1997ዓም አላሰናዝር ብለው የነበሩትን አናጎሜዝን በተመለከተ ለአዲስ ዘመን እና ዘኢትዮጵያን ሄራልድ ጋዜጦች ኤዲተር በፃፉት ማስታዎሻ “what love has to do with this” የሚለውን የታዋቂዋን ዘፋኝ የቲና ተርነርን ሙዚቃ ግጥም መንግስትነትን በማይመጥን አላስፈላጊ ሁኔታ አስገብተው ነበር፡፡

አሁን የመንግስት አንደበት ተደርገው የተሰየሙት አቶ ጌታቸው ረዳ መሆናቸው ደግሞ በኢህአዴግ መንደር ለአንደበት ጨዋነት ብዙ ቦታ እንደሌለ አሳባቂ ነው፡፡ ብሶት በጠበንጃ ፊት እንደቆመ እንኳን አስረስቶ የሚያጮኽውን የኦሮሞ ህዝብ ከጅኒ ጋር እያነፃፀሩ ሲያስረዱ ለአቶ ጌታቸው በአማርኛ መራቀቅ፤ በሃሳብ መምጠቃቸው ሊሆን ይችላል፡፡ለሰሚ ግን ትርጉሙ ሌላ ነው፡፡ አንድ ሰው በቤቱ የቀረ በማይመስል ሁኔታ ነቅሎ የወጣውን የአማራ ህዝብ ትቂት የሽፍታ ጠበቆች ሲሉ ዘለፉ፡፡ ሁለቱ ህዝቦች ከተገደሉ ልጆቻቸው እኩል የተሰደቡት ስድብ አስቆጥቷቸዋል፡፡ በዚህ የማያበቁት አቶ ጌታቸው ‘ሁለት ባላንጣዎች ያተቀደሰ ጋብቻ መስርተዋል’ ሲሉ አከሉ፡፡ እውነት ለመናገር ነገሩ በጋብቻ ሁኔታ ባይገለጽ ደግ ነበር:: ሆኖም ሰው በልቡ የሞላውን በአንደበቱ ይናገራልና አቶ ጌታቸው በልባቸው የሞላውን ገለፁ፡፡ነገሩ የሚገባቸው በጋብቻ ሁኔታ መገለፅ ካለበት የኦሮሞ እና የአማራ ታላላቅ ህዝቦች ቅዱስ ጋብቻ ጎንደር ላይ በቀረበችው የፍቅር ጥሎሽ (ያቺ ባነር)ተጀምሮ ኦሮሚያ ላይ “አማራ የኛ” በሚል ሙዚቃ ታጅቦ ተፈፅሟል፡፡ይህ ቢመርም ሊቀበሉት የሚያስፈልግ ሃቅ ነው! በምድር ላይ የሚያስተዳድረው ህዝብ መተሳሰብ የሚያናድደው፣ክፉ የሚያናግረው መንግስት ኢህአዴግ ብቻ ሳይሆን አይቀርም፡፡ “የአማራ እና የኦሮሞ ህዝብ ይህን አይነት መፈክር ይዘው መውጣታቸው የእኛን ስራ ለ,ያለመስራት ያመላክታል” አሉ አቶ ጌታቸው ረዳ ለፋና ሬዲዮ፡፡ ፋይሉ በድህረገፆች ስላለ ዝርዝሩን አንባቢዎቼ ቢያዳምጡ ሙሉ ስዕሉን ለማግኘት ይችላሉ፡፡ይህ ከአእምሮ በላይ ነው!

ቅዱሱ ጋብቻ!

የኢህአዴግን እግር ተከትሎ በሃገራችን የተንሰራፋው እትብት እየተማዘዙ የጎሪጥ የመተያየት አባዜ አሁንም የሃገራችን ፖለቲካ ዋና ነቀርሳ ነው፡፡ ችግሩ የሚመነጨውም ሆነ የሚበረታው ተማርኩ በሚለው የህብረተሰብ ክፍል ነው፡፡ መማሩ ስነልቦናውን ከታሪክ ጋር እያዋቃ ጥላቻን ብቻ እንዲሰብክ ያደረገው የትየለሌ ነው፡፡እንደ ደህና ነገር ስንት ገፅ መፅሃፍ አሳትሞ በየገፁ ጥላቻን ሳይረሳ የሚሰብክ ምሁር በበዛበት ሃገር፤ኢህአዴግም ይህን በደንብ ሲያሳልጥ ሃያ አምስት አመት ከንቱ ሲደክም ቢኖርም ሰሚው ሰፊ ህዝብ ጥላቻን የሚሰማበት የጆሮ መስኮቱን ዘግቶ ኖሯል፡፡ የጎንደር ህዝብ የጀመረውን የፍቅር ምልክት የኦሮሚያ ህዝብ ወዲያው ማስተጋባቱ ድሮም ኢህአዴግ በሚያራግበውን እና ፅንፈኛ የጎሳ ልሂቃን በሚያንፀባርቁት ደረጃ ህዝቦች በጠላትነት እንደማይፈላለጉ ነው፡፡ የኦሮሞ ህዝብ ሳይውልሳያድር እናንተም የእኛ ናችሁ ሲል መልስ የሰጠው በፍቅር መበለጥን ስላልፈለገ ነው፡፡በፍቅር ላለመበላለጥ መሽቀዳደም ደግሞ የመልካም ልቦና ዝንባሌ ነው፡፡ይህ ብው በሚያደርግ ንዴት ውስጥ የሚከተው ደግሞ ራሱን መመርመር ግድ ይለዋል!

ንደር እና አዳማ አፋፍ ላይ ሆነው “ደምህ ደሜ፣አጥንትህ አጥንቴ” ሲባባሉ ሌሎች ከተሞችም ይህን ሲከተሉ የኮምፒውተር “በተን” በነኩ ቁጥር ህዝብን የመሩ የሚመስላቸው የጥላቻ ሰባኪዎች የወንጀለኝነት ስሜት እንደሚሰማቸው ጥርጥር የለኝም፡፡ ወትሮም ገታራነት የማይጫናቸው የኦሮሞ ምሁራን ይህ የህዝብ መተሳሰብ የኖሩበትን የፖለቲካ አቅጣጫ እንዳስቀየራቸው በአንደበታቸው ሲናገሩ ሰምቻለሁ፡፡ሁሉም የሚሉት ‘ህዝብ መራን፤ህዝብ በለጠን፤ ህዝብ ቀደመን’ ነው ! የትምህርት ደረጃን ቆጥሮ ብዙሃኑን ህዝብ ሳይንቁ፣ እኔ አውቅልሃለሁ ሳይሉ፣ይልቅ መበለጥን አውቆ አካሄድን ማስተካልም የምሁራኑን ትህትና ያመለክታልና በተለይ የኦሮሞ ምሁራን ለዚህ ትህትናቸው ምስጋና ይገባቸዋል፡፡

ያመኑት ፈረስ …..

ከህወሃት የወቅቱ ዘዋሪዎች አንዱ አይተ ኣባይ ፀሃይየ የፓርቲያቸውን አርባኛ አመት ድል ባለ ድግስ ሲያከብሩ ‘እነ ኢህአፓ ሲንኮታኮቱ እኛ ድል የተቀዳጀነው ህዝብን ለማታገል ቀለል ያለውን የጎሳ ፖለቲካ የሙጥኝ ስላልን ነው’ አይነት ንግግር ሲናገሩ ተገርሜ ነበር ያዳመጥኳቸው፡፡ህዝብን የማታገያ ዘይቤ የሚመረጠው ስለቀለለ ነው ወይስ የህዝብ እውነተኛ ጥያቄ ስለሆነ? ቀላል የተባለው የጎሳ ፖለቲካ ከምክንያት ይልቅ ስሜትን ስለሚፈልግ ብልጣብልጦቹ የህወሃት መኳንንት በጎሳህ ምክንያት የፈረደበት አማራ ቆረጠህ ፈለጠህ እያሉ የብረት ተሸካሚ፣ ወላፈን እሳት ላይ ተማጋጅ ነፍስ ለማግኘት ስለማያስቸግር ነው፡፡ስልጣን ላይ ከተሳፈረ በኋላም ህወሃት መራሹ ኢህአዴግ ከላይ ለመጥቀስ በተሞከረው መልክ በሃገሪቱ የሚገኙ ወንድማማች ህዝቦችን ከአንድነታቸው ይልቅ ልነት ላይ እንዲያተኩሩ ማድረጉን በቀላሉ ስልጣን ላይ ተወዝቶ የመኖሪያ ሁነኛ ዘዴ አድርጎት እንደነበር ነገራ ነገሩ ያስታውቃል፡፡ በዚሁ በጎሳ እና በጥላቻ ፖለቲካ ተፀንሶ፣አድጎ ዙፋን ላይ የተሰየመው ህወሃት/ኢህአዴግ የሚወደውን ዙፋኑን እየነቀነቀው ያለው ከጎሳ ፖለቲካ ጋር በተዛመደ የመረረ ጥያቄ መሆኑ ትልቅ የፖለቲካ አያዎ ነው!

_________
መስከረም አበራን በሚከተለው የኢሜይል አድራሻ ማግኘት ይቻላል : meskiduye99@gmail.com

ሼር ያድርጉ ፤ ቦርከናን በፌስ ቡክ ላይክ ያድርጉ

- Advertisement -Early Bird Holiday Deals! Before you know it, the holidays will be right around the corner! Take advantage of our early bird deals today and save up to $40 on our fees with code SPOT40!
Stay Connected
28,789FansLike
13,732FollowersFollow
8,540SubscribersSubscribe
Stacy Adams
Must Read
Related News

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here