ቦርከና
ታህሳስ 1,2010 ዓ ም
በደቡብ ምዕራብ እና ደቡብ ምስራቅ ዮኒቨርስቲዎች ሲስተዋል የከረመው በብሄር ላይ የመተሰረት ግጭት እና ከዚያው ጋር ተያያዞ የተነሳው ውጥረት እና ጭንቀት ወደ ሰሜን ኢትዮጵያ እንደተዛመተ ተሰማ።
በትግራይ ክልል በአዲግራት ዮኒቨርስቲ የሚማሩ የአማራ እና የኦሮሞ ብሄር ተወላጂ ተማሪዎች በትግራይ ክልል ተማሪዎች ጥቃት እየደረሰባቸው እንደሆነ ፤ በዚህም ምክንያት ቢያንስ ሶስት የአማራ ክልል ተማሪዎች እንደተገደሉ በማህበራዊ ድረ ገጽ የሚወጡ መረጃዎች ያመለክታሉ። በመቶዎች የሚቆጠሩ ሌሎች ተማሪዎች ራሳቸውን በየዶርሚቶሪያቸው ቆልፈው እንዳሉም ተሰምቷል። ስለ ተገደሉት ተማሪዎች ማንነት እና ሌሎች ዝርዝሮች በዚህ ሰዓት የተገኘ ተጨማሪ መረጃ የለም።
ጉዳዮን የሚከታተሉ የአማራ መብት ተሟጋቾች እንደሚሉት በአዲግራት የነበረው ውጥረት ሶስት ቀናትን ያስቆጠረ እንደሆነ እና የጸጥታ ኃይል ችግሩን ለማስቆም ትርጉም ያለው ስራ እንዳልሰራ በመጠቆም የሌላ ክልል ተማሪዎች ተጨማሪ ጉዳት ሳይደርስባቸው ከትግራይ የሚለቁበትን ሁኔታ መፈጠር አለበት የሚል ሃሳብም እየሰነዘሩ ነው።
አዲግራት ዮኒቨርሲቲ ስለተነሳው ችግር የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቭዥን ትላንት በፌስ ቡክ ገጹ የዘገበው ጉዳይ ነው። የመንግስት መገናኛ ብዙሃህን እስካሁን በጉዳዮ ላይ ያቀረቡት ዘገባ የለም።
በትግራይ ከሌሎች ክልልሎች በተለይም ከአማራ እና በኦሮሞ የሚመጡት ተማሪዎች ላይ በዚህ ሳምንት እንደ አዲስ የተጀመረው ጥቃት ምክንያቱ ባለፈው ሳምንት በወልዲያ ከነማ እግር ኳስ ክለብ ደጋፊዎች እና በመቀሌ ከነማ እግር ኳስ ክለብ ደጋፊዎች መካካከል በወልዲያ ግጭት ከተነሳ በኋላ እና የመቀሌ ከነማ ደጋፊዎች ጉዳት ደረሰብን በማለት በመቀሌ ሰልፍ ከወጡ በኋላ ነው።
ብዙዎች ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በስፋት እየተስተዋለ የመጣው የብሄር ግጭት የጎሳ ፖለቲካ ጡዘት ያመጣው ችግር እንደሆነ ሲያምኑ፤ በስልጣን ላይ ያለው መንግስት ደሞ የጎሳ ፓለቲካ “የብሄር ብሄረሰቦችን ነጻነት አስከብሯል፤ ችግሩ ህገ መግስታዊ ስርዓቱ አደጋ ላይ ሰለወደቀ ነው” ባይ ነው።
———
ቦርከናን በፌስ ቡክ ላይክ ማድረግ አይርሱ። ከኢትዮጵያ መረጃ ለማካፈል ከፈለጉ በፌስ ቡክ በውስጥ መስመር ወይንም ደሞ በሚከተለው የኢሜይል አድራሻ ይላኩልን። editor@borkena.com