spot_img
Wednesday, November 29, 2023
Homeነፃ አስተያየትወይ አዲስ አበባ....! (በመስከረም አበራ)

ወይ አዲስ አበባ….! (በመስከረም አበራ)

advertisement

ጳጉሜ 2 2009 ዓ ም
በመስከረም አበራ

ቅድመ-ነገር

Meskerem Abera - article -Addis Ababa
Meskerem Abera
ታሪክ የሰው ልጆችን ያለፈ የህይወት ስንክሳር መርምሮ፣ መጭው ትውልድ ካለፈው ድካምም ብርታትም እንዲማርና የተሻለ ዓለም
እንዲፈጥር ማስቻልን ያለመ የጥናት መስክ ነው፡፡የሃገራችን ወቅታዊ የፖለቲካ አተናተን ዘይቤ ክፉኛ በታሪክ ላይ የተጣበቀ ነው፡፡
ፖለቲካችን ታሪክን የሙጥኝ ማለቱ በራሱ ጥፋት የለውም፡፡አስቸጋሪ የሚሆነው ታሪካችንን ለወቅታዊ ፖለቲካችን ትንታኔ
በምንጠቀምበት ጊዜ ስነ-ልቦናችንን አብረን ማጋመዳችን ነው፡፡የሃገራችን ፖለቲካ ውቃቤ እንዲርቀው ካደረጉ ነገሮች ዋነኛው
ታሪክን እና ፖለቲካን በየግል ስነ-ልቦናችን ለንቅጠን፣ የስነልቦናችን ደመነፍስ ያቀበለንን የስሜት ግንፍላት በምክንያታዊነት ላይ
አንግሰን መንጎዳችን ይመስለኛል፡፡

ወደ ስሜታዊነት የሚመራን ፖለቲካዊ ስነልቦናችን ምንጩ ሲመረመር ወይ ዝቅተኝነት የሚያንገላታው የ‘ተበድያለሁ’ እዬዬ ነው
ወይ እብሪት የነገሰበት ‘የገዥ ነኝ’ የበላይነት ስሜት ነው፡፡ የዚህ ፖለቲካዊ ስነ-ልቦና ምንጩ ደግሞ ደመነፍሳዊ ማነብነብን
እንደ ሁነኛ የርዕዮት አለም ትጥቅ ይቆጥር የነበረው የስልሳዎቹ ትውልድ ፖለቲካዊ ስነ-ምህዳር ነው፡፡ ይህ ትውልድ ሃገሩ ፀንታቆማ ዘመን የተሻገረችበትን ሃገረሰባዊ አዕማድ፣ፖለቲካዊ መስተጋብር፣ማህበራዊ ቁርኝት፣ኢኮኖሚያዊ ትንቅንቅ ለመመርመር ጊዜ ሳይወስድ በነስታሊን ወጭት የኢትዮጵያን ወጥ ሊወጠውጥ የተነሳ፣ እንደ ቤቱ ሳይሆን እንደ ጎረቤቱ ሊኖር የፋተረ ነበር፡፡በመሆኑም ኢትዮጵያ ከሶቬት ህብረት ቀድማና ተለይታ በራሷ የታሪክ ዱካ ከመጓዟ የተነሳ የተሰበዘችበትን ፖለቲካዊ ሰበዝ ልዩ ተፈጥሮ ለመመርመር የማርክስ/ሌኒንን ድርሳን ማነብነቡ ፋታ አልሰጠውም ነበር፡፡

የማነብነብ ቱርፋቱ እውቀት የሚያመጣው እርጋታ እና ብስለት አይደለምና ያነብናቢነት እውቀት ያቀበለው የዘረኝነት ክፉ እንክርዳድ
በሃገራችን የፖለቲካ ማሳ ላይ ተዘራ፡፡ ሃገሪቱ የድሆች እስርቤት መሆኗ ቀርቶ “የብሄረሰቦች እስርቤት ነች” ተባለ፡፡ አንድ ብሄር
አሳሪ ሌላው ብሄር ታሳሪ ተደርጎ የአጋች ታቻች፤የበዳይ ተበዳይ ፖለቲካ እንደ ኤርታሌ ድንገት ገንፍሎ ይንተከተክ ያዘ! የኢትዮጵያ
ታሪክ ሁሉ የመበደል መበደል ድራማ ብቻ እስኪመስል ድረስ ተበደልኩ ባይ ሙሾ አውራጁ በዛ፡፡ አንድ ብሄረሰብ በነሲብ በዳይ
ሌላው ብሄረሰብ በጅምላ ተበዳይ ሆኖ የጎሳ ጥላቻ ሰልፍ፣ የመነጣጠል ጎራ፣ የጥርጣሬ መንፈስ በሃገራችን የፖለቲካ አየር ረበበ፡፡
ሁሉም የተሰለፈበት የዝቅተኝነት ወይ የበላይነት ፖለቲካዊ ስነልቦና እንደመራው ብድግ ብሎ ፖለቲካን መተንተን ጀመረ፡፡ ፖለቲካዊ
ስድነት በሃገሪቱ ነገሰ! የገዛ ሃገርን ቅኝ ገዥ ማለት ከአዋቂነት ተፃፈ፡፡ የሃገርን ትውፊት ማቃለል ዘመናዊነት ሆነ፡፡ የእነ
ገብረህይወት ባይከዳኝ ምጡቅ ልቦና ለሃገራችን ችግር ሃገርኛ መንስኤ እና መፍትሄ የጠቆመበትን ድርሳን ትራስ አድርጎ ተኝቶ
የነሌኒንን የጠብ ዶሴ ማገላበጥ፣ውጭ ውጭውን ማለት የምጡቅነት መለዮ ሆነ፡፡

ይህ የማነብነብ ደመነፍስ በጠመንጃ ታግዞ ስልጣን ላይ ለመውጣት በሚፋትርበት ወቅት ያዋጋ ያጋድል የነበረው ደመ-ጠጭ ዛር
በስተመጨረሻ ለህወሃት ቆሞለት ስልጣን ላይ ሰየመው፡፡ ህወሃት ከላይ ከተነሱት ሁለት ፖለቲካዊ ስነልቦናዎች በተበድያለሁ
መስመር የተሰለፈ ነበረና የህወሃት ስልጣን ላይ መውጣት ለተበድያለሁ ፖለቲከኞች ጥሩ የማላዘኛ መድረክ ፈጠረ፡፡ የተበድየ
ፖለቲካው ሰልፍ ፊታውራሪዎቹ ኦነግና ህወሃት ፍቅራቸው ገመሬ ዝንጀሮ እንዳየው ክምር ድራሹ እስኪጠፋ ድረስ ሻዕብያን ሙሾ
አውራጅ አድርገው በተበድየው ሙዚቃ ደረት ሲደቁ ባጁ!

በአንፃሩ የበዳይነት ጦስ የወደቀበት የአማራው ብሄር የሚወረወርበትን የወቀሳ ፍላፃ ለመመከት የሚያስችል መድረክ እንኳን
ተነፈገው፡፡ በሌለበት የፖለቲካ ችሎት ወንጀለኝነቱ ተረጋግጦ የመገለል ክፉ ፍርድ ተፈረደበት፡፡በሃገሩ ሁነኛ ፖለቲካዊ ውሳኔዎች ላይ
እንዳይሳተፍ በግልፅም በስውርም እግድ ተጣለበት፡፡የሽግግር ቻርተር በማርቀቅ ቢሉ ቻርተሩን ህገመንግስት በማድረጉ ሂደት ይህ ነው
የሚባል ውክልና ተነፈገው፡፡ያለፈው የሃገሪቱ ክፉ ክስተት ሁሉ ተጠያቂ ተደረገ፡፡ታሪክም አማራውን ጭራቅ አድርጎ ለማሳየት
ያስችላል ተብሎ ከተገመተበት ዘመን ይቆጠር ጀመር፡፡ የሉሲ ሃገር ኢትዮጵያም የመቶ አመት ብላቴና ተደርጋ አረፈችው!

የሰው ልጆች ያለፈ ሁለንተናዊ የህይወት ልምድ ታሪክ መባል ያለበት መቼ ነው የሚለው ነገር የሚያከራክረው ከቅርቡ ወደ ሩቁ
ሲቆጠር ነው፡፡ታሪክ እንደ ጥናት መስክ የሩቁን ለማጥናት ይጓጓል እንጅ የቅርቡን በአያሌው የሚወስነውን የሩቁን ታሪክ ጥሎ
የቅርቡን አንጠልጥሎ አይደናበርም፡፡ የሃገራችንን ፖለቲካ ቅጥ አምባር ያሳጣው ይሄው ብዙውን ጥሎ ጥቂቱን አንጠልጥሎ
የመንጎዱ የእብድ እሩጫ ነው፡፡ በደንባራ በቅሎ ቃጭል ሲጨመር ደግሞ በዚህ ላይ ስነልቦናችን ታክሎበት መመለሻችንን
በሚያስናፍቅ የቁልቁሊት ሩጫ ውስጥ ዶሎናል፤ላለመደማመጥ አማምሎናል፤ምክንያታዊነትን ለዘረኝነት አሰውቶ ፖለቲካችንን
የስነ-ልቦና ቀውስ በሽተኞች መድረክ አድርጎታል፡፡

የፊት አውራሪው ህወሃት ወደ ስልጣን መምጣት ገበያ ያደራለት የተበድየ ፖለቲካ በዚሁ ስነ-ልቦና የተጠቁ አባብሉኝ ባይ
ፖለቲከኞችን እያፈላ ይገኛል፡፡ ቀደምት የበደል ፖለቲካ ቄሰ-ገበዞች፣ የህወሃት ባለንጀሮች እነ አቶ ሌንጮ ለታ እና ጓዶቻቸው
ከህወሃትም ተፋተው፣ እድሜ ብቻ ያደረጋቸውን፣ እንደስማቸው የሚታወቁበትን የበደል ትረካ ፖለቲካ ጥቅም ጉዳት መዝነው፣
‘ዛሬ የተለየ መንገድ ይዘናል’ ቢሉም የዘሩት ዘር ግን እነሱ የተቀየሩ ዕለት የሚቀየር አይደምና በዝቶ ተባዝቶ በቦታው አለ፡፡ የነ
ሌንጮ ለታ የበደል እዬዬ ስብከት ዛሬ መምህሩን የሚያስከነዱ የጥላቻ ደቀመዛሙርትን አምርቷል፡፡ በእንዲህ ያለው ደዌ የተለከፉ
በአብዛኛው የምሁርነትንም ካባ የደረቡ ልሂቃን የሚደውሩት የከረረ የኦሮሞ ብሄርተኝነት ፖለቲካ የህመሙን ክፋት ከሚያሳዩ ብዙ
ምልክቶች አንዱ በቅርቡ የተያዘው የሃገራችን ዋና ከተማ አዲስ አበባ የአንድ ብሄር/የኦሮሞ ብሄር/ ተቀዳሚ ንብረት ነች
የሚለው ጉዳይ ነው፡፡

የብቻ አዲስ አበባ?

የአዲስ አበባ ቀደምት ነዋሪዎች የኦሮሞዎች ናቸው በሚለው እሳቤ እርግጠኛ ተሁኖ አዲስ አበባም መተዳደር ያለባት በኦሮሚያ
ክልል ስር ነው የሚል ክርክር በቅርቡ ተፋፍሞ ማነጋገሩን ቀጥሏል፡፡ይሄው የአዲስ አበባ ቀደምት ነዋሪነት እና ተቀዳሚ ባለቤትነት
ተረክ ሌሎች የዚሁ እሳቤ ውላጅ የሆኑ መብት ጥያቄዎችን ያስከትላል፡፡ በአዲስ አበባ ላይ ህገመንግስታዊ የልዩ ጥቅም
ባለመብትነት ጉዳይ፣የአዲስ አበባ በኦሮሚያ ክልል ውስጥ መገኘት ኦሮሚያን በአዲስ አበባ ላይ የባለቤት ፀዳል ለማላበስ በቂ ሁኔታ
ነው የሚሉት ክርክሮች መነሻቸው ይሄው የቀደምት ነዋሪነት ጉዳይ ነው፡፡

የኦሮሚያ ክልል አዲስ አበባ ላይ ጅኦግራፊያዊ እና ታሪካዊ ባለቤት እንደሆነች የሚወተውተው ክርክር ዋናው መሰረቱ ኦሮሞዎች
በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ በአዲስ አበባ የኖሩ የአዳም ዘሮች ናቸው የሚለው ተረክ ነው፡፡ በአዲስ አበባ ላይ የኦሮሞዎችን ቀደምት
ነዋሪነት ትርክት ተአማኒ/ኢ-ተአማኒነት ለማስረገጥ በአዲስ አበባ እና በኦሮሚያ መካከል ባለው “የባለቤት/ባለ ልዩ መብትነት”
ጉዳይ ለሚነሱ ንትርኮች በታሪካዊ መዛግብት የተደገፈ ማስረጃ ሊቀርብ ያስፈልጋል፡፡ በታሪክ ምስክርነት ሳይታገዝ የሚቀርብ
‘የኔነው የኔነው’ ሽሚያ ያደገን ሰው እንደ ህፃን ልጅ ‘ሁሉን ነገር ለእኔ’ የሚያስብል የስነ-ልቦና ቀውስ ምልክት እንጅ ሌላ ሊሆን
አይችልም!

“ተው ማነህ ተው ማነህ..”!

ባለፈው ሳምንት ONN በተባለው ቴሌቭዥን “አንደበተ ርቱዕ ምሁር” ተብለው የተጋበዙት ፀጋየ ሃራርሳ “በ1800 ዓ.ም መቶ
ፐርሰንቱ የአዲስ አበባ ነዋሪ ኦሮሞ ነበረ፤አሁን ግን በወራሪዎች ግፍ ተገፍቶ ተገፍቶ ከአዲስ አበባ ነዋሪዎች ውስጥ አስራ ዘጠኝ
ፐርሰንቱ ብቻ ኦሮሞ እንዲሆን ተደርጓል ይላሉ፡፡” የዚህ ክርክራቸውን ታሪካዊ ማስረጃ አብረው አልጠቀሱም፡፡ ሆኖም ክርክሩ አዲስ
አበባ ሰው ማኖር ስትጀምር ለመጀመሪያ ጊዜ የኖሩባት ኦሮሞዎች ናቸው የሚለውን ተረክ ለማጠናከር የተመዘዘ ሃሳብ እንደሆነ
መረዳት አይከብድም፡፡

በ1800 የአዲስ አበባ መቶ ፐርሰንት ነዋሪ ኦሮሞ ብቻ እንደ እንደሆነ ያውም ምሁር በተባለ ሰው አፍ ተሞልቶ ሲነገር ታሳቢ
መደረግ ያለበት ነገር ይህን ያህል አስተማምኖ የሚያናግር የህዝብ ቆጠራ በ1800 ያካሄደው አካል ማን ነው? ድሮ ቀርቶ ዛሬ
የሃገራችን የህዝብ ቆጠራ የትክክለኝነት ደረጃ እከሌ የእንትን ምድር ባለቤት እንቶኔ ደግሞ መፃተኛ የሚያስብል ነው ወይ? ያኔ

ይቅር ዛሬ በኮምፒውተር ዘመን የሃገራችን ህዝብ ቆጠራ ‘በሚሊዮን የሚቆጠር ህዝብ የገባበት ጠፋ’ የሚባልበት፣ የበዛው አንሶ
ያነሰው በዝቶ የሚቀርብበት እንደሆነ በደንብ የምናውቀው የቤታችን ጉድ ነው፡፡ታዲያ በ1800 አዲስ አበባ ላይ የታየ የአዳም ዘር
ሁሉ አንድ ሳይቀር ኦሮሞ ነበር ማለት ሊበሉ ያሰቧትን አሞራ ጅግራ የማለት የስነ-ልቦና ቀውስ ካልሆነ ትርጉሙ ምንድን ነው?
ደግሞስ እንዴት ባለ ምትሃት ነው በአንድ ምድር ላይ በስህተት እንኳን አንድ ሰው ሳይደባለቅ ኦሮሞ ብቻ ሊሰፍር የሚችለው? እሽ
ይሄም በሆነ ምትሃታዊ ሃይል ምክንያት ሆነ እንበልና የ1800 አሰፋፈር የአሁኗን አዲስ አበባ የባለቤትነት መብት ሊወስን የበቃው
እንዴት ነው?

ዛሬ ላይ ተቁሞ፣ሁለት ሶስት ምዕተ-ዓመት ወደኋላ ተጉዞ፣ የከተማ ባለቤትነትን መብት መወሰን ከተቻለ በዚሁ ስሌት
ከአስራስምንተኛው ምዕተ አመትም ወደ ኋላ መሄድና የባለቤትነት ጥያቄ ማንሳት ሊቻል ነው ማለት ነው፡፡ ከአስራ ስምንተኛው
ክፍለዘመን ወደ ኋላ ሲኬድ ደግሞ አዲስ አበባ ላይ ቀርቶ መላ ኦሮሚያ ላይም የኦሮሞ ህዝብ እንዲህ በገፍ አልሰፈረም ነበርና
በአሁኗ ኦሮሚያ ላይ ልዩ ጥቅም ሊጠበቅለት የሚገባ ሌላ ቀደምት የመሬት ባለቤት ህዝብ ፍለጋ መኳተን ሊያስፈልግ ነው፡፡ ነፍሱን
ይማርና ጋሼ አሰፋ ጫቦ ‘ተው ማነት ተው ማነህ የተኛው አለ ትቀሰቅሳለህ’ ይል የነበረው እንዲህ ያለውን ነገር ነበር፡፡ዛሬ
ሃብታምነቷ፣ለምለምነቷ፣ስፋቷ፣የህዝብ ብዛቷ እየተጠቀሰ በአክራሪ የኦሮሞ ብሄርተኞች ዘንድ ‘ዋ! እንዳንገነጠል’ አይነት
ማስፈራሪያነት የምትውለዋ የኦሮሚያ ምድር ከማንም ዘር ጋር አብራ ያልተወለደች፣ ይልቅስ በፊተኛው ዘመን ሌሎችን ህዝቦችን
ይዛ እንደኖረችው ሁሉ ከጊዜ በኋላ ደግሞ በተፈጥሯዊው የሰው ልጆች የመውረር መወረር አይቀሬ ክስተት ኦሮምኛ ተናጋሪ
ወገኖችንም ተቀብላ ያስተናገደች ምድር እንደሆነች ታሪክ አገላብጦ ማወቅ ያስፈልጋል፡፡
ታሪክ ምን ይላል?

የመካከለኛውን ዘመን የሃገራችን ታሪክ ግልፅ አድርገው ከፃፉ ፀሃፍት አንዱ አቶ ይልማ ደሬሳ ናቸው፡፡ ፀሃፊው “የኢትዮጵያ
ታሪክ፤በአስራ ስድስተኛው ክፍለ ዘመን” በሚል ርዕስ በፃፉት መፅሃፍ ውስጥ ለኦሮሞ ህዝቦች ወደ መሃል እና ሰሜን ኢትዮጵያ
የመስፋፋት ታሪክ የመደቡት ገፅ አነስተኛ ቢሆንም በጥሩ ሁኔታ አቅርበውታል፡፡ እግረመንገዴን ይህን መፅሃፍ ያላነበበ አንባቢ
ቢያነበው እመክራለሁ፡፡ በያዝነው አጀንዳ ላይ በማስረጃ ላይ የተመሰረተ ግንዛቤ እንዲኖር ስለሚያስፈልግ ሰፋ ተደርጎ የተቀመጠውን
ማስረጃ ከስር መሰረቱ ማቅረብን መርጫለሁ፡፡ አቶ ይልማ የኦሮሞን ህዝብ የመስፋፋት ታሪክ ሲያስረዱ በምስራቅ አፍሪካ
ከታየበት ዘመን ጀምረው እንዲህ ይተርካሉ፡፡

“ኦሮሞዎች ከመቼ ጀምሮ በምስራቅ አፍሪካ መኖር እንደ ጀመሩ፣እነሱ በዛ ስፍራ ከመስፈራቸው በፊት በቦታው የነበሩ ሰዎች
ማንነት በውል ባይታወቅም በ10ኛው ክፍለ ዘመን ሶማሌ የተባለው ነገድ ከታጁራ ሰርጥ አቅጣጫ ባነሳባቸው ተግዳሮት የተነሳ ወደ
ደቡብ እና ምስራቅ በመጓዝ በዋቢ ሸበሌና ጁባ ወንዞች መሃከል ቤናዲር በተባለው ስፍራ እና በቆላማው ባሌ ሰፈሩ፡፡ ኦሮሞዎች
ጥንታዊውን ሃገራቸውን ለቀው ከቤናዲር በቆላው ባሌ ከሰፈሩ በኋላ የፀጥታ ኑሮ ለማግኘት አልቻሉም፡፡ …..ከሰሜን ወደ
ደቡብ በተጓዙ ጊዜ በሰፈሩበት አገር በስተ ደቡብ ባንቱ የሚባሉ አርበኛ ነገድ ጎረቤት ሆኗቸው፡፡ ስለዚህ ከሰሜን
የሱማሌዎች፣ከደቡብ ባንቱዎች የሚያደርባቸው ጦርነት ምንም ጊዜ ሰላም የሰጣቸው አይመስልም፡፡ ስለዚህ ከዚህም ከአዲሱ
ሃገራቸው እንደገና መሰደድ ግዴታ ሆነባቸው፡፡……ጠብ አጫሪ ከሆኑት ከሶማሌዎች እና ከባንቱዎች ለመራቅ ይህ ሰላማዊ
የነበረው ህዝብ ዋቢንና የገናሌን ወንዝ ተከትሎ ወደ ደቡባዊ ኢትዮጵያ ወይናደጋ መሰደድ ጀመረ፡፡…….የኦሮሞ ህዝብ በስጋ
እና በወተት የሚመገብ [አርብቶ አደር] ስለነበረ ድርቅ ከሆነው ከቤናዲር አውራጃ ተጉዞ ወላቡ ወይናደጋ በገባ ጊዜ ይህች ምድር
ማርና ወተት ታፈሳለች እንደተባለችው እንደ ምድረ ከነዓን የምትቆጠር ሁና አገኟት፡፡ ኦሮሞዎች ወላቡ ብለው የሰየሙት አዲሱ
አገራቸው ብዙ ዝናብ የሚዘንብበት፣ ለምለም ምድር በመሆኑ ነድተው ላመጧቸው መንጋዎች ወሰን የሌለው ግጦሽ የሚበቅልበት
ሆኖ ተገኘ፡፡በወረዳውም ውስጥ ለሰውና ለከብት ወሰን የሌለው ውሃ የሚገኝበት ሃገር ነው፡፡……..ከሃገሪቱ ልምላሜ ሌላ
ይህ አውራጃ ጠብ ጫሪ ከሆነው ከሱማሌ ጎሳ፣ ከባንቱዎች ጉርብትና የራቀ በመሆኑ የወላቡ ሰፈር ለኦሮሞ ህዝብ ምድረ-ገነት
ሆኖ በሰላም፣ በምቾት ትዳራቸውን የሚያስፋፉበት ፋታ ሰጣቸው፡፡ ኦሮሞዎች በወላቡ የነበሩበትን ዘመን በማያቋርጥ ናፍቆት
በታሪካዊ ግጥማቸው እና ዝሙራቸው መዝግበውታል፡፡ወደ ደጋው በመሰደድ ምክንያት ከጦረኞች ስለራቁ ወደ ወይና ደጋው ከገቡ
ዘመን አንስቶ እስከ 16ኛው መቶ ክ/ዘመን መጀመሪያ ድረስ ጦርነት እና ውጊያ አልነካቸውም” (ይልማ ደሬሳ፤ የኢትዮጵያ ታሪክ
ገፅ፣ 212-216)

ከዚህ ታሪክ የምንረዳው ኦሮሞዎችም እንደማንኛውም ህዝብ በሰዋዊው የመግፋት መገፋት፣መወረር መውረር፣ ማሰደድ መሰደድ
ማህበራዊ ህግ እየተገዙ የሰፈሩ ህዝቦች እንጁ አሁን ያሉበትን የኦሮሚያ ክልል መሬት ይዘው የተወለዱ ልዩ ፍጡራን እንዳልሆኑ ነው፡፡
በምክንያት ለሚያምን ይህ በራሱ ማንም ሰው የሚኖርበት መሬት ባለቤት የመሆን መብት እንዳለው አስረጅ ነው፡፡ ምክንያቱም
ያኔ ከቤናዲር መገፋት አብርሮ ያመጣው የኦሮሞ ህዝብ የሰፈረበት መሬት ባለቤት ሆኖ እየኖረ ነው፡፡ የኦሮሞ ህዝብ በሰፈረበት
መሬት ላይ ባለቤት ሆኖ፣ ከመሬቱ ስባት እያረሰ እያረባ ከኖረ ሌላው ህዝብ የሰፈረበት መሬት ባለቤት የማይሆንበት ምክንያት
ምንድን ነው? ኦሮሚያን እንገነጥላለን የሚሉ ፖቲከኞች ደግሞ ጭራሽ የኦሮሞ ህዝብ በሰፈረበት ለም መሬት ማረስ ማርባቱ
ስለማይበቃው መሬቱን ይዞ ይገንጠል ባዮች ናቸው፡፡ እነዚህ ሰዎች የመገንጠሉን ነገር ሲያመቻቹ ኦሮሞ ያልሆነ በተለይ ደግሞ
ኦሮሚያን ወሮ ያዘ የሚሉት አማራው ከኦሮሚያ ምድር መውጣት እንዳለበት ሲያስገድዱ ሰው ወደ ገደል እስከመወርወር በደረሰ
ጭካኔ ነበር፡፡የዛሬው አዲስ አበባ የኦሮሞ ንብረት ነች ዜማም የዚሁ ምክንያት አልቦ ተረክ ቅጅ ነው፡፡ ለራሱ ጎሳ ሲሆን ሰፋሪው
ወገን የሰፈረበት መሬት ሙሉ ባለቤትነት አንሶት መሬቱን ጠቅልሎ ይዞ የመገንጠል መብት እንዳለው የሚከራከር አካል ሌላ ሰፋሪ
ለፍቶ ደክሞ ባያቀናው ከተማ ባይትዋር እንዲሆን የሚፈልግ ከሆነ እንዴት መግባባት ይቻላል?

ወደ ታሪኩ ስንመለስ ኦሮሞዎች ቀደም ብለው ያደረጉት መስፋፋት መዳወላቡ እንዳደረሳቸው የሚነግሩን አቶ ይልማ ከቤናዲር በረሃ
ወደ በመዳወላቦ ምድረ-ገነት መጥቶ የሰፈረው የኦሮሞ ህዝብ አሁንም መስፋፋትን ግድ የሚል የህይወት ህግ ስለገጠመው
መስፋፋቱን እንደቀጠለ እንዲህ ከትበዋል፤ “ኦሮሞዎች ከላይ በተመለከትነው አኳኋን በወላቡ ዙሪያ ብዙ ትወልድ
ካሳለፉ በኋላ ከልክ ያለፈ ተራብተው ምድር ጠበባቸው ከደረቁ ቤናዲር ይዘዋቸው ወደ ወይናደጋው ያመጧቸው የቦረና ዘር ላሞች
ግጦሽ ከመላበት ከለምለሙ ወይና ደጋ በደረሱ ጊዜ አለመጠን ረቡላቸው፡፡ ስዚህ ኦሮሞዎች ከወላቡ ከመንቀሳቀሳቸው በፊት
በግጦሽም መሬት እንደጠበባቸው አይጠረጠርም፡፡ ከዚህ ሌላ በጥንት ዘመን ከቀድሞ መኖሪያቸው ከአፍሪካ ቀንድ ወግቶ
ያስወጣቸው የሶማሌ ህዝብ አስራ አምስተኛው መቶ ሲጋመስ ከወይናደጋው ድረስ እየመጣ አዲሱን አገራቸውን መውረር
ጀመረ፡፡በዚህ አኳኋን የኦሮሞ ህዝብ ለመከላከል እና ለግጦሽ የሚፈልገውን መሬት አስፍቶ ለመያዝ ከሰላማዊ አኗኗር ወደ
አርበኝነት ሃሳቡን መለሰ፡፡….በዚህ ዘመን ኦሮሞዎች ከረዩ፣ቱለማ፣ሜጫ፣ወሎ በሚባል ትልልቅ ነገድ ተከፍለው ይገኙ ነበር፡፡
ስለዚህ ከረዩ የተባለው ነገድ ባሌን ፈጠጋርን ደዋሮን እንዲወር፤ ቱለማ ወደ ሰሜን ተጉዞ ዛሬ የሸዋ ኦሮሞ ምድር የተባለውን
እንዲይዝ ሜጫ በስተምዕራብ እና በስተደቡብ የሚገኘውን የኢናሪያዎችን አገር እንዲወስድና ወሎ የተባለው ነገድ በሸዋ
በስተምስራቅ ተጉዞ ከወሎ አውራጃ እስከ ትግሬ ተዘረጋውን አንጎት የተባለውን አውራጃ እንዲይዝ የተቀየሰው ኦዳ ነቤ በነበሩ ጊዜ
ነው፡፡ ነገዶቹ ሁሉ ወረራውን በአንድ ጊዜ አለመጀመራቸውን ስንመለከት የጦሩ ስልት የታቀደበትን አኳኋን በማስተዋል ስንመረምር
ከወረራው አስቀድሞ ጉዳዩ በስርአት የታሰበበት መሆኑን ልንገነዘብ እንችላለን፡፡” ገፅ፤225-226፡፡ ይህ ታሪክ ወደ ተነሳንበት
የአዲስ አበባ ባለ ልዩ ጥቅም ባለመብትነት/ባለቤትነት ጥያቄ ስረ-ነገር ይመራናል፡፡

ከላይ ያነበብነው ታሪክ በአፍሪካ ደረጃ ሳይቀር በታላቅነቱ የሚነሳው የኦሮሞ ህዝብ ወደ ሰሜን መስፋፋት ብዙ ሰው
እንደሚያስበው በግብታዊነት የተደረገ የግፋኝ ጉዞ ሳይሆን በወቅቱ በሰፊው ኦሮሞ ህዝብ ዘንድ የነበሩ ጎሳዎች ተከፋፍለው፣
የቀዳሚ ተከታዩ የጊዜ ምጥነት ተደርጎለት፣ ማን በየት አቅጣጫ እንደሚሄድ በጥንቃ ድልድል የተደረገበት መስፋፋት ነበር፡፡በዚህ
ድልድል መሰረት የዚህ ፅሁፍ ስረ-ነገር የሆነው በአሁኑ ወቅት አዲስ አበባ በመሃሉ የከተመችበት የሸዋ ኦሮሞ ክልልላዊ ግዛት
የተወረረው ቱለማ በተባለው የኦሮሞ ነገድ እንደሆነ ነው ከላይ ይልማ ደሬሳ የከተቡት ታሪካዊ ድርሳን የሚያስረዳው፡፡ ሌላው የታሪክ
ፀሃፊ ተክለፃዲቅ መኩሪያ “የኢትዮጵያ ታሪክ ከአፄ ልብነድንግል እስከ አፄ ቴዎድሮስ” በሚል ርዕስ በፃፉት መፅሃፍ ገፅ 94-95
አቶ ይልማ በሰፊው ያቀረቡትን ታሪክ እንዲህ ያጠቃልላሉ “ነገር ግን ኦሮሞዎች እንደ ሱማሌዎች የኢትዮጵያ ሰፊ ግዛት ነው እያልን
በምንመካበት በደቡብ ኢትዮጵያ ከብዙ ዘመን ዠምሮ መኖራቸው የታወቀ ነው፡፡ ነገር ግን በየምክንያቱ በመዠመሪያ ጊዜ
በጥቂቱ፤ በአፄ ልብነድንግልና በግራኝ መካከል በተደረገው ጦርነት ጊዜ ግን በየነገዳቸው እየተከፈሉ ኦሮሞዎች ቁጥራቸውን
አበርክተው ከደቡብ ኢትዮጵያ ወደ ማኽል ሸዋ ወደ ዳሞት እና ወደ ጎጃም ወደ በጌ ምድር መግባታቸው የታወቀ ነው፡፡” ስለዚህ
የዛሬዋ አዲስ አበባ የተንጣለለችበት ግዛት ከኦሮሞዎች ጋር በመካከለኛው ዘመን (ከ1562 በኋላ) የተዋወቀ እንጅ የዘመናችን
አክራሪ የኦሮሞ ብሄርተኞች አዳም ሲፈጠር በኤደን ገነት እንደተገኘ እንደዛው ሁሉ በአዲስ አበባ ምድር የሰው ፍጡር ሲታይ ቀድሞ
የታየው ኦሮሞ ነው እንደሚሉት አይነት አይደለም! እንዲህ ታሪክ ተድበስብሶ ነው እንደግዲህ አዲስ አበባ ለኦሮሞ ቤት ለሌላው
የሰው ቤት ነች እየተባለ አስተዛዛቢ ሙግት እየተነገረ ያለው፡፡

አዲስ አበባ የኦሮሞ ንብረት በመሆኗ እንደ ማንኛውም በኦሮሚያ ክልል እንደሚገኝ ከተማ ትተዳደር የሚለው ክርክር በስረጅነት
የሚጠቅሰው በታሪክ በውል ያልተደገፈው የኦሮሞ ህዝብ ቀደምት የአዲስ አበባ ነዋሪነት ታሪካዊ መብት አለው የሚለው ተረክ
ከላይ በተጠቀሰው፣ሸዋ ራሷ መቼ እና እንዴት በኦሮሞዎች እንደተያዘች በሚያስረዳው ታሪካዊ ማስረጃ ከእውነት የራቀ እንደሆነ
አይተናል፡፡ ሆኖም ለግራቀኙ ክርክር ንፅፅር እና ፍርድ እንዲመች አዲስ አበባ የኦሮሞ ቀደምት ቤት ነች የሚሉ ወገኖችን ማስረጃ
ማቅረብ ያስፈልጋል፡፡ አስረጅ ሲያቀርቡ ያጋጠመኝ የዚህ ክርክር ባለቤቶች “በ18ኛው ክፍለዘመን የአዲስ አበባ ነዋሪ ሁሉ መቶ
ፐርሰንት ኦሮሞ ነበር” የሚል ከላይ የተጠቀሰው የፀጋየ አራርሳ ገራሚ ክርክር ሲሆን ሌላው ዶ/ር ነጋሶ ሃምሌ 8/2009
ከወጣው ከአዲስ አድማስ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ታሪክ ጠቅሰው ያቀረቡት ክርክር ነው፡፡ ዶ/ር ነጋሶ ጋዜጠኛው “የአዲስ አበባ
እና ኦሮሞዎች በታሪክ ያላቸው ግንኙነት መቼ ነው የሚጀምረው?” ለሚለው ጥሩ ጥያቄ የመለሱት መልስ በአፄ ምኒልክ አባት
እና አያት ዙሪያ የሚያጠነጥን፣ የተለመደው ታሪክን ከወገቡ የሚጀምር፣ የኦሮሞ እና የትግሬ ብሄርተኞች(ኦነግ እና ህወሃት)
ውሸትን ደጋግሞ እውነት የማስመሰል፣ ከምክንያታዊነቱ ይልቅ ማደናቆሩ የበዛ የብልጣብልጥነት መልስ ነው፡፡ ብዙ የሚዞረው
የዶ/ር ነጋሶ መልስ ነጥብ ያለው እንዲህ በሚለው ማሳረጊያው ላይ ነው “….አፄ ምኒልክ ቤተ-መንግስታቸውን አሁን
ወዳለበት ያመጡት ለፍል ውሃ ቅርብ ለመሆን ነው፤ እንጅ ቦታው ላይ ኦሮሞዎች በ16ኛው ክ/ዘመን ጀምረው ይኖሩበት ነበር፡፡
….. ቦታውን ምኒልክ ሲይዙት ብዙ የጎሳ መሪዎች ተገድለዋል፡፡ ጎሳ መሪዎቹ ተገድለው መሬታቸው ለቤተ-መንግስት
ሰዎች፣ለውጭ ሃገር ዲፕሎመቶች ነው የተከፋፈለው፡፡ በህይዎት የተረፉት ሸሽተዋል፡፡ ሆን ተብሎ በማፈናቀልም ወደ
አርሲ፣ባሌ፣አካባቢ እንዲሰፍሩ የተደረጉ አሉ፡፡ ባህሉና ቋንቋውም በክርስትና መስፋፋት ጠፍቷል፡፡” የዶ/ር ነጋሶ መልስ ከላይ
ለተነሳው የቀደምትነት ጥያቄ ልከኛ ማስረጃ የሚሆነው አለም የተፈጠረው፣ታሪክ የተቆጠረው ከ16ኛው ክ/ዘመን ጀምሮ ቢሆን
ነበር፡፡ እውነታው ግን ያ አይደለም! አፄ ምኒልክ ፍል ውሃውን ከጓሮዋቸው ለማድረግ፣ ለባህር ማዶ ወዳጅ ሃገራት ኢምባሲ
ለመስራት የሃገሬውን ሰው አፈናቅለው ሊሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን እነዚህ ተፈናቀሉ የሚባሉ ሰዎች ኦሮሞዎች ብቻ ስለመሆናቸው
ምን ማስረጃ ይቀርባል? የተፈናቀሉት ሰዎች ኦሮሞዎች ብቻ ነበሩ የሚለውን ብንቀበልስ ለመላው አዲስ አበባ የኦሮሞ ቀደምት
ርስትነት ማስረገጫ በምኒልክ ዘመን በፍል ውሃ አካባቢ ኦሮሞዎች የነበሩ መሆናቸው እና በምኒልክ መፈናቀላቸውን ብቻ
ማስረጃ አድርጎ ማረብ ማንን ያጠግባል? ዶ/ር ነጋሶ ሲቀጥሉ “….ሰሜን ሸዋ አሁን ላሎ ተብሎ ሚጠራው አካባቢ ለአዲስ
አበባ እጅጉን ቅርብ ነው፤ ስለዚህ አዲስ አበባ አካባቢ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ኦሮሞዎች እንደ ነበሩ የሚታወቅ ነው ማለት ነው::”
ዶ/ር ነጋሶ በሰሜን ሸዋ አካባቢ ላሎ የሚባል ቦታ ላይ ኦሮሞዎች ከ16ኛው ክፍለዘመን ጀምሮ መኖራቸው በምን ስሌት አዲስ
አበባን የኦሮሞ ንብረት ያደርጋታል ብለው እንዳሰቡ ለኔ ግራ ነው፡፡ ኦሮሞዎች ከ16ኛው ክፍለዘመን ጀምረው የአሁኑን የሸዋ
ኦሮሞን ግዛት እንደያዙ ታሪክም ከዶ/ር ነጋሶ ሃሳብ ጋር ይስማማል፡፡ እዚህ ላይመነሳት ያለበት ጥያቄ ግን 16ኛው ክፍለዘመን
የዘመን ጅማሬ አይደለምና በዚህ ሰዓት የወረረ አካል የሃገር ብቸኛ ባለቤት ነው ከተባለ ከዛ በፊት በቦታው የነበሩ የሰው ዘሮች
ባለቤት የማይሆኑበት ምክንያት ምንድን ነው? የሚለው ነው፡፡ለዚህ ክርክር አክራሪ የኦሮሞ ብሄርተኝነት ፖለቲከኞች ሲያነሱ
የሚያጋጥመኝ መልስ ኦሮሞ በሚስፋፋበት ዘመን የሚይዘው መሬት ሰው ያልሰፈረበት ምድረበዳ እንደሆነ ነው፡፡ ይሄም
የሚያስኬድ አይደለም፡፡ የታሪክ መዛግብትን እንፈትሽ፡፡

የኦሮሞን ታሪክ የፃፉ ሌላው ፀሃፊ አለቃ አፅሜ “የኦሮሞ ታሪክ ክፍል አንድ” በሚለው መፅሃፋቸው ገፅ 171 ላይ ይህን ፅፈዋል
“…ኦሮሞ አማራን አባሮ ፈጅቶ፣ኢትዮጵያን ከትግሬ በቀር ወረሳት፡፡” ይህ ማስረጃ እኛ ከምናውቀው አባራሪ ተባራሪ ምድብ
ያፈነገጠ፤ አባራሪን (ኦሮሞ) ተባራሪን(አማራ) አድርጎ የዘመናችን ፖለቲካ በደመነፍስ ያስቀመጠውን የበዳይ ተበዳይ ድልድልን
ያቀያየረ ነው፡፡ ታሪክን ከወገቡ ጎምዶ የሚያቀርበው ወቅታዊ ፖለቲካችን የሃገራችን ብቸኛ ወራሪ አማራ የዘወትር ተባራሪ ደግሞ
ኦሮሞን አድርጎ ያቀርባል፡፡ ከጎማዳው ታሪክ እልፍ ሲሉ ያለው እውነታ ግን ሌላ ነው፡፡ የኑሮ ስንክሳር፣ የሃይል ሚዛን እንዲያባርር
ያስገደደው ሁሉ ያባርራል፣ ያፈናቅላል፡፡ሁሉም መውረር መወረር፤መስማማት መጣላት የኢኮኖሚ ጥያቄ፣የሃይል ሚዛን ጉዳይ
ነው! ባለበት ተገትሮ የሚቀር ነገር የለምና አባራሪም የተባራሪነት እጣ ይገጥመዋል፡፡ በዚህ ውስጥ ጎሳዊ ቅድስናው
ተባራሪ፣ጎጣዊ እርኩስነቱ አባራሪ የሚያደርገው የሰው ልጅ የለም፡፡ ስለዚህ ሁኔታ አለቃ ተክለኢየሱስ ዋቅጅራ በፃፉት እና ዶ/ር
ሥርግው ገላው አርትኦት በሰሩበት “የኢትዮጵያ ታሪክ” የሚል ርዕስ ባለው መፅሃፍ ገፅ 156 ላይ ይህን ፅፈዋል “…ያን ጊዜ
አማራ እና ኦሮሞ ሞጋሳ ተባብለው ቃል ኪዳን ተገባቡ፡፡ አማራ እና ኦሮሞ ከዚያ ወዲህ ተደባለቀ፡፡ያን ጊዜም ለሚመጣው
ለኋለኛው ዘመን ንግር ተነገረ፡፡ንግሩም እንዲህነው፡፡ኦሮሞ አማራን እያሳደደ ግቤን ወንዝ ባሻገረው በአማራ በዘጠነኛው በኦሮሞ
በአስረኛው ትውልድ ሲሆን ግፍ ብድር አይቀርምና ፈንታውን አማራ ኦሮሞን ያሳድደዋል ተብሎ ተነገረ፡፡ይህም ንግር ጊዜው
በደረሰበት ላይ በኋላ ይፃፋል”፡፡ ለማከል ያህል ፕ/ሮ ጌታቸው ኃይሌ “የአባ ባህርይ ድርሰቶች” በሚል ርዕስ ባሳተሙት መፅሃፍ ገፅ
123 እንዲህ ይላሉ “ኦሮሞዎች ወደ መሃል ኢትዮጵያ ገብተው የያዙት ሃገር ግራኝ ባዶ ያደረገውን ነው የሚሉትን የዛሬ ኦሮሞ ታሪክ
ፀሃፊዎችን የአባ ባህርይ ጥናት አይደግፈውም፡፡ ኦሮሞዎች ሃገር ሲወሩ ነባሩን ህዝብ እያጠፉና ኦሮሞ እያደረጉነበር…” አባ
ባህርይ ለዚህ ያቀረቡትን ነባራዊ አስረጅ እዚህ ለመፃፍ ስለማልችል አንባቢዎቼ መለስ ብለው እንዲያነቡ የተሸለ ነው፡፡ ከላይ
የተጠቃቀሱት ታሪካዊ ማስረጃዎች በኦሮሞዎች መስፋፋት ወቅት በሃገራችን የነበረውን አጠቃላዩን ነባራዊ ሁኔታ የሚያስረዱ
ናቸው፡፡ የዚህ ፅሁፍ ዋና ጉዳይ የሆነው የአዲስ አበባ እና የኦሮሞ ህዝብ ታሪካዊ መስተጋብርን ከዚህ ከትልቁ ምስል የማይወጣ
በመሆኑ አንባቢ ከትልቁ ምስል አንፃር ደግሞ እንዲያየው በማሰብ ያመጣሁት ነው፡፡

የአጠቃላይ ነገሩን ማስረጃ እዚህ ላይ ልግታና የፅሁፉ ልብ የሆነው አዲስ አበባ የምትገኝበት የአሁኑ የሸዋ ኦሮሞ ግዛት በ16
ክ/ዘመን ኦሮሞዎች ሲወረር ባዶ መሬት ነበር/አልነበረም የሚለውን ወደመመርመሩ እንለፍ፡፡ የአቶ ይልማ ደሬሳን መፅሃፍ ገፅ
245 እንመልከት፡፡ “በ1562 ዓ.ም የሐንሩፋ ገዳ 8 አመት ተፈፅሞ ከአርባ አመት በፊት በሙዳና ገዳ ጊዜ ቡታ ያረደው
ትውልድ ልጆች ባለገዳ ለመሆን ደረሱ፡፡ ቡታ ባረዱም ጊዜ ገዳውን ሮበሌ ብለው ሰየሙት፡፡ በዚህ በሮበሌ ገዳ ጊዜ ትልቅ ዘመቻ
ያደረገው የቱለማ ጎሳ ነው፤ እላይ እንደተመለከትነው ሁሉ ከረዩዎች ወደ ምስራቅ፤ መጫዎች ወደ ምዕራብ፤ ወሎዎች ወደ
ምስራቅ ሰሜን መጓዛቸውን ስናትት ቱለማዎችን ኦዳ ነቤ ላይ ተውናቸው፡፡ በ1562 ዓም ቱለማዎች ከኦዳ ነቤ ዙሪያ ተነስተው
ሸዋን ለመውረር በተጓዙ ጊዜ በአዝማች ዘረ ዮሃንስ የተመራ የንጉሠ ነገሥት ጦር መንገድ ላይ ጠብቆ ገጠማቸው፡፡ ከጦርነቱም
ላይ አዝማች ዘረ ዮሐንስ ሞቱ፤ሰራዊቱም ተሸነፈ፡፡ በዚያን ጊዜ ሮበሌ ባለገዳዎች የሸዋና የጎጃም መንገድ እንደተከፈተላቸው
ቆጥረው በግስጋሴ ወደ ፊት ተራምደው ዛሬ የሸዋ ኦሮሞ ምድር ከተባለው አገር ላይ ሰፈሩ፡፡” ከዚህ የምንረዳው ቀላሉ ነገር
ኦሮሞዎች የአሁኑን የሸዋ ኦሮሞ ግዛት ሲወሩ በቦታው ሌሎች ሰፋሪ ህዝቦች እንደነበሩ ነው፡፡ ህዝቦቹ ገዥ ንጉሰ-ነገስት የነበራቸው
ነገር ግን የኦሮሞዎቹ ጉልበት ስለጠናበት ወረራውን መቋቋ የተሳነው በመሆኑ ሳይወድ በግድ መወረሩን የተቀበለ እንደሆነም
እንረዳለን፡፡ ይህ የመውረር መወረር ክስተት ያለና የነበረ በመሆኑ በታሪክ ሁነትነቱ ከመቀበል ሌላ ትርጉም ያለው ነገር የለም፡፡
ኦሮሞዎቹ በሸዋ ምድር ከመስፈራቸው በፊት የነበሩ ህዝቦችን ማንነት የማፈላለግ ስራ-ፈት ጥያቄ አንስቼ፣ የአዲስ አበባ
ባለቤቶች ኦሮሞዎች ሳይሆኑ ከነሱ በፊት በንጉስ እንቶኔ ሲመሩ የነበሩት የእንትን ጎሳ ሰዎች ናቸው የሚል አዋጭ ያልሆነ ክርክር
ውስጥ መግባት አልፈልግምና የታሪክ መዛግብት ምርመራየን እዚህ ላይ ልግታና እስካሁን ያየናቸው የታሪክ መዛግብት
የሚያቀብሉን መረጃ ከወቅታዊው የአዲስ አበባ ባለቤትነት ጥያቄ ጋር ያለውን መስተጋብር ላንሳ፡፡

ይሄን ሁሉ ያነጋገረን ጉዳይ አዲስ አበባ በታሪክ ቀደምት ነዋሪዎቿ ናቸው የተባሉት የኦሮሞዎች ንብረት መሆን እንዳለባት የሚነሳው
ክርክር ነው፡፡ ይህ በታሪክ መነፅር ሲፈተሸ ኦሮሞዎች እና አዲስ አበባ የምትገኝበት ሸዋ የተዋወቁት በ1562፣ ኦሮሞዎች
ቀድሟቸው በአካባቢው ተገኝቶ፣ አገዛዝ መስርቶ የነበረን የንጉሰነገስት ጦር አሸንፈው አካባቢውን በመውረራቸው ሳቢያ እንደሆነ
አረጋግጠናል፡፡ ስለዚህ ኦሮሞ የአዲስ አበባ ቀደምት ነዋሪ ነው በሚለው ከእውነት የራቀ ክርክር ላይ ተቁሞ የሚነሳው ኦሮሞ
ህዝብ የበለጠ የአዲስ አበባ ባለቤትነት መብት ይከበርለት የሚለው ጥያቄ የማያስኬድ ነው ማለት ነው፡፡ በነገራችን ላይ በግሌ
የቀደምት ነዋሪነት ክርክር ራሱ ሳይንሳዊ አይመስለኝም፡፡ ምክንያቱም ቀደምት የምንለው ታሪክ ራሱ ሌላ ቀደምት አለውና
ዘመንን ከሚመች ቦታ ጀምሮ ቆጥሮ እኔ ቀደምት ነኝ ሚለው ክርክር ትርጉም የማይሰጥ ነው፡፡የሆነው ሆኖ የቀደምትነቱ ጨዋታ
ቀደምትነትን ከሚመቻቸው ቦታ ለሚቆጥሩ አካላት ሌላ የቀደምትነት አቅርቦት ስላለው እዳው ገብስ ነው፡፡

ከባዱ ነገር የቀደምትነት የታሪክ ልቃቂተ ሲጎለጎል፣የታሪክ ሃቅ ከፈለጉት ቦታ አንስቶ ወዳልፈለጉት ቦታ ሲያስቀምጥም
የቀደምትነቱን ዜማ እንደያዙ መቆየቱ ነው፡፡አክራሪ የኦሮሞ ብሄርተኛ ፖለቲከኞች የቀደምትነት ውሽልሽል ክርክራቸው ላይ
ተመስርተው የአዲስ አበባ ባለቤትነትን ጥያቄ ሲያነሱ የሚወክሉት የራሳቸውን ስስታምነት እና የስነልቦና ቀውስ እንጅ በጉዲፈቻ
ላሳደገው ልጅ ሃብት ንብረቱን ከወለደው ልጅ እኩል የሚያካፍለውን የኦሮሞ ህዝብ ስነልቦና አይመስለኝም፡፡ እነዚህ ፖለቲከኞች
ቀደምት ነዋሪነትን ጠቅሰው የአዲስ አበባ ባለቤትነት ይገባናል ካሉ ከአዲስ አበባ ቀድመው መጠየቅ ያለባቸው ታሪክ ሲገለጥ
የኦሮሞ ህዝብ ከአዲስ አበባም ከመዳወላቡም ቀድሞ ይኖርበት የነበረውን በረሃማውን የቤናዲርን ግዛት ነው፡፡ ይህን ግን
አያደርጉም፡፡ ምክንያቱም ያልሆነውን የቀደምትነት ጥያቄ ያስነሳቸው ኢትዮጵያዊ ሁሉ የለፋበት የአዲስ አበባ ወቅታዊ
መንቆጥቆጥ እንጅ እነሱ የሚሉት፣ ታሪክ ግን የማያውቀው የቀደምትነትን ነገር አይደለም፡፡ እነዚህ ፖለቲከኞች የአዲስ አበባ
ባለቤትነታቸውን ለማስረገጥ የሚጠቅሱት የታሪክን መዝገብ ብቻ ስላልሆነ በህገመንግስታዊ እና መልከ-ዓምድራዊ ማስረጃዎች
ላይ ተመስርተው የሚያነሱትን ሙግቶች ለማጠየቅ ደግሞ ለሚቀጥለው እትም ላሳድረው፡፡

ጸሀፊዋን በሚከተለው የኢሜይል አድራሻ ማግኘት ይቻላል:: meskiduye99@gmail.com

___
በዚህ ድረ ገጽ መጣጥፍ ለማውጣት በሚከተለው አድራሻ ኢሜይል ያድርጉልን። editor@borkena.com

- Advertisement -Early Bird Holiday Deals! Before you know it, the holidays will be right around the corner! Take advantage of our early bird deals today and save up to $40 on our fees with code SPOT40!
Stay Connected
28,789FansLike
13,920FollowersFollow
8,540SubscribersSubscribe
Stacy Adams
Must Read
Related News

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here