በሚካኤል አራጌ
መጋቢት 23 2010 ዓ ም
ከአንድ አውራጃ የመጡ ግለሰቦችን ሰብስበው < የዐማራ ድርጅት ነን> ይላሉ። ያለውን ጎስት(ባዶ) መዋቅር ተጠቅመው እነሱ ተሰብስበው ማድረግ የማይችሉትን የሚያደርግን በመስደብና ጎጣቸውን (አሳፋሪና ደረቅ አጭበርባሪዎቻቸውን ጨምሮ) ለመንዛትና ለማጀገን ይጠቀሙበታል።
< < ትክክለኛ ፣ ሁሉንም ዐማራ በተገቢው መንገድ ሊወክል የሚችል የዐማራ ትስስር ሊፈጠር የሚቻለው ውስጥ ለውስጥ በአውራጃ ተጠራርቶ የሚደረግ ውይይት አይደለም። ሁሉንም ዐማራ በተገቢው መንገድ ሊወክል የሚችል የዐማራ ድርጅት መፍጠር የሚቻለው የጎንዮሽ በመቆመር አይደለም። ሁሉንም ዐማራ በተገቢው መንገድ ሊወክል የሚችል የዐማራ ድርጅት መፍጠር የሚቻለው ከመላው የዐማራ ክልል ፣ አዲስ አበባና ሌሎች ዐማራበብዛት ካለበቸው አካባቢዎች የመጡ ፖለቲካው ላይ ጉልህና ተግባራዊ እንቅስቃሴ እያደረጉ ያሉ ሰዎች ያሉበት ተመጣጣኝ የአካባቢ ውክልና ያለው የዐማራ ካውንስል ሲመሰረት ፤ ይህንም ፅህፈት-ቤት ማዕከል ያደረገ ድርጅትና አካሄድ ሲኖር ብቻና ብቻ ነው። ማምጣት እምንፈልገውን ዲሞክራሲንም ከወዲሁ በትግል ባህልና በድርጅታዊ አካሄድ ማዳበር እንችላለን>> ቢባሉ አይሰሙም ።
ግንቦት ሰባት ደግሞ በህብረ ብሄርና በጋራ ጥቅም አኴያ ያለው ቁም ነገር ላይ ዘንገት ብሎ ፤ በፊናው ዳግማዊ ብአዴንን(፩ ዐማራን) መስርቶ እንሆ አስቀያሚ ቀልድ ቀልዷል። አሁንስ በጣም በዛ።
< ባለቤቱን ካልናቁ አጥሩን አይነቀንቁ> ይባላል።
የግንቦት ፯ አባላቶችን በዚህ —ዳግማዊ ብአዴንን(፩ ዐማራ)—ፍራንቻይዝ ምስረታ ላይ ማሰማራት ለምን አስፈለገ? ከድርጅቱ ጥሩ ህብረ ብሄርዊ ፕሮግራም ጋር የሚጣረስ አካሄድ አይደለምን?
አንድ ግልፅ የሆነ ፣ ቀዩን መስመርና የዐማራን የማንነት ሉአላዊነት የተላላፈ ፣ የድርጅት ስነ ስርዐትን፣ ስልትና ፕሮግራም የጣሰ አካሄድ አለ። ግንቦት ፯ የዐማራ ህዝብ ላይ ትልቅ ስህተት እየፈፀመ ነው። ህብረ ብሄራዊ ድርጅት ዐማራን ለመቆጣጠር ለምን እንደዚህ ያደርጋል?
በዚህ ጉዳይ ድርጅቱ መልስ ካልሰጠበት ፤ እራሱን የሚጎዳበት ጨዋታ ይሆናል ማ ለት ነው።
የአውሮፓና አሜሪካን ናሙና ካያችሁ ዐማራ በጣም ብዙ ምሁራኖች ያሉት ማህበረስብ ነው። ነገር ግን አብዛኛው ፖለቲካ ላይ ቸል ይላል። የዚህን ሃይል ፩% ማካተት ከተቻለ ፤ ለዐማራ ጤናማ በሆነ መልኩ መደራጀት ሰፊ በር ይከፍታል። በአማራ ላይ የሚሰራ ታዋቂ ድርጅት — ለምሳሌ ሞርሽ— ዋና ስራው መሆን ያለበት እነዚህን ግለሰቦች ማሰባሰብና ከተለያዩ አካባቢ የመጡ ዐማራዎች ያሉበት ድርጅት መመስረት ነው።
፩ ድርጅትን ድርጅት ከሚያስብሉት መሰራታዊ ገፀ ባህሪያቶች ውስጥ የህዝብ ተቀባይነት ፣ ስነስርዐት ፣ አካሄድ ፣ እቅድ ፣ አባላት ፣ መዋቅር ፣ አማካሪ ፣ ተግባራት፣ ግምገማ ፣ ስልት ፣ አጋር፣ ባላድርሻ አካላት ፣ ህዝብ ግንኙንት ፣ ጥናትና ምርምር ፣ ገንዘብ ፣ ደህንነት ፣ አክቲቪስትና ወዘተ አበይት ናቸው። ስለዚህም አክቲቪስት ብቻ የያዘ ድርጅት ፤ ድርጅት ሊሆን አይችልም። አባላት ብቻ የያዘ ድርጅት ፤ ድርጅት ሊሆን አይችልም። በአጠቃላይ ከጠቀስኴቸው አንድና ሁሉቱን ብቻ የያዘ ድርጅት ፤ ድርጅት ሊሆን አይችልም። በዚህም የመንደርደሪያ ሃሳብ ድርጅት ነኝ የሚል እራሱን መፈተሽ ያለበት ይመስለኛል። አለበለዚያ መጨረሺያው ተቧድኖ መገለልና(Marginal group) እብደት ነው ሊሆን የሚችለው ፤ ይህም በማህበራዊና ፖለቲካዊ ድርጅቶች ላይ በብዛት የሚታይ ንዑስ አደነጋገረ ቀውስ ነው። ተቧድኖ መገለል ባለበት ምህዳር ደግሞ ፅንፈኝነት(Radicalization) ይንሰራፋል። ተቧድኖ መገለል ባለበት ኑረት(Ecosystem) ላይ ደግሞ የፖለቲካና ማህበረሰብ ዋለታነት(Polarization) ይደራል። ተቧድኖ መገለል ባለበት ኑረት(Ecosystem) ደግም ለሌሎች ሃሳብና ትችት ዝግነት ይፈጥራል። ከህወሃት መራሹ ስርዐት ጋር ትንቅንቅ የገባነው የፀነፈና በራስ ፍላጎት ፣ ጥቅምና አስተሳሰብ ብቻ የተወሰነ የተገለለ ቡድን(Marginal group) አስተሳሰብን ለማስወገድ እንደሆነ ከቶ ሊዘነጋ አይገባም።
ድብብቆሽ ፣ ጠባብ ጎጠኝነትና በዐማራ ስም ማፌዝ ይብቃ ፤ ግልፅነት ፣ ተግባር ፣ ቅንነትና ብዘሃነት ይቅደም።
ለማንኛውም መልካም ሆሳዕና!
“The young man knows the rules, but the old man knows the exceptions.”
___
ማስታወሻ : በዚህ ጽሁፍ ላይ የተንጸባረቁ ሳሃቦች የጸሃፊውን እንጂ የድረገጹን አቋም አያንጸባርቁም። ነጻ አስተያየት ወይንም ሃሳብ በዚህ ድረ ገጽ ለማውጣት ጽሁፍዎትን በሚከተለው አድራሻ ይላኩልን editor@borkena.com ወይንም በ info@borkena.com