በእውቀቱ ዘኢትዮጵያ
ጥር 19 2010 ዓ ም
የእባብ ልጅ እባብ እንደሚባለው ሁሉ ይህ ግለሰብ በየጊዜው በሚያቀርበው የፅሁፍ ቡቱቶ ዋናው ትኩረቱ ኢትዮጵያውያኖች እርስበራሳቸው በጠላትነት እንዲተያዩ መርዝ ማሰራጨት ነው። በተለይ በአሁኑ ወቅት ሁሉም ኢትዮጵያዊ በመተባበር አቅሙንና ትኩረቱን ፀረ ኢትዮጵያ በሆነው ወያኔ ላይ ማድረግ በሚገባው ወቅት ይህ ግለሰብ ሌላ አጀንዳ እየፈጠር ኢትዮጵያውያንን ለመከፋፈል መወራጨቱን አብዝቷል። በኢትዮጵያ ባንዲራ እየተጠቀለለና የኢትዮጵያዊነት ዋና ተካራካሪነኝ ብሎ በማስመሰል ኢትዮጵያውያን ድርጅቶችና ግለሰቦች ላይ የሚያወርደው የማዋረድ ዘመቻና በመሀከላችን የሚረጨው የጠላትነት መርዝ ቀላል አይደለም። እራሱ የፈጠረውን አሉባልታ ከዚ ወይም ከዛ አገኘሁት በማለት፤ ወይም አንድ ወዳጄ ነገረኝ በማለት፤ ወይም በህይወት የሌለ ሰው በምሥክርነት እየጠቀሰ፤ ወይም የግለሰቦችን ስህተት እያገዘፈ ወዘተ በኢትዮጵያውያን መሀከል መርዝ ሲረጭ ኖሯል አሁንም በሰፊው እየቀጠለበት ይገኛል። በኢትዮጵያውያን የፓለቲካ ድርጅቶች መካከል ንትርክ ወይም መበጣበጥ ሲፈጠር የዚህ ግለሰብ ዋናው ተግባር ኢትዮጵያውያኖቹን ለማስታረቅ ሙከራ ማድረግ ሳይሆን አንዱን ክፍል በመወገን የአሉባልታና የፈጠራ የወሬ ቡትቶዎችን በማሰራጨት ንትርኮችና ብጥብጦቹ ወደ ጠላትነት እንዲለወጡና የተቃረኑት ኢትዮጵያዊያኖች እንዲቋሰሉ ድንጋይ በማቀበል የተቻለውን ሁሉ መርዝ ሲረጭ ይከርማል። ስለዚህ ግለሰብ መፃፍ ጊዜ እንደማጥፋት የሚቆጠር ቢሆንም፤ ነገር ግን በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያውያን መሀከል ትብብር በሚያስፈልግበት ወሳኝ ወቅት ላይ ይህ ግለሰብ አንዳንድ የዋህ የሆኑ ኢትዮጵያውያን ወንድሞቻችንን ወይም በግለሰብ ወይም በድርጅት ጥላቻ ተሸፍነው ትልቁን የአገር ችግር ለማየት የተቸገሩትን ኢትዮጵያውያን ወንድሞቻችንን፤ ወይንም በራሳቸው የአስተሳሰብ ርዕዮተ አለም እንከንየለሽነት በእጅግ የተመኩ ኢትዮጵያውያን ወንድሞቻችንን እያማለለና እያታለለ መርዝ የመርጨት ተግባሩን በሰፊው በመቀጠል የኢትዮጵያውያንን ፀረ ወያኔ ትብብር ለመጉዳት ከፍተኛ ጥረት እያደረግ ይገኛል።
አቶ ጌታቸው ረዳ ዋና ተግባሩ የሆነው በብዙ ኢትዮጵያውያን ዘንድ የሚወደዱ የሚከበሩና እንዲሁም ለኢትዮጵያ ብዙ የደከሙ ኢትዮጵያውያን ድርጅቶችንም ሆነ ግለሰቦችን ስህተቶች እየፈለገና እያገዘፈ የፈጠራ አሉባልታዎችንም እየጨመረበት እነዚህ ግለሰቦችም ሆነ ድርጅቶችን ለማስጠላት ከፍተኛ ዘመቻ በማድረግ የኢትዮጵያውያንን ትብብሮች ለማዳከም መትጋት ነው። ግለሰቦችም ሆነ ድርጅቶች ስህተት ሊፈፅሙ ይችላሉ። ብዙ የሚሰራ ሰውም ሆነ ድርጅት ይሳሳታል። የማይሰራ ብቻ ነው ስህተት የማይፈፅም። ለኢትዮጵያ ብልፅግናና እድገት ይበጃል በማለት በያዙት አቋም ግለሰቦችም ሆነ ድርጅቶች ስህተት ሊሰሩ ይችላሉ፤ ይህንን ስህተት ግን ሆን ተብሎ ኢትዮጵያን ለመጉዳት የተደረገ ነው ብሎ በማናፈሰና አሉባልታ በመጨመር የወንድሞቻችንን መስዋዕትነትና ድካም ከንቱ ለማድረግ መሞከር ኢትዮጵያውያንን ማዋርድ እንጂ ለኢትዮጵያ መቆርቆር አይደለም። ያለፉት ቅደመ አያቶቻችን፣ አያቶቻችን፣ አባቶቻችንም ሆነ ወንድሞቻችን አገራችን ኢትዮጵያን ታላቅ አገር እናደርጋታለን በማለትና በወቅቱ የነበረውን መሪ አስተሳሰበ በመከተል የሚቻላቸውን አድረገው አልፈዋል። የፈጠሯቸው በጎ ተግባራትም ሆነ ስህተቶች የኛው የኢትዮጵያውያኖች ናቸው። ይህ ለዚህ ያ ለዚያ የሚባል የለም፤ ሁሉም ወገኖቻችን ናቸው አራት ነጥብ። አገራችን ኢትዮጵያን ይጠቅማል ብለው በሞከሩት መንገድ ለተፈጠሩት ስህተቶች የምናወግዛቸው ሳይሆን ለሙከራቸው፣ ለተግባራቸውንና ለመስዋዕትነታቸው ትልቅ ክብር በመስጠት ከተፈጠሩት ስህተቶች ትምህርት በመቅሰም የተሻለ ለመስራት ትምህርት ማግኘት ይገባናል። በውግዘት ብኩንነት እንጂ ትምህርት ማግኘት አይገኝም።አሁን ያለው ትውልድ ትልቁ ኃላፊነት ካለፉት በጎ ተግባራትና ስህተቶች በመማር የተሻለች ኢትዮጵያ ለመፍጠር መትጋት እንጂ ጎራ በመለየት ጠላትነት ማስፋፋት መሆን አይገባውም። አሁን ላይ ሆኖ ያለፈውን መተቸት እጅግ በጣም ቀላል ነገር ነው። ዛሬ የዕውቀት፣ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂና ኮሙንኬሽን በተሰፋፋበት ጊዜ ላይ ሆኖ የድሮውን የዕውቀትና የኮሙኒኬሽን ደረጃ መረዳት ያስፈልጋል። የተፈጠረውንም ስህተቶች በወቅቱ በነበረውን የዕውቀትና የሥልጣኔ ደረጃ መመዘን ያስፈልጋል። አሁን ላይ ሆኖ ያለፈውን ስህተት ማየት እጅግ በጣም ቀላል ነው። ነገር ግን ያለፈውን ለመማሪያ እንጂ ለውግዘት መጠቀም የደካማነትና የብክነት መንፈስ ነው። ትልቁ ቁም ነገር ካለፈው በመማር አሁን ላይ ሆኖ ለአሁን የሚሰራ ኢትዮጵያውያንን የሚያስተባብርና የሚያስከብር ተግባር መፈፀም ነው። በአሁኑ ወቅት በወንድማማቾች ኢትዮጵያውያን ላይ ጥላቻ ለማሰራጨት እንቅልፍ አጥቶ መድከም ለወያኔ ይጠቅም ይሆን እንጂ ለማንም የሚጠቅም አይደለም።
አቶ ጌታቸው ረዳ ማወቅ የሚገባህ ወያኔ ፀረ ኢትዮጵያ መሆኑን ነው። ወያኔ ሁልጊዜም በኢትዮጵያውያን የተተፋና በአሁኑ ወቅትም በተለያዮ የኢትዮጵያ አካባቢዎች እየተጠቃ ይገኛል። በአገር ቤት የሚገኘው ሕዝብ ወያኔ ላይ ያለውን ተቃውሞ በተለያዩ መንገዶች እየገለፀና እያጠናከረ ይገኛል። ታዲያ አቶ ጌታቸው ረዳ ላለፉት ወራቶች ያወጣህው የፁሁፍ ቡቱቶና አሉባልታ በሰፊው የሚያብጠልጠው ወያኔን ሳይሆን ወያኔን በሚታገሉ ኢትዮጵያውያን ድርጅቶችና ግለሰቦች ላይ ነው። ይህ እንግዲህ አፍንጫ ሲመታ ዓይን ያለቅሳል እንደሚባለው ወያኔ ሲጠቃ የወያኔ ህመም አንተም ይሰማህ ይሆን ወይንስ ኢትዮጵያውያን ሊያሸንፋ ሲሆን ብርክ እየያዘህ ነው። በዚህ አካሄድህ ወያኔ ከፍተኛ ጥቅት ከደረሰበት የተቃዋሚ ቡልኮዎቻቸውን አሽቀንጥረው ጥለው ወያኔን እንደተቀላቀሉት ግለሰቦች ልትሆን እንደምትችል እንጠረጥራለን። አንተ የምታብጠለጥላቸው ኢትዮጵያውያን ግለሰቦችም ሆነ ኢትዮጵያውያን ድርጅቶች በፀረ ወያኔ አቋማቸው የማይጠረጠሩ ስለሆነ በድኅረ ወያኔ ኢትዮጵያ ከሌሎች ኢትዮጵያውያን ጋር በመሆን ለመጪው ኢትዮጵያ በጎ ሊያበረክቱ እንደሚችሉ ምንም አንጠራጠርም። በኢትዮጵያውያን ድርጅቶችና ግለሰቦች መሀከል የሀሳብ ልዮነቶች አሉ እነዚህ ልዮነቶች ግን የሀሳብ ልዮነቶች እንጂ አንተ በፅሁፍ ቡቱቶዎችህና አሉባልታዎችህ እንደምታሰራጨው ፀረ ኢትዮጵያ ሀሳቦች አይደሉም። አንተ ግን ፀረ ኢትዮጵያ ለመሆንህ ብዙ መረጃዎችንን እያየን ነው። በኢትዮጵያዎያን መካከል የጥላቻ መርዝ መርጨት ዋናው የፀረ ኢትዮጵያዊነት መገለጫ ነው። ወያኔንም እኮ አጥብቀን የምንጠላውና የምንቃወመው በዋንኛነት በኢትዮጵያውያኖች መካከል የጥላቻ መርዝ ስለሚረጭ ነው። የሀሳብ ልዮነትን በመርዝነት ሳይሆን ኢትዮጵያውያን ድርጅቶችንና ግለሰቦችን በማክበር ማንፀባረቅ ለኢትዮጵያውያን ትብብርና ለኢትዮጵያ ትንሳኤ ወሳኝ ናቸው።
አስተያየቶ ይጠቅማልና በሚከተለው ኢሜል አድራሻ ይላኩ። beweketuzeethiopia@gmail.com
———
በዚህ መጣጥፍ ላይ የቀረቡት ሃሳቦች የጸሃፊውን እንጂ የድረ ገጹን አቋም አያንጸባርቁም። ሃገራችን ኢትዮጵያ ስላለችበት ሁኔታ እና የመፍትሄ ሃሳቦች ላይ ምልከታ በአማርኛም ሆነ በእንግሊዝኛ ለማጋራት ከፈለጉ በሚከተለው አድራሻ ይላኩልን ፤ editor@borkena.com