ቦርከና
መጋቢት 2 2010 ዓ ም
ለሁለተኛ ጊዜ የካቲት 09/2010 ዓ. ም [February 16, 2018] የታወጀውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በአገሪቱ ላይ የጋረጣቸው ወቅታዊ ሁኔታዎችና የመፍትሄ ሃሳቦች።
የወያኔ/ኢህአዴግ (ከዚህ በመቀጠል የወያኔ)መንግስት ስልጣኑን በመሳሪያ በመታገዝ በ1983 ዓ. ም [1991] ከተቆጣጠረ ጀምሮ የስልጣኑን ዘመን ለማራዘም የተጭበረበሩ ምርጫዎችን በመጠቀም ራሱን ህዝብ የመረጠው መንግስት በማስመሰል አገሪትዋን በማመስ፣ ህዝቡን በማሸበርና በማሰቃየት ላይ ይገኛል። የወያኔ መንግስት ቁንጮዎች በትግራይ ህዝብ ክልል ተወክለናል በማለት አትወክሉንም የሚላቸውን ህዝብ በማሰር፣ በመግረፍና በማንገላታት ላይ ይገኛሉ። ባሳለፍናቸው ወራት በመላው የኢትዮጵያ ህዝብ የተደገፈና በተለይም በአማራና በኦሮሞ ወጣቶች የሚመራው ህዝባዊ ተቀነባበረ አመፅ የወያኔ/ኢህአዴግ መንግስት ስልጣኑን ባስቸኳይ እንዲለቅና ሁሉም የፖለቲካ እስረኞች ያለ ቅድመ ሁኔታዎች እንዲፈቱ በመጠየቅ ላይ ይገኛል።
የወያኔ መንግስት ሁኔታዎች አስገድደውት የተወሰኑ የፖለቲካ እስረኞችን ቢፈታም የወያኔ መንግስት ያለ ህዝብ ፈቃድ በመሳሪያ በመታገዝና በተጭበረበሩ ድምፆች የያዘውን ስልጣን በእውነተኛ ምርጫ ወይንም የሽግግር መንግስት በማቋቋም የኢትዮጵያ ህዝብ ለመረጣቸው ወገኖች ለማስረከብ ምንም አይነት ፍላጎትና አስተዋይነት አይታይበትም።
ይባስ ብሎ ለሁለተኛ ጊዜ የካቲት 09/2010 ዓ. ም [February 16, 2018] ለስድስት ወር የሚቆይ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አዉጅዏል። አዋጁ ከሚጥሳቸው መብቶች በጥቂቱ፦ ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ በቁጥጥር ስር ማዋል፣ ባልታወቀ ቦታ ማሰር፣ ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ በማናቸውም ሰዓት ብርበራ ማድረግ፣ በማንኛውም ሬድዮ፣ ቴሌቪዥን፣ ጽሁፍ ፣ ምስል ፣ ፎቶ ግራፍ፣ ቲያትርና ፊልም የሚተላለፉ መልዕክቶችን መቆጣጠርና መገደብ፤ ፅሁፍ ማዘጋጀት፣ ማተምና ማሰራጨት፣ ትእይንት ማሳየት፣ በምልክት መግለፅ ወይም መልእክትን በማናቸውም ሌላ መንገድ ለህዝብ ይፋ ማድረግ፤ ፍቃድ ሳይኖር ማንኛውንም ህትመት ወደ ሀገር ውሰጥ ማሰገባት ወይም ወደ ውጪ ሀገር መላክ፤ መልእክት በኢንተርኔት፣ በሞባይል፣ በፅሁፍ፣ በቴሌቭዥን፣ በቪድዮ፣ በማህበራዊ ሚድያ ወይም ሌሎች የግንኙነት ዘዴዎች መለዋወጥ ይገኙበታል። እንዲሁም ማንኛውም የሚጠረጠሩ ሰዎችንና ቡድኖችን እንቅስቃሴዎች መገደብና ማንኛውንም እርምጃ መውሰድ የሚሉት ይገኙበታል።
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተገን በማድረግ የወያኔ መንግስት በኮማንድ ፖስት ስም መላውን የኢትዮጵያ ህዝብ በተለይም በአማራና በኦሮምያ ክልሎች ነዋሪዎችን በማሰር፣ በመግረፍ፣ በመግደልና በማንገላታታ ላይ ይገኛል። ከትግራይ ክልል የመጡ የወያኔ መንግስት ቁንጮዎቹ የኢትዮጵያን ህዝብ ስልጣንና ሃብትን በግል ቁጥጥራቸው ስር በማድረግ በተለይም የኢትዮጵያ ማገርና ምሰሶ የሆኑትን የአማራና የኦሮሞ ህዝቦች በጠላትነት በመፈረጅ ኢ-ሰብአዊ ጥቃት እየፈፀሙባቸው ይገኛል።
የወያኔ መንግስት በኢትዮጵያ ህዝብ ለይ የሚፈፅመውን ኢ-ሰብአዊ ጥቃት ባስቸኳይ እንዲያቆም እንጠይቃለንን።
የወያኔ መንግስት በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ የሚፈፅመውን ግድያ፣ ማፈናቀል፣ መከፋፈል፣ ማጋጨት፣ ስቃይ፣ ሰቆቃ፣ እንግልት፣ ዘረፋ፣ በአገር ውስጥና ከአገር ውጭ ለስደት መዳረግ፣ ተንኮል የተሞላበት አካሄድ ባስቸኳዋይ መቆም እንዳለበት እንጠይቃለን።
የወያኔ መንግስት በግፍ የያዘውን ስልጣን ለሽግግር መንግስት እንዲያስረክብ እንጠይቃለን ።
የወያኔ መንግስት በኢትዮጵያ ህዝብ ለይ የሚፈፅመውን ኢ-ሰብአዊ ጥቃት የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ በዝምተኝነትና በቸልተኝነት እንዳያዩት እንጠይቃለን።
ጉተንበርግ ለኢትዮጵያ የወያኔ መንግስት በኢትዮጵያ ህዝብ ለይ የሚፈፅመው ግፍ ባጭሩ እንዲቀጭና የኢትዮጵያ ህዝብ ትግል እንዲሳካ ከተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ትብብርና ድጋፍ እንደሚያሰፈልገው ያምናል።
ኢትዮጵያ በልጆችዋ ታፍራና ተከብራ ለዘላለም ትኖራለች!
ጉተንበርግ ለኢትዮጵያ. መጋቢት 1 ቀን 2010 ዓ. ም.
Gothenburg for Ethiopia. 10 March, 2018