spot_img
Sunday, May 28, 2023
Homeነፃ አስተያየትየአማራ ብሄርተኝነት ነገር... (መስከረም አበራ)

የአማራ ብሄርተኝነት ነገር… (መስከረም አበራ)

- Advertisement -

(በመስከረም አበራ; e-mail meskiduye99@gmail.com)
ጥቅምት 2 2009 ዓ ም

ከፅንሰት ውልደቱ ጀምሮ አማራ የሚለውን ቃል በበጎ ማንሳት የማይወደው ህወሃት ከጫካ ወደ ዙፋን በሚያደርገው ጉዞ ሁሉ በኢትዮጵያ ታሪክ የታየውን የታሪክ ዥጉርጉር በተለይ ክፉ ክፉውን ለአማራ ያስረክብ ነበር፡፡ ስልጣን ላይ ተመቻችቶ ከተቀመጠ በኋላም ያልቀየረው ሙዚቃ ይሄው አማራን ማክፋፋት፣ ማጥላላት፣ከሰው መነጠል፣ ማሳደድ፣ ማሸማቀቅ፣መግደሉን ነው፡፡ ‘ከአማራ ክፉ አገዛዝ ነፃ አወጣኋችሁ’ ሲል በየብሄራቸው አደራጅቶ ከባለጠግነቱ ትቂትም ቢሆን የከፈለላቸው የኢህአዴግ አባል እና አጋር ድርጅቶችም ይህንኑ ሲያስተጋቡ ኖረዋል፡፡የማፈናቀል መግደሉ ፊታውራሪ የሆኑም በርካታ ናቸው፡፡

‘የብሄር ብሄረሰቦች መሲህ ነኝ ስለነሱ እኩልነት እና ነፃነት ስል አስራ ሰባት አመት በበረሃ አይሆኑ ሆኛለሁ’ ሲል የማይደክመው ህወሃት ስልጣን ከጨበጠ በኋላ ለተቀሩት ብሄር ብሄረሰቦች አለኝ የሚለውን ተቆርቋሪነት የሚያስመሰክረው አማራውን በአደባባይ በማጥላላት፣በማዋረድና የሌለ ክፉ ስም በመጋገር ነው፡፡በህወሃት የእልቅና ዘመን የአማራን ህዝብ በሚዲያ ሳይቀር ማክፋፋት ሁለት ጊዜ የማይታሰብበት ‘መብት’ ብቻ ሳይሆን ለአብዮታዊ ዲሞክራሲ ያለን ታማኝነት ማሳያ ተደርጎም ይቆጠራል፡፡ይህ ከመንደር ካድሬ እስከ ቁንጮው መለስ ዜናዊ ድረስ የሚደረግ የቤቱ ልማድ ነው፡፡ለዚህ ነው ከአማራ ህዝብ ወጥቻለሁ ብሎ ክልሉን ሊመራ የተቀመጠው አለምነው መኮንን በአንድ ወቅት ያለውን ያለው፤ካለ በኋላም ህዝብ አይንህ ላፈር እያለው አበጀህ ተብሎ በመንበሩ የፀናው፡፡ አማራ ነኝ ባዮቹ ተፈራ ዋልዋ እና በረከት ስምኦን አማራነታቸውን ቀርቶ አዛውንትነታቸውን የማይመጥን ሃላፊነት የጎደው ብዙ ብዙ ንግግር ተናግረዋል፡፡ለስብሃት ነጋ ደግሞ አማራን መወረፍ የእግዚአብሄር ሰላምታ ያህል አስደሳች እና ዘወትራዊ ነው፤አማራ ተመልሶ ስልጣን ላይ መታየት እንደሌለበት በአደባባይ ሲናገር ከአረጋዊነቱ ጋር በማይሄድ ሁኔታ ነገን ሳያስብ ነበር፡፡

ይህ የህወሃት/ኢህአዴግ ክፉ አስተሳሰብ ወደ ተቃውሞው ጎራም ተሻግሮ ለኢትዮጵያ ብሄርተኝነት የተሰባሰቡ ታጋዮች የመሰረቱትን ህብረ-ብሄራዊ ፓርቲ ‘የደርግን ስርዓት መልሶ ለማምጣት የተሰባሰቡ አማሮች የመሰረቱት የአማራ ፓርቲ’ በማለት በህዝብ ዘንድ ተቀባነት እንዳይኖረው፣ በፍርሃት እንዲታይ ‘የጅቡ መጣላችሁ’ ፖለቲካውን የማጧጧፍ ልማዱ የአደባባይ ወግ ነው፡፡ ይህ ፈሊጥ ህብረብሄራዊ ነን ሲሉ በህብረ-ብሄራዊ ተቃዋሚ ፓርቲ ውስጥ አባል እና አመራር በሆኑ ሰዎችም እንደሚቀነቀን አውቃለሁ፡፡ በአንድ ወቅት መድረክ በሚባለው ስብስብ ውስጥ በነበረው የአንድነት ፓርቲ እና በሌሎች ብሄር ተኮር ፓርዎች መሃከል የጦፈ ንትርክ ነበር፡፡ የንትርኩ መነሾ ደግሞ በመድረክ ስብስብ ውስጥ ‘አማሮች ሊገኑ እየሞከሩ ነው’ የሚል አስገራሚ ስጋት ነበር፡፡ ነገሩ በየሚዲያው ‘የነፍጠኛ ልጆች ተጠንቀቁ!’ የሚል አርቲክል እስከመፃፃፍ እና መወራረፍ የደረሰ የእርስ በርስ መጎሻመጥ ድረስ ደርሶ እንደነበር ፀሃይ የሞቀው እውነት ነው፡፡ሲብስም በቅንጅት ውስጥ ሳይቀር በብዙ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ዘንድ ‘ተቀባይነት እንድናገኝ አማሮችን ሊቀመንበር እና አመራር ባናደርግ’ የሚባል ድርድር ሁሉ እንዳለ ይነገራል፡፡ ይህ ሁሉ ከግራ ከቀኝ የሚወረወር ሃፊነት አልቦ ድርጊት እና ንግግር ተጠራቅሞ አማራውን ከኢትዮጵያዊ ብሄርተኝነት ወደ አማራ ብሄርተኝነት የግድ ነፍስ የማትረፍ፣ክብርን የማስመለስ ጉዞ ነድቶታል፡፡

‘ክፉ ጠሪ ወይ ባዩን ያከፋል’

የጎሳ ብሄርተኝነት ምንጩ ዘውግን ማዕከል ያደረገ በደል ነው፡፡በደል ደግሞ በአንደበት ከማቁሰል በጥይት እስከ መግደል ይደርሳል፡፡ በእኛ ሃገር እና በአማራ ዘውግ ሁኔታ ደግሞ በመሃሉ መገለል እና መፈናቀልም አለ፡፡ከመጀመሪያው ያለ ምንም ቅጥያ በደፈናው አማራን ቀጥሎ ደግሞ የአማራ ገዥ መደብ ጠላቴ ነው እያለ በምድረበዳ ሲሰብክ የኖረው ህወሃት ስልጣን ሲይዝም ይህንኑ ባላንጣነቱን የሚያሳይበት ፈርጅ ብዙ ነው፡፡ በደሉን ሲጀምረው አዋቀርኩ ባለው የሽግግር መንግስት ላይ የአማራን ህዝብ ውክልና አሳጣ፡፡ ከዛ በኋላ ሁሉ ለመጣው በደል መሰረት የጣለበት ስልት ይህ ጅማሬ ይመስለኛል፡፡ምክንያቱም የሽግግሩ ዘመን የሃገሪቱን የፌደራል አወቃቀር ጨምሮ የወደፊት ዋነኛ ፖሊካዊ አቅጣጫ የሚተልሙ ውሳኔዎች የተሰጡበት ነበር፡፡በዚህ ወሳኝ ሰዓት ከሃገሪቱ ህዝብ ብዛት ሁለተኛ ተርታ ላይ የተቀመጠን ህዝብ ማግለል በአጋጣሚ ነው ማለት አይቻልም፤ነገ የተሰነቀውን ሆድ ስለሚያውቅ እንጅ!

ሁለተኛው ለአማራ ህዝብ የተሰነዘረ ክፉ ጥሪ ከህወሃት መንጭቶ አማራን ህዝብ ቆምኩልህ ከሚለው ኢህዴን/ብአዴን አንደበት አእንዲሰማው የተደረገው እና እስከዛሬም እየተነገረ ያለው ሃላፊነት የጎደለው ንግግር ነው፡፡ ነገሩን ሁሉ እንዳይሆን ይዞት እንደነበረ የሚነገረው ታምራት ላይኔ ‘ብአዴን የቆመው በአማራ ክልል ለሚኖረው አማራ ብቻ ነው’ ሲል በአደባባይ የሞት አዋጅ እንዳሳወጀ በዘመኑ ፖለቲካን ለመከታተል የደረሱ ሁሉ የሚመሰክሩት ነው፡፡ለራሱ የተቆፈረትን ጉድጓድ ያላወቀው ታምራት ላይኔ ብዙ ንፁሃን አማሮችን ከነነፍሳቸው ወደገደል የማስወርወሩን የአሽከርነት ስራ በደንብ ሰርቷል፡፡ ታምራትን ሳይውል ሳያድር የራሱ ስራ ጠልፎ ጥሎት አሁን ከሁለት ያጣ ሆኖ ማንንም ወደማይጠየፈው አምላክ አምባ የተጠጋ ቢሆንም በምድራዊ የፍርድ አደባባይ እስካልታየ ድረስ ክፉ ስራው ስብዕና ከሚሰመው ኢትዮጵያዊ ልቦና ውስጥ ሁሉ አይጠፋም፡፡

ክልሉ ውጭ ባለ አማራ ጉዳይ አያገባንም የተባለው የአማራ ህዝብ በመላ ሃገሪቱ በብዛት ተበትኖ እንደሚኖር ስለሚታወቅ በሰፊው የልብን ለመስራት ታስቦ ነው፡፡ በተጨማሪ የአማራ ህዝብ ታታሪነት ስለሚታዎቅ በሄደበት ለፍቶ ደክሞ ሃብት ማፍራቱም ግልፅ ነው፡፡ ያፈራውን ሃብት ዘርፎ ማፈናቀሉ ደግሞ ኢኮኖሚያዊ አቅሙን ሽባ ስለሚየደርገው ህወሃት የማይወደውን በራስ መተማመኑን ለመንጠቅ ያስችላል፤ይሄኔ አስራ ሰባት አመት ተዋደቅንለት የሚባለው የአማራ “ትምክህት” ድል ተደረገ ማለት ነው፡፡ይህ ምኞት ሙሉ በሙሉ አልተሳካም ማለት አይቻልም፡፡ በሃገሪቱ ዳርቻ ውክቢያ የበዛበት የአማራ ህዝብ፣ የለፋበተን የእሳት እራት አድርጎ ያረጀበትን ቀየ በሃያ አራት ሰዓት ለቆ እንዲወጣ የተደረገ ህዝብ በራስ መተማመኑ አብሮት ሊኖር አይችልም፡፡

ህወሃት/ኢህአዴግ ክልልህ ነው ብሎ ከተመነለት ምድር ውጭ የሚኖረው አማራ በስነልቦና፣ በኢኮኖሚ እና ፖለቲካዊ ተደራራቢ ቅጣት ሲቀጣ በክልሉ ያለው አማራ ደግሞ ቆምኩልህ የሚለው ፓርቲ መሪዎች ጮክ ብለው እንዲሰድቡት ሲደረግ ራሱን ጠበቃ የሌለው “ወንጀለኛ” አድርጎ ይቆጥራልና ራሱን ቀና የማድረግ ልማዱን ይተዋል፡፡ በዚህ ሁኔታ ህወሃት ትምክህት የሚለወን ግን ደግሞ አጥብቆ የሚፈራውና የሚጠላውን የአማራን ህዝብ በራስ መተማመን ለማትነን ተሞክሯል፡፡ ይህም የታሰበውን ያህል ባይሆንም በመጠኑ ተሳክቷል፡፡ ወንድሙ ከሃገር ዳርቻ እግሩን ነቅሎ ሲሰደድ ፣ማግኘቱ አፍታም ሳይቆይ ማጣት ሆኖ ለማኝ ሲሆን ያየ በክልሉ የሚኖር አማራ ወኪልህ ነኝ በሚለው ሰው ሲሰደብ የሚቆምለት መንግስታዊ አካል እንደሌለ ተገንዝቦ በገዛ ሃገሩ የመፃተኛ መንፈስ እንዲዋረሰው ሆኗል፡፡ ይህ ታስቦበት የተሰራ የስነልቦና፣ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ጥቃት ባህላዊ ገፅታም አለው፡፡

የአንድ ማህበረሰብ ስነ-ቃሎች የማህበረሰቡን የእይታ ምጥቀት፣ የአስተሳሰብ ደረጃ ጥልቀት የሚያስገነዝቡ ምስክሮች ከመሆናቸውም በላይ እንደ ህዝብ የሚደምቅባቸው ጌጦቹ፣ ራሱን የሚገልፅባቸው መተንፈሻዎቹም ናቸው፡፡ እንደ ሃገርም ተጠብቀው ጥናት እና ምርምር እየተደረገባቸው፣ እየተተነተኑ ለመጭው ትውልድ መተላለፍ ያለባቸው የሃገር ሃብቶች ናቸው፡፡ በእኛ ሃገር ሁኔታ ሁሉም ማህበረሰብ ስሜቱን የሚገልፅበት የራሱ የሆኑ ስነ-ቃሎች አሉት፡፡ከዚህ ሳይንሳዊ ሃቅ በተቃራኒው ተረት ያለው የአማራ ህዝብ ብቻ ተደርጎ ሲቀርብ ይህም የኋላቀርነት፣የነገር ወዳድነት እና የስራፈትነት መገለጫ ተደርጎ የሚያኮራው ነገር መሰደቢያ ሆኖ ኖሯል፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትርነትን መንበር የተፈናጠጠው ሟቹ መለስ ‘የአማራ ተረት ነው ወደ ኋላ ያስቀረን’ ሲል ለሱ አንድም ንግግር ማወቅ ነው ሁለትም የሚጠላውን የአማራ ህዝብ ቅስም መስበር ነው፡፡ የአማርኛ ቋንቋ የአማራ ህዝብ ብቻ ንብረት ይመስል ቋንቋው እንደ ክፍለ-ትምህርት ተደራጅቶ ከአማራ ክልል በቀር በአብዛኞቹ የሃገራችን ዩኒቨርሲቲዎች በአብይ(major)ም ሆነ በንኡስ(minor) የጥናት መስክ ሆኖ እንዳይሰጥ መደረጉ በዘፈቀደ የተደረገ ሳይሆን ከላይ የተጠቀሰውን አማራን አኮስሶ “ትምክህቱን” ለማራገፍ ሲባል ወገብ ጠበቅ ተደርጎ የተሰራበት ጉዳይ ነው፡፡

‘አይን አፋሩ’ የአማራ ብሄርተኝነት

ያመነበትን ነገር አጥብቆ መያዝ የሚያውቀው ህወሃት/ኢህአዴግ ከመነሻው በበጎ ጠርቶት የማያውቀውን የአማራ ህዝብ በብዙ ለበቅ እየገረፈም ቢሆን የአማራ ህዝብም ሆነ ልሂቃኑ ለኢትዮጵያዊነት ያላቸው የቀደመ ፍቅር እንደነበረ ቀጥሏል፡፡ሆኖም ከበደል የአማራ ብሄርተኝነተን ለመትከል ሳይሆን ከደረሰው በደል አንፃር ተሰብስቦ መላ ለማለት ፕሮፌሰር አስራት እና ጓዶቻቸው ህይወታቸውን ያስከፈለ ትግል አድርገው የመጀመሪያውን የአማራ ዘውግ ወገናዊነት ማዕከል ያደረገ ፓርቲ መስርተው ነፍስ የማዳን ትግል ጀመሩ፡፡ ይህን ትግል ሲጀምሩ ፕሮፌሰሩም ሆኑ የትግል አጋሮቻቸው የአማራ ብሄርተኝነትን ለማቀንቀን አይናፋርነት እንደነበራቸው በቅርቡ “አንፀባራቂው ኮከብ” በሚል ርዕስ በፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ ህይወት ዙሪያ የተፃፈው መፅሃፍ ካሰፈራቸው መረጃዎች መረዳት ይቻላል፡፡የትግላቸው መዳረሻም የአማራ ሳይሆን ኢትዮጵያዊ ብሄርተኝነት እንደሆነ ያስገነዝቡ እንደ ነበርም ያስረዳል መፅሃፉ፡፡

ነፍሳቸውን አስይዘው በአማራ ህዝብ ክፉ ቀናት ለትግል የታጠቁት ፕ/ሮ አስራትም ሆኑ የትግል አጋሮቻቸው በሰዓቱ ተገቢውን ስራ የሰሩ ቢሆንም የሚታይ ተግዳሮት ከብዙ አቅጣጫ ገጥሟቸው ነበር፡፡ህይወትን ጭምር የጠየቀው ተግዳሮት የመጣው ከህወሃት/ኢህአዴግ ቢሆንም ከአማራ ልሂቃንም ቀላል የማይባል እንቅፋት ገጥሟቸው ነበር፡፡ የአማራ ልሂቃን ክርክር በአማራነት መደራጀት አማራው ኢትዮጵያዊነትን ቸል ብሎ ኢህአዴግ ወደ ሰፋለት የዘር ከረጢት ሰተት አድሮጎ የሚያስገባ፣ ኢህአዴግን ድል የሚያስመታ አካሄድ ነው ባይ ነው፡፡ እንደክርክሩ ህወሃት/ኢህአዴግ በአማራ ህዝብ ላይ ያደረገውን ያደረገው የኢትዮጵያዊ ብሄርትነት ትምክህቱን ለማስጣልና ነው ይህ ደግሞ ለአማራው ሽንፈት ብቻ ሳይሆን መኮሰስም ነው፡፡ እነዚህ ተከራካሪዎች የማይመልሱት፣ አዲሱ የአማራ ብሄርተኝነት ፓርቲ (መአድ) የሚያቀርበው ተገቢ ጥያቄ ለሚሞት፣ ለሚሰደድ፣ለሚፈናቀው፣ በሃገሪቱ ዳርቻ ለሚዋከበው አማራ ማን ይቁምለት? እጣፋንታውስ ምን ይሁን ? የሚለው ነው፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ የሁላችንም የሆነችውን ኢትዮጵያ ብሄርተኝነት ማስጠበቅ ለአማራው ብቻ የሚሰጥ ሃላፊነት አድርጎ የማሰቡ ነገር ልክ ካለመሆኑም ባሻገር ለኢትዮጵያ ብሄርተኝነት መለምለም ሲባል አማራው ሲሞት ዝም ብሎ መታየት አለበት ለማለት የሚቃጣው ነው፡፡ ስለዚህ ፕሮፌሰር አስራት የወሰዱት እርምጃ በወቅቱ አማራጭ የሌለው እንደ ነበር ይሰማኛል፡፡

የመአአድ ወደ መኢአድ መቀየር ከመነሻው የታሰበበት በመሆኑ መኢአድ እና ሌሎች ህብረብሄራዊ ሆነን በሰላማዊ መንገድ እንታገላለን ባይ ፓርቲዎች የቀጠለውን የአማራ ህዝብ እንግልት ለማስቆም ለፍተዋል፡፡ ሆኖም ልፋታቸው ከጅብ እንደማያስጥለው የአህያ ባል ያለ ነገር በመሆኑ የአማራ ህዝብ ሁለንተናዊ ፈተና ቀጥሏል፡፡ ከጥፋቱ መማር የማይችለው ህወሃት/ኢህአዴግ በአማራ ህዝብ ላይ ያነሳውን ጨካኝ ክንዱን ማጠፍ ባለመቻሉ ለአማራ ብሄርተኝነት አይናፋር የነበረውን የአማራ ልሂቅ ፈራ ተባ ከማለት በግልፅ አንዳንዴም በከፍተኛ ምሬት እና ፅንፈኝነት የአማራ ብሄርተኝነት እንዲያቀነቅን፤ ግፋ ሲልም ነውጠኛ እንዲሆን አድርጎታል፡፡ ይህ አመነም አላመነም የህወሃት/ኢህአዴግ እብሪት አይሉት አላዋቂነት የመራው ጥላቻን አደብ ያለማስያዝ ስህተት ውጤት ነው፡፡

“ከትምክህተኝነት” ወደ “ጥበት”?

ሃገር መውደዱ፣ ቅድሚያ ስለሁላችን ኢትዮጵያ ማለቱ ወንጀል ሆኖ በትምክህተኝት አስፈርጆ በድርብ ድርብርብ ለበቅ ሲያስገርፈው የኖረው አማራ ሃያ አምስት አመት ያጠራቀመው ፅዋ ሞልቶ እነሆ ዛሬ የአማራው ብሄረርተኝነት በአስፈሪ ፅንፍ ታጅቦ ድክ ድክ እያለ ነው፡፡ የዚህ ህዝብ ዝምታ እና ፅዋ እስኪሞላ መታገስ በገዥዎች ዘንድ ሞቶ ከመቀበር፣እንደሲጋራ ተረግቶ ከመጣል ተቆጥሮ በደል በላይ በላይ መዝነቡ ትልቁ ስህተት ነበር፡፡ ዛሬ ትናንት አይደለም፡፡ስለ አማራ የፈለጉትን መናገር አይቻልም፡፡ አማራነቱ ሲነገረው ብቻ ትዝ የሚለው የአማራ ልሂቅ ዛሬ ዛሬ የአማራን በክፉ መነሳት መታገስ ተስኖታል፡፡ ‘አማራን አስራ የምትገርፍ እንጀራ እናት ኢትዮጵያ አታስፈልገንም’ የሚል ያለወትሮ የሆነ የመገንጠል ድምፅ ከወጣት አማራ ልሂቃን አቅጣጫ እየተሰማ ነው፡፡ ስም ጋገራ የማይሰለቸው ህወሃት/ኢህአዴግ ለዚህ አዲስ የአማራ ልሂቃን ፅንፈኛ አቋም ምን ስም እንደሚያወጣለት ለመስማት ጉጉ ነኝ፤ መቼም አልሰማም አይባልም፡፡ እንደተባለው የአማራ ብሄርተኝነት ህወሃት/ኢህአዴግን የሚያስደስት ከሆነም መደሰቻው አሁን ነው፡፡

እስከመገንጠል የወጣው የባይተዋርነት እና ፅንፈኝነት አካሄድ ላይ ባልስማማም ለዘብተኛ የአማራ ብሄርተኝነት እንደሚያስፈልግ ግልፅ ይመስለኛል፡፡የሚታየው የአማራ ህዝብ ጠበቃ አልቦነት፣ የረዘመ መከራ፣ ቅጥያጣ የመንኳሰስ በደል፣እንደ ኦሪት ለምፃም ከሃገር ዳርቻ መዋከብ ወዘተ ነው ፅንፈኝነትን አይጋበብዝም ባልልም በኢትዮጵያዊነት ጥላስር ሆኖ የአማራ ህዝቡ በደል የሚያበቃበትን ትግል መታገሉ ተሻይ መስሎ ይታየኛል፡፡

- Advertisement -Early Bird Holiday Deals! Before you know it, the holidays will be right around the corner! Take advantage of our early bird deals today and save up to $40 on our fees with code SPOT40!
Stay Connected
28,789FansLike
12,856FollowersFollow
8,540SubscribersSubscribe
Stacy Adams
Must Read
Related News

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here