ታህሳስ 11 ፤ 2010 ዓ ም
የኢሕአዴግ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ባለፈው አመት በድርጅታችን የተጀመረውን በጥልቀት የመታደስ ንቅናቄ አፈፃፀም በዝርዝር መገምገም ጀምሯል፡፡
በድርጅታችን ኢሕአዴግ የቆየ ባሕል መሰረት አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ፕሮግራሙን ተግባራዊ ለማድረግ በሚያካሂደው የትግል ሂደት የሚያጋጥሙትን ጉድለቶች ሰፊ ጊዜ ሰጥቶ በጥልቀት ይገመግማል። ግምገማውን መሰረት በማድረግም ራሱን በራሱ ያርማል። እነሆም የኢሕአዴግ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ቀደም ሲል የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባላት የነበሩና የተተኩ ነባር ታጋዮችን ባከተተ አግባብ ከታህሳስ 3 ቀን 2010 ዓ.ም ጀምሮ ግምገማ በማካሄድ ላይ ይገኛል።
ኢሕአዴግ የህብረተሰቡን ለውጥ የሚመራ ድርጅት ሲሆን አስተማማኝ የለውጥ መሪ የሚሆነውም ራሱንም እየለወጠ መሆኑን በፅኑ ያምናል፡፡ እናም ሁሌም ራሱን እየገመገመ ከነባራዊው ሁኔታ የሚመጥን ድርጅታዊ ቁመና ለመያዝ ያላሰለሰ ጥረት ያደርጋል። በአሁኑ ወቅት አገራችን በፈጣን ኢኮኖሚያዊ እድገት አቅጣጫ ወደፊት እየገሰገሰች እንደምትገኝ መላ የአገራችን ሕዝቦችና አለም አቀፍ ማህበረሰብ ጭምር በገሃድ የመሰከሩት ሃቅ ነው።
በአሁኑ ወቅት በአገራችን በመታየት ላይ የሚገኙት በዋነኛነት ከልማት፣ ከመልካም አስተዳደርና ከሰላም ጋር የተያያዙ ችግሮች የማያዳግምና መሰረታዊ የሆነ መፍትሄ የሚሰጡ ይሆናል። እስካሁን በተደረጉት ግምገማዎችም የችግሮቹን አይነተኛ ባህሪዎችና ዋነኛ መንስዔዎች አስመልክቶ ዝርዝር ውይይት የተደረገ ሲሆን በአመራሩ ዘንድ ከመቼውም ጊዜ በላቀ አኳኃን የአስተሳሰብ አንድነት መፍጠር ተችሏል። የአስተሳሰብ አንድነት ለተግባር አንድነት መሰረት በመሆኑም ኢሕአዴግ የኢትዮጵያ ሕዝቦች የሰጡትን ሃላፊነት በብቃት ለመወጣት እንደወትሮው በላቀ ደረጃ ለመንቀሳቀስ ዝግጁ መሆኑን ይገልፃል።
የኢሕአዴግ ስራ አስፈፃሚ በአሁኑ ሰዓት ሀገራችን ፈጣን ኢኮኖሚያዊ እድገት በፈጠረው ተስፋና የተከመሩ ፖለቲካዊ ችግሮች ፊታችን ላይ በደቀኑት ስጋት መካከል አጣብቂኝ ውስጥ የገባችበት ሁኔታ እንዳለ በትክክል ይገነዘባል። ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴው የተጀመረውን ፈጣን እድገትና የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ እስካሁን የመጣበትን ርቀት ለማሳካትም ሆነ ወደፊትም ለማስቀጠል በኢሕአዴግ አባል ድርጅቶች መካከል ካሁን በፊት የነበረው አኩሪ በመተጋገል ላይ የተመሰረተ አንድነት በቦታው ላይ መሆኑን ማረጋገጥ እንደሚያስፈልግ ያምናል። ስራ አስፈፃሚው እስካሁን ባደረገው ግምገማ በአራቱ ብሔራዊ ድርጅቶች መካከል ያለው ግንኙነት በተለይም ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ የርስ በርስ መጠራጠር ያመዘነበት፣ አለመተማመን ቀስ በቀስ እየገነነ የመጣበት መሆኑን በጥብቅ ተገንዝቧል። በዚህ ላይ ተመስርቶ በተደረገው ሰፊና ጥልቅ ውይይት በዚህ ረገድ የታዩ ችግሮችን በስፋት መርምሮ የቆየውን የሃሳብና የተግባር አንድነት ለማምጣት የሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ የጋራ መግባባት ላይ ደርሷል።
ስራ አስፈፃሚው በተጨማሪም ባለፉት ሁለት አመታት ድርጅታችን ኢሕአዴግ ያደረገው የጥልቅ ተሃድሶ እንቅስቃሴ በርካታ አበረታች ውጤቶች የተገኙበት ቢሆንም በሚፈለገው ደረጃ ጥልቀት ያልነበረው ከመሆኑ ጋር ተያይዞ ተመልሰን ወደ አዘቅቱ መመለስ መጀመራችንን በትክክል አስቀምጧል። በሃገራችን የተለያዩ አካባቢዎች እየተከሰቱ ያሉ ደም አፋሳሽ ግጭቶች በዋነኛነት የድርጅታችን አመራር ያሳየው ድክመት የፈጠራቸው መሆናቸውን በሚገባ ይገነዘባል። ሃገራችን በአሁኑ ሰዓት ለምትገኝበት አስጊ ሁኔታ ድክመቱ ያደረገው አስተዋፆ ከፍተኛ ነው።
የድርጅታችን በየደረጃው ያለው አመራር ከሞላ ጎደል የዚሁ ድክመት ተጋሪ ቢሆንም ስራ አስፈፃሚው የዚህ ችግር ዋነኛ ባለቤት መሆኑንና ሕዝባዊ ወገንተኝነቱ እየተሸረሸረ ችግሮችን በቁጭት መንፈስ ከመፍታት ይልቅ የእርስ በርስ ንትርክ ላይ እንደሚያተኩር መግባባት ላይ ተደርሷል።
የውስጠ ድርጅት ዴሞክራሲ በድርጅታችን ውስጥ ያለበት ደረጃ ከፍተኛ ድክመት የሚስተዋልበት መሆኑንና ህብረተሰባችን ውስጥ ጤናማ ዴሞክራሲያዊ ሕይወት በመፍጠር ረገድ ያደረሰውን ተፅዕኖ ስራ አስፈፃሚው በሚገባ ይረዳል።
እስካሁን በተደረገው ጥልቅ ግምገማ ከስኬት ጎዳና እያራቁን የሚገኙ የአስተሳሰብና የተግባር አንድነት መታጣት፣ የርስ በርስ መጠራጠር፣ የውስጠ ድርጅት ዴሞክራሲ እጦትና የሕዝባዊ ወገንተኝነት መሸርሸር ተገቢ ውይይት ተደርጎባቸው የሕዝባችንን የመልካም አስተዳደር፣ የዴሞክራሲ፣ የልማትና የሰላም ጥያቄዎችን በሚገባ ለመመለስ በሚያስችሉን አቅጣጫዎች ላይ መግባባት ተደርሷል። ከምንም ነገር በላይ በሃገራችን በየቦታው የሚከሰቱ ግጭቶችን ከመፍታትና የፌዴራል ስርዓታችንን ከአደጋ ከመታደግ አንፃር የህግ የበላይነትና ተጠያቂነትን ባረጋገጠ መልኩ የተጠናከረ ስራ መስራት እንዳለብን የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴው የጋራ አቋም ይዟል።
የድርጅታችን ስራ አስፈፃሚ ለሃገራችን ሕዝቦች ጥያቄ በተሟላ መልኩ መመለስና ለፌዴራል ስርዓታችን በአስተማማኝ ሁኔታ መጠበቅ አስፈላጊ የሆኑ የመፍትሄ አቅጣጫዎችን ለማስቀመጥና ለዚህ ግብ ዝግጅት አስፈላጊ የሆኑ እርምጃዎችን ለመውሰድ የሚያስችለውን የተሳካ ውይይትና መተጋገል በፅናት ቀጥሎበት በቅርብ ጊዜ በድል የሚያጠናቅቅ ይሆናል። ሂደቱንም ለመላው የሀገራችን ሕዝቦችና ለኢሕአዴግ አባላት በተከታታይ የሚገልፅ መሆኑን ያስገነዝባል።