spot_img
Wednesday, November 29, 2023
Homeነፃ አስተያየትየዕብድ ገላጋዩ ሪፖርት (መስከረም አበራ)

የዕብድ ገላጋዩ ሪፖርት (መስከረም አበራ)

advertisement

መስከረም አበራ
meskiduye99@gmail.com
ሚያዚያ 24 2009 ዓ ም

ዲሞክራሲ ባልሰፈነበት ሃገር ሰብዓዊ መብት ይከበራል ማለት ዘበት ነው፡፡ እንዲህ ባለው ስርዓት የዲሞክራሲም ሆነ የሰብዓዊ መብት ተቋማትን ገለልተኝነት ወይም ነፃነት መጠበቅ ከዓለት ላይ ውሃ የማፍለቅን ተዓምር እንደ መሻት ያለ ቀቢፀ-ተስፋ ይሆናል፡፡ሃገራችን የዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ቻርተሮች ፈራሚ እንደመሆኗ የዓለም አቀፍ ህግጋቱን አንቀፆች አሁን በሥራ ላይ ባለው ህገ-መንግስቷ አካታለች፡፡‘ዲሞክራትም ልማታዊም ነኝ’ የሚለው ኢህአዴግ የሚመራው መንግስት ይህን ማድረጉ ብቻ በቂ ስለሚመስለው ወይም እንዲመስለን ስለሚፈልግ ቀደምት ገዥዎች ባላደረጉት ሁኔታ ለሰብዓዊ መብቶች ትኩረት ሰጥቶ የህገመንግስት አካል ማድረጉን ደጋግሞ ሲያወራ አይሰለቸውም፡፡ሆኖም በተግባሩ የሰብዐዊ መብት ጉዳይ በገለልተኛ እና እውነተኛ ተቋም እንዲመራ አይሻም፡፡በማስመሰሉ ዘመን እያቃረውም ቢሆን ይሁን ብሎ ህልውናውን የፈቀደለት ኢ.ሰ.መ.ጉ የተባለውን ገለልተኛ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋም በህግ፣ በጠመንጃ፣በበጀት ድርቅ ጥምር ጉልበት አዳክሞ እነሆ ዛሬ እልም ስልም በሚል ህልውና ውስጥ እንዲሆን አድርጎታል፡፡

ኢ.ሰ.መ.ጉን መላወሻ አሳጥቶ ወደ አለመኖር እያንደረደረው ያለው ኢህአዴግ ታዲያ ብዙ ያወራለት “የሰብአዊ መብት ዘበኝነት” ወጉም እንዳይቀርበት የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን የሚባል ድርጅት ሰይሞ የልቡን ይናገርለት ዘንድ በፓርላማ ያመላልሰው ይዟል፡፡ኮሚሽኑን የሚመሩት ዶ/ር አዲሱ ገ/ማርያም ቀደም ሲል የሃገሪቱን ምርጫ ቦርድ ይመሩ የነበሩ ሰው ናቸው፡፡ ሰውየው ምርጫ ቦርድን በሚመሩበት ጊዜ በኢ.ህ.አ.ዴግ ነገር አንጀታቸው የማይጠና፤ ክፉውን ማውራት የማይወዱ ከመሆናቸውም ባሻገር አንዳንዴ የሚመሩትን ተቋም ገለልተኝነት ዘንግተው ለመንግስት ወገባቸውን ይዘው ለመከራከርም ሲሞክራቸው ያጋጥማል፡፡ በተለይ በምርጫ ሰሞን ተቃዋሚዎች ለሚያቀርቧቸው አቤቱታዎች ሁሉ መረጃው እዳልደረሳቸው፤እንዲህ ያለ ነገር ይፈጠራል ብለው እንደማያስቡም ፈርጠም ብለው ይናገራሉ፡፡በአንፃሩ የተቃዋሚዎችን ድካም ያሳያል ለሚሉት ነገር ሁሉ ከበቂ በላይ በመረጃ ታጥቀው ይመጣሉ፤ስንት ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ ማድረግ ሲገባቸው ስንተ ጊዜ ብቻ እንዳደረጉ ደንቀፍ ሳይላቸው ይናገራሉ፡፡ ፓርቲዎቹን ከህይወት መዝገብ ለመሰረዝ ባበቃቸውን “ውስጣዊ ሽኩቻ”፣የትኛው አንጃ ህግ ተከትሎ ለምርጫ ቦርድ ታዞ እደሚኖር የትኛው ለምርጫ ቦርድ ታዛዥ እንዳልሆነ አበጥረው ሲናገሩ መረጃ አያጥራቸውም፤ ‘ሰው ይታዘበኝ ይሆን?’ ብለውም አይጨነቁም!

በሚኒስትር ማዕረግ ቢሰየሙም ‘ገለልተኛ ነኝ’ ብለው ምርጫ ቦርድን ይዘውሩ የነበሩት ዶ/ር አዲሱ የምርጫ ቦርድ ወንበራቸውን ለማን አስረክበው እንደመጡ ባይታወቅም የሰብዊ መብት ኮሚሽን ዋና ሰው ሆነው ምርጫ ቦርድ በነበሩበት ጊዜ የሚያባጥሏቸውን ተቃዋሚዎች በሰብዓዊ መብት መጣስ ተጠያቂ የሚያደርግ ሪፖርት ይዘው ብቅ ብለዋል፡፡ እንደ ዛር በየቦታው ብቅ የሚሉት ዶ/ር አዲሱ የምርጫ ቦርድ ወንበራቸውን ተመልሰው የሚቀመጡበት ከሆነ በሰብዓዊ መብት ጥሰት የሚከሷቸውን ፓርቲዎች በለመደ እጃቸው ከህይወት መዝገብ ለመሰረዝ ርቆ የማይርቀው መንገድ ይበልጥ ይቀርባቸዋል፡፡

በህዝባዊ አመፁ ወቅት ለተደረገው የሰብዐዊ መብት ጥሰት ተኩሶ ከገደለው ወገን ይልቅ ተቃዋሚዎችን እና የመገናኛ ብዙሃንን ተጠያቂ ያደረገው የዶ/ር አዲሱ ሪፖርት ኢህአዴግ ሲለው የባጀውን በሪፖርት ተብየው ከማድመቅ ባለፈ፤ህዝብም ኮሚሽኑን የሚያውቅበትን ማነት ይበልጥ ከማጉላት ሌላ የጨመረው ነገር የለም፡፡ኮሚሽኑ ‘ተዘዋውሬ አጣራሁ’ ባለባቸው የሃገሪቱ የተለያዩ ክልሎች ለታየው የሰብዓዊ መብት ጥሰት በምክንያትነት ያቀረበው መንግስት ሲለው ሲሰልሰው ሲደጋግመው ሰንብቶ ‘ለጥልቅ ተሃድሶ ሱባኤ አስገባኝ’ ያለውን የመልካም አስተዳደር ጉዳይ ነው፡፡ ኮሚሽኑ በተጨማሪ ምክንያትነት ያነሳው የስራ አጥነት ነገር መንግስት እስኪያቅረን ያልነገረን ነገር አይደለም፡፡ የተጠያቂነቱ ጣት የተቀሰረባቸው እነ ኢሳት፣ኦ.ኤም.ኤን እና ፌስቡክም መንግስት ቀድሞ ተጠያቂ አድርጎ በአስቸኳይ ጊዜ ህጉ እንዳይደመጡ አዋጅ ያስነገረባቸው ናቸው፡፡ ለኦሮሚያ ክልል ኦ.ፌ.ኮ፣ኦነግ ለአማራ ክልል ሰማያዊ ፓርቲ፣ ቤተ-አማራ የችግሩ አባባሽ እንደሆኑም ከመንግስት አፍ ያልሰማነው ነገር አይደለም፡፡ የሪፖርቱ ነገራ ነገር እንደውም የመንግስት እና የኮሚሽኑን አንድነት እና ልዩነት ድንግርግር ከማባባስ ባለፈ ለሰሚ ያመጣው አዲስ ነገርም ሆነ ለችግሩ አፈታት እነሆ ያለው የአዋቂ አስተዋፅኦ አይታየኝም፡፡

ሪፖርቱ መንግስት የችግሩን ዋና መንስኤ ከማጣራት ይልቅ ያልሆነ አካሄድ ለመሄድ እያዘገመ ያበትን አደገኛ አካሄድ ትቶ ወደ ተሻለው መንገድ እንዲሄድ ትክክለኛው የችግሩ ዋና ፈጣሪ የራሱ አምባገነንነት፣ እንደ አፍላ ጎረምሳ ሁሉን በቡጢ የማለት አካሄድ መሆኑን ከመንገር ይልቅ “አባረህ በለውን” እያዜመ እንደ እብድ ገላጋይ ድንጋይ የሚያቀብል ነው፡፡ መንግስት ሊበላቸው ያሰባቸውን ፓርቲዎች የጥፋቱ ሁሉ መነሾ አድርጎ ቁጭ ሲል ‘አዎ ልክነህ’ የሚል ሪፖርት ገለልተኝነቱ እንዴት ነው? ከወራት በፊት መንግስት ቢሮው ቁጭ ብሎ የጥፋቱ ሁሉ መንስኤ ያደረገውን ነገር ሳይጨምር ሳይቀንስ ቦታው ድረስ ሄጄ አጥንቼ ያገኘሁት የችግሩ መንስኤ ነው የሚል አካል ተላላ አድርጎ ያሰበው ማንን ነው?
ሪፖርቱ ጠለቅ ብለው ሲያዩትም በብዙ እንከኖች የተሞላ ነው፡፡ መረጃ ከማሰባሰብ ዘዴው ቢጀመር የመረጃ ምንጭ ተብለው ከቀረቡት አካላት ውስጥ በአካባቢው የሚገኙ የመንግስት ተወካዩች አሉበት፡፡እዚህ የመንግስት ተወካዩች የዲሞክራሲያዊ መንግስት ተወካዩች እንዳልሆኑ ግልፅ በመሆኑ በሰብዐዊ መብት ጥሰቱ የመንግስትን ትክክለኛ ድርሻ ለመናገር ወይ ይፈራሉ አለያም ራሳቸውን የመንግስት አካል አድርገው ስለሚያስቡ ጦሱን ወደሌላ ይጥላሉ እንጅ ለስብዕና ወግነው መንግስታቸውን የሚያጋልጡበት ልቅና ላይ የሚደርሱ አይመስለኝም፡፡

ሌሎቹ የመረጃ ምንጮች ተደርገው የቀረቡት የሃይማኖት አባቶች እና የሃገር ሽማግሌዎች ናቸው፡፡ የዘመናችን የሃይማኖት አባቶች እንዴት ያሉ ናቸው? ከሰማዩ እና ከምድሩ ንጉስ ይበልጡን ለየትኛው ሲያገለግሉ ነው የምናውቃቸው?እውነት እውነቱን በመናገር እንጠረጥራቸዋለን ወይ? እውነት እንናገር ቢሉስ መንግስት ከሱባኤ ሳይቀር አውጥቶ የሚፈልገውን እንደሚያደርግ አያውቁምና እውነት ሊናገሩ ይሞክራሉ? የሃገር ሽማግሌዎች የተባሉትስ እንደ ፕ/ሮ ኤፍሬም ይስሃቅ እና አትሌት ኃ/ገብረስላሴ አይነት ናቸው ሌላ?የሚለውን ነገር ይዞ መረጃቸውን የማመን ያለማመን የአድጭ ፋንታ ነው፡፡

በሶስተኛ የመረጃ ምንጭነት የቀረቡት የተጎጅ ቤተሰቦች ናቸው፡፡እነዚህ ምንጮች ተጎጅ ዘመዶቻቸው ከመከላከያ ጋር ያደረጉት ግጭት መንስኤ እና የጉዳት ደረጃን በተመለከተ መረጃ ሰጥተዋል ነው የሚለው ሪፖርቱ፡፡ምን ያህሉ የተጎጅ ቤተሰቦች በተለይ ተጎጅ ዘመዶቻቸው በግጭቱ ወቅት የት ነበሩ ተብሎ ነው ለግጭቱ መንስኤ የሆነውን ነገር በትክክል ያስረዳሉ ተብለው የታሰቡት? የሚለው ጥያቄ እንዳለ ሆኖ ያውቃሉ ቢባል እንኳን የሚያውቁትን እውነት ለመናገር አይፈሩም ለማለት የእነ ዶ/ር አዲሱ ኮሚሽን በህዝብ ዘንድ ባለው የገለልተኝነት ምስል ይወሰናል፡፡ ሌላው የመረጃ ምንጭ የነ ዶ/ር አዲሱ መስሪያ ቤት ሰዎች የምልከታ እና የቪዲዮ ምስሎች ናቸው፡፡ የነሱን ምልከታ እንዴትነት ለአንባቢ እተዋለሁ፡፡

የኦሮሚያን ህዝባዊ አመፅ ተከትሎ የተደረገውን የሰብአዊ መብት ጥሰት አጣራሁ የሚለው ሪፖርቱ ከኢሬቻው አመፅ በፊት ሃምሌ 30 የተደረገውን እንቅስቃሴ የሰው ህይወት የጠፋበት፣የአካል ጉዳት የደረሰበት እና ህይወት ያልጠፋበት እንቅስቃሴ ብሎ ለሁለት ከመክፈል ባለፈ ስንት ሰዎች በማን ህይወታቸው እንደጠፋ፣ ምን ያህሉ በማን የትኛውን አካላቸውን እንዳጡ ሰይዘረዝር ሾላ በድፍን አድርጎ ፍትህ ቢኖር እንኳን ለፍትህ አሰጣጥ እንደማይመች አድርጎ አልፎታል፡፡ 2.5ሚሊዮን ሰዎች ተገኝተውበታል ባለው የኢሬቻ በዓል ላይ የተነሳ አመፅ በተመለከተ አንድ ወጣቶት በአሉን ከሚያስጀምሩት አባገዳ የድምፅ ማጉያ ነጥቆ መንግስትን የሚያወግዝ እና አመፅን የሚገልፅ መዕክት ማሰማት ሲጀምር፣ሌሎች ወጣቶች የኦነግን አርማ ማውለብለብ እና እጅ ማጣመር ሲጀምሩ የፀጥታ ሃይሎች ነገሩን ላመረጋጋት ሙከራ ሲያደርጉ ወጣቶቹ ከፀጥታ ሃይሎች ጋር ግብግብ ጀመሩ፤ በዚህ መሃል የፀጥታ ሃይሎች አስለቃሽ ጋዝ ሲተኩሱ ተሳታፊዎች ህይወታቸውን ለማትረፍ መሯሯጥና መገፋፋት ጀመሩ፡፡ በዚህ ክስተት በአካባቢው በነበረው ገደል በመግባትና በመረጋገጥ 56 ሰዎች ሞቱ ሲል መንግስት ያለውን ሳይጨምር ሳይቀንስ ያቀርባል፡፡ ይሄ ሁሉ የሆነው በመልካም አስተዳደር ችግር፣ የመብት ጥሰት፣የስራ ቅጥር በዘመድ መሆን፣ስራ አጥነት፣የኦሮሚያ በአዲስ አበባ ላይ ያለው ልዩ ጥቅም አለመከበር ነው ይልና ኦ.ፌ.ኮ.ን፣ኦነግና ኦ.ኤም.ኤንን ደግሞ በአባባሽነት ይከሳል፡፡ የደረሰበት ምሬት ህዝብ በዓልን ሳይቀር ለብሶት መግለጫ እስከማዋል የሚያደርስ የመብት ጥሰት፣ስራ አጥነት ፣የመልካም አስተዳደር ወዘተ ችግር መኖሩ ከታመነ በኋላ ሃገር አስተዳድራለሁ የሚለው መንግስት ይህን ሁሉ ችግር በመፍጠርም ሆነ መፍትሄ ባለመስጠት ሊጠየቅ ሲገባ ዋናውን አስቀምጦ አባባሽ ፈልጎ ጦሱን ወደ ሌላ አካል መጣሉ ምን ማለት እንደሆነ ግራ ነው፡፡ ራሱ አባባሽ ማለት ምን ማለት ነው? የመረረው ህዝብ ወጥቶ ብሶቱን ለመግለፅ ምን አባባሽም ሆነ ጎትጓች ያስፈልገዋል? አመካኝቶ ፓርቲዎቹን ለመብላት ካልሆነ!

ሌላው አስተዛዛቢ ነገር የተተኮውን አስለቃሽ ጭስ አስመልክቶ ሪፖርቱ በለሆሳስ ያለፈው ነገር ነው፡፡ የአስለቃሽ ጭሱ ጉዳይ ሪፖርቱ በዓሉ ወደ አመፅ ሲያመራ የፀጥታ ሃይሎች አስለቃሽ ጭስ ተኮሱ ብሎ ብቻ በሽፍንፍን እንዳለፈው ቀላል ነገር አይደለም፡፡ አስለቃሽ ጭስ የሚተኮስበት ህጋዊ ሁኔታ እና የሰው መጠን አለ፡፡ አስለቃሽ ጭስ መተኮስ ያለበት በቁጥር ብዙ ያልሆኑ፣ ዘርዘር ብለው ለመሸሽም ሰፋ ባለ መልከዓ-ምድር ላይ ባሉ አማፅያን ላይ እንጅ እንደዚህ መተናፈሻ በሌለው፣ገበቴ በመሰለ ሸለቆ ውስጥ ታፍገው ባሉ ሚሊዮኖች ላይ እንዳልሆነ ለሰብዓዊ መብት ቆምኩ የሚል ድርጅት ግንዛቤ ያጣል ማለት አይቻልም፡፡ የአስለቃሽ ጭስ አላማ ሰዎችን መበተን እንጅ መግደል አይደለም፡፡ የኢሬቻው አስለቃሽ ጭስ ተኩስ ሰዎችን ለመበተን ታስቦ የተደረገ ከሆነ እንደዛ ባለ መልከዓምድር የተሰበሰበ በሚሊዮን የሚቆጠር ህዝብ በየት ብሎ በሰላም እንዲበተን ታስቦ ድርጊቱ እንደተፈፀመ ተኳሹን አካል መንግስትን ተጠያቂ የማያደርግ የሰብዓዊ መብት ኮሚሽ አላማው ምንድን ነው?እንዲህ ያለውን በስብዕና ላይ የተቃጣ ወንጀል አድበስብሶ አልፎ ምን ለማትረፍ ነው ባለ መቶ ሰባ ገፅ ሪፖርት የሚፃፈው? ይብስ የሚገርመው ደግሞ የበዓሉ አዘጋጆች ይህ እንዳይፈጠር የቢሾፍቱን ገደሎች መድፈን ነበረበረባቸው የሚለው የሪፖርቱ ቀልድ አይሉት ቁምነገር ነው፡፡ ይህ ነገር ሪፖርቱ አህያውን ሽሽት ምን ያህል ተንጠራርተቶ ዳውላውን እንደሚደበድብ ራሱን ከማስገመት ባለፈ የቢሾፍቱ ገደል ተሞልቶ ያልቃል ብሎ ገምቶ የሚያምን ቂል አገኛለሁ ብሎ አይመስለኝም!

ሌላው ሚገርመው ነገር የኢሬቻው አመፅ ጉዳይ የመንግስት እና የፀጥታ ሃይሎች ቀድመው እያወቁ በዓሉ እንዲካሄድ መደረጉ ህዝባዊ ሃላፊነት የጎደለው ነው የሚለው የሪፖርቱ ፈሊጥ ነው፡፡ ለመሆኑ የህዝብን በዓል በፖለቲካዊ ምክንያት ማስቀረት ለማን ይቻለዋል? በዓሉ ህዝብ በአመት አንዴ ጉጉት ጠብቆ በደስታ የሚያከብረው መሆኑ ተረሳ? ደግሞስ በዓሉን ለዩኒስኮ አስመዘግባለሁ ብሎ መደገሱ በመንግስት በራሱ ብሶ አልነበረምና ነው በዓሉን ማስቀረቱ እንደአማራጭ የቀረበው? በዓሉን ከማስቀረትና ወጣቶች እጃቸውን ሲያጣምሩና የኦነግን ባንዲራ ሲያውለበልቡ በትዕግስት አልፎ በኋላ በህግ ከመጠየቅ የቱ ይቀላል? የዛን ሁሉ ወገን አስከሬን አጋድሞ በዓለም ጉድ ከመባልና የአመፀኞችን የተጣመሩ እጆች እንዳላዩ ከማለፍ የትኛው መንግስትነትን ይመጥናል?

ሪፖርቱ አንድ አበጄ የሚባልለት ነገር ቢኖር በውጭ ሃገር የከተሙ የኦሮሞ አክቲቪስቶች እና መገናኛ ብዙሃን በኢሬቻ በዓል ላይ መንግስት በሄሊኮፕተር የታገዘ ጥቃት ፈፅሞ ከ600 በላይ ሰዎችን ገደለ ብለው ያሰራጩትን ከጤነኛሰው የማይጠበቅ፣ ሃላፊነት የጎደለው፣ ቅንነት የራቀውን አስተዛዛቢ ወሬ በተመለከተ ያቀረበው መረጃ ነው፡፡ በወቅቱ መንግስት እንኳን አደረሳችሁ የሚል መልዕክት የያዘ ወረቀት በሄሊኮፕተር የበተነበትን ሁኔታ በሄሊኮፕተር የተደረገ ወታደራዊ ጥቃት ተደርጎ ማቅረቡ ለማን ይጠቅማል ተብሎ እንደሆነ አይታወቅም፡፡

የአማራ ክልልን በተመለከተ ሃምሌ 4 ቀን የፌደራል ፀረ-ሽብር ግብረሃይል በሽብር የተጠረጠሩ ግለሰቦችን ለመያዝ ከሌሊቱ 10፡30 ያደረገውን እንቅስቃሴ ተከትሎ ሁከትና ብጥብጥ ተከትሏል ፌስቡክና ኢሳት አባብሰዋል ከማት በቀር ከሌሊቱ አስር ሰአት ሰው ቤት መሄድ ከሰብዓዊ መብት አንፃር እንዴት እንደሚታይ በመንግስት ነገር ሆዱ የማይጠናው የዶ/ር አዲሱ ቢሮ ቃል ትንፍሽ አላላም፡፡ ምናልባትም ድርጊቱ ልክ ነው ብለን እንድናስብ ተብሎ ይሆናል ዝምታው፡፡ አመፁ በመሰረተ ልማት ላይና በትግራይ ተወላጆች ላይ ጉዳት አድርሷል ይበል እንጅ በትግራይ ተወላጆች ደረሰ ያለው ጉዳት የአካል ይሁን የህይወት መጥፋት በግልፅ አያስቀምጥም፡፡ በጥቅል 11,678 የትግራይ ተወላጆች ተፈናቅለዋል ያለው ሪፖርቱ ሰዎቹ የተፈናቀሉባቸውን ቦታዎች ልዩ ስም እና ከየአንዳንዱ ቦታ የተፈናቀሉትን ሰዎች ቁጥር አይገልጽም፡፡ ይህን ያህል ሰው ከጎንደር ከተማ ብቻ ተፈናቀለ እያለ ከሆነም ግልፅ አይደለም፡፡ይሄ ሁሉ “ተፈናቃይ” በአሁኑ ጊዜ ያለበትን ሁኔታም አይገልፅም -ሪፖርቱ፡፡ የትግራይ ተወላጆች ደረሰባቸው የተባለውን ጉዳት የአማራ ህዝብ እንደመከተላቸው የሚገልፀው ሪፖርቱ ሶህዴፓ ለትግራይ ተፈናቃዮች የለገሰውን ገንዘብ ጠቅሶ ገለታ ሳያቀርብ አልፎታል፡፡ በአንፃሩ የአማራ ክልልን መንግስትና የወረዳ አስተዳደሮች ተገቢውን የደንንነት ጥበቃ አላደረጉም፣አደጋው ከደረሰ በኋላም ከመከላከል ይልቅ እግሬ አውጭኝ ብለው በመሸሻቸው የጎበዝ አለቆች አካባቢውን እስከ ማስተዳደር እንዲደርሱ አድርገዋል ሲል በአዴኖችን ከላይ እስከታች ይከሳል፡፡ በአማራ ክልል በአጠቃላይ ያለቀውን የህዝብ ቁጥር በመቶዎቹ ብቻ መጥኖ፤በተለመደው ተመጣጣኝ ሃይል የመጠቀምና ያለመጠቀም ቁማር አምታቶ አልፎታል፡፡

- Advertisement -Early Bird Holiday Deals! Before you know it, the holidays will be right around the corner! Take advantage of our early bird deals today and save up to $40 on our fees with code SPOT40!
Stay Connected
28,789FansLike
13,920FollowersFollow
8,540SubscribersSubscribe
Stacy Adams
Must Read
Related News

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here