ቦርከና
ጥር 19 2010 ዓ ም
ዛሬ በመርሳ ከተማ ባሳለፍነው ሳምንት በወልዲያ እና በቆቦ በንጹሃን ዜጎች ላይ አጋዚ በመባል በሚታወቀው የህወሓት መንግስት ታማኝ ወታደሮች የተደረጉ ግድያዎችን ለማውገዝ በተጠራ ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ ላይ በተወሰደ የኃይል ርምጃ ቢያንስ አስር ያህል ሰዎች እንደተገደሉ ተሰምቷል። በርካታ ሰዎችም ቆስለዋል። የመንግስት መስሪያ ቤቶች እና ከገዥው የህወሓት ፓርቲ ጋር ንክኪ አላቸው ተብለው የሚታመኑ የንግድ ተቋማት ላይ ክፍተኛ ጥቃት ደርሷል። ቤቶች ተቃጥለዋል። በከተማዋ በሰሜን እና ደቡብ ጫፍ ያሉ መንገዶች ተዘገተዋል።
ማንነታቸው እንዳይገለጽ በመጠየቅ ለቦርከና በውስጥ መስመር መረጃ ያደረሱ ሰዎች እንደሚሉት በከተማዋ ባለው የፖሊስ ጣቢያ የነበሩ እስረኞችንም ማስለቀቅ ተችሏል።
ባለፈው ሳምንት የአጋዚ ሰራዊት በወልዲያ የቅዱስ ሚካኤልን ቃና ዘገሊ በዓል በማክበር ላይ በነበሩ ምዕመናን ላይ ባደረሰው ግፍ የተሞላበት ጥቃት ምክንያት ህጻናትን ጨምሮ በርካታ ሰዎች እንደተገደሉ የሚታወስ ሲሆን ይሄንኑ ግድያ ለማውገዝ በቆቦ የተቃውሞ ሰልፍ በማድረግ ላይ የነበሩ ሰልፈኞች ላይም ተመሳሳይ የግፍ ርምጃ ተወስዶ ቢያንስ ሰባት ያህል ሰዎች እንደተገደሉ ይታወቃል። የቆቦው ግድያ በተዋጊ ሄሊኮፕተሮች የታገዘ እንደነበረም ከአካባቢው መረጃ ያደረሱን ነዋሪዎች ተናግረዋል። ቆቦ በነበረው ግድያ የተቆጡ የከተማዋ ነዋሪዎች ሁለት ያህል የአጋዚ ወታደሮችን ገድለዋል።
———
ወቅታዊ መረጃን ለማግኘት ቦርከናን በፌስ ቡክ ላይክ ያድርጉ።