spot_img
Wednesday, November 29, 2023
Homeነፃ አስተያየትህልም የመሰለኝ እምዬ አንዳርጋቸው ፅጌ (በመስከረም አበራ)

ህልም የመሰለኝ እምዬ አንዳርጋቸው ፅጌ (በመስከረም አበራ)

advertisement

ግንቦት 28 2010 ዓ.ም.

አንዳርጋቸው ፅጌ ከገዘፉት ገዝፎ የሚታየኝ ፖለቲከኛ ነው -በመፅሃፉ እያዳንዱ መስመር ሳልፍ አንድ ደረጃ ከፍ እያለብኝ እየራቀኝ የሚሄድ ምጡቅ፡፡ግጥም ልፃፍ ሲልም በእያንዳዱ ስንኝ ውስጥ ቢፈቱት የሚረዝም እምቅ እውቀት ለማስታቀፍ የሚያጥረው የለም፡፡ንባብ ገንዘቡ ነው፡፡ አንባቢነቱ በንግግሩም ሆነ በፅሁፉ ውስጥ ጎልቶ ይታያል፡፡የነፍሱ መስህብ ሃያል ነው፡፡ ከክርክሩ ማምለጫ ቀዳዳ የለም፡፡ ማለት የፈለገውን ሲል አንባቢን በምክንያት ገመድ ጎትቶ ወደ ራሱ ያስጠጋል፡፡ የፃፈ የተናገረውን እንደ ቡና ብደጋግም አይሰለቸኝም፡፡ደጋግሜ ባነበብኩት መፅሃፉ እና በማያልፉኝ ቃለ-ምልልሶቹ ውስጥ አሰላስለዋለሁ እንጅ በአይኔ አየዋለሁ ብየ አስቤ አላውቅም፡፡መታሰሩን ስሰማ ሃገር ኦና የቀረች መስሎ ተሰማኝ፡፡ እስር ቤት መከርቼሙ ብክነት መሰለኝ፡፡ ችግር መፍትሄን ሲያስር የሃገሬ ነገር እንደማይሆን ሆኖ እንደተተበተበ ታወቀኝ፡፡ ከሁሉ በላይ የተያዘበት መንገድ አንገበገበኝ፡፡

ክፉ ቀን እና ክፉ ሰዎች ገጥመው እስርቤት ከከረቼሙት ቀን በኋላ አንዳርጋቸው ፅጌን አየዋለሁ ብየ አስቤ አላውቅም፡፡የመፈታቱን ዜና ዋዜማ ሬዲዮ ከዘገበ ቀን ጀምሮ በመፈታቱ ላይ እምነት ጣልኩ-መቼ ይፈታል የሚለው ቀላል ጥያቄ እንዳ ሆኖ፡፡ ለእኔ ከባድ ምጥ የነበረው በጤና እና በስነ-ልቦና እንዴት ያለ አቋም ላይ ይሆን? የሚለው ነገር ነበር፡፡ አንዳርጋቸው ከሆነበት መከራ የተነሳ “ትግል በቃኝ” እንዳይል የሚለው መጥፎ ስጋት ሽው ይለኝ ነበር፡፡ አንዳርጋቸው ፅጌ የሌለበት ትግል ደግሞ መስህብ ይጎድለዋል፡፡ይህን እያሰላሰልኩ፣ ዋዜማ የዘገበው ዜና መላዕክት ፅፈው የላኩት እስኪመስለኝ አምኜው እሁድ በሌሊት ወደ አዲስ አባባ በረርኩ፡፡ እስከ ሰኞ የአቀባበሉ ሸብ ረብ ላይ ማተኮርን መረጥኩ፡፡

ሰኞ ግንቦት ሃያ እንደሚፈታ ለህወሃት ቅርብ የሆኑ አንድ አይሉ ሁለት ሰዎች ነግረውኛል፡፡ አንዱ ግን ማክሰኞም ሊሆን እንደሚችል ከእዛ ግን እንደማያልፍ አስረግጦ ሲነግረኝ የአንዳርጋቸው ፍች አሳስቦት ሳይሆን ለእኔ ብሎ እንደሆነ አበክሮ ነገረኝ፡፡ አመስግኜ ማክሰኞ ላይ አተኮርኩ፡፡ ነገር ግን ሰኞ ሌሊት ከመጣም በሚል ሌሊቱንም ስንጓጓ አደርን፤ምንም የለም፡፡ ማክሰኞ እየተጎተተ መጣ፤እየተጎተተ ረፈደ፤ እየተሳበ ሊመሻሽ ቃጣው፡፡ ዝናቡ መጣሁ መጣሁ ማለት ጀመረ፡፡ አንዲ ግን የለም! ብስጭት ጀመረን፡፡ ጩኽት ሁሉ የሞከረው ነበረ፡፡ ጀግናችን በዘገየ ቁጥር የጠባቂው ጉጉ ህዝብ ቁጥር እየጨመረ ሄደ፡፡ያለፈ ያገደመው መኪና ላይ ሁሉ ማፍጠጥ ሆነ፡፡

በስተመጨረሻው አንድ አልባሌ አሮጌ አንቡላንስ በሚጎተት ፍጥነት መጣች፡፡በበኩሌ ህመምተኛ ቤቱ አድርሳ የምትለስ ነበር የመሰለኝ እንጅ የጥበቃችንን መልስ፣ የህመማችንን ፈውስ ይዛ የመጣች አድርጌ አላሰብኩም፡፡ከወደ ሁዋላየ ቆመ አንድ ሰው “ይሄ ይሆን እንዴ?” ከማለቱ መኪናዋ ፍጥነቷን ጨምራ ወደ አቶ ፅጌ ቤት ፈትለክ ስትል ሰው በሰው ላይ እየተነባበረ ተሯሯጠ፡፡ እኔ እግሬ ከዳኝ፡፡ እንደምንም እግሮቼን ሰብስቤ መኪናዋን ተከተልኩ፡፡ መኪናው ጋ ስደርስ ገቢና የተቀመጠው ነጭ ለባሽ ደህንነት እና ሾፌሩ ብቻ ናቸው፤አንዳርጋቸው ከኋላ ነው፡፡ መኪናውን የከበበውን ሰው ብዛት ሲያይ አመልጣለሁ ብሎ መፈትለኩ ከመወረር እንዳላተረፈው ሲያውቅ በድንጋጤ የሚጨብጠው ጠፋበት፡፡ አስሬ ስልክ ይደውላል፣በብስጭት እና በክርክር ሁኔታ ያወራል፣ስልኩን ዘግቶ ወደ ውጭ ሲያይ እያደር በሚጨምር ሰው ተወሯል፡፡ አንዳርጋቸውን ከመኪና ማውረድ ትልቅ ፈተና ሆነበት፡፡ አኛ ደግሞ አንዳርጋቸውን ለማየት ሰባት አመት እንደቆየው አይነስውር ትዕግስት አጣን፡፡ በስተኋላ በኩል የመኪናው መስታውት ላይ ያለውን ዝናብ ጠራርጌ ወደ ውስጥ ለማየት ተንጠራራሁ፡፡ መስታውቱ በጥቁር ቀለም ስለተደፈነ ከኋላ የተቀመጠውን ናፍቆታችንን ማየት አልቻኩም፡፡

የግፊያ እርግጫው ነገር አይወራ፡፡ ዝናቡ ትዕግስቱ አልቆ የያዘውን ውሃ እላያችን ላይ ዘረገፈው፡፡ አቶ ደህንነት በር ለመክፈት የሚሆን ቦታ እስኪያጣ ድረስ ፍቅር ብቻ ስቦ ባመጣው የአንዲ ሰራዊት ተከበበ፡፡ “አባቱን ጥሩልኝ ለአባቱ ነው የማስረክበው” አለ:: አቶ ፅጌ በዛ ሁሉ ህዝብ መሃል ቀጭን መንገድ ተከፍታላቸው መምጣት ጀመሩ፡፡ ሆኖም ግፊያው አስፈሪ ስለነበረ አንዲን በእጃቸው መስጠት አልተቻለም፡፡እሳቸው ከተመለሱ በኋላ የባሰ ግፊያ ሆነ፡፡ ግራ የገባው አድራሽ ደህንነት “በቃ እምቢ ካላችሁ ይዤው እመለሳለሁ” አለ፡፡ “ትመለሳለህ? ደም ይፈሳታላ!” አለ ከመሃላችን አንዱ አይኑን አፍጥጦ፡፡

እንደምንም ተገፍትረን የኋላ በር ተከፍቶ አንዳርጋቸው ብቅ ሲል እንደ ትንሽ ልጅ አፈፍ አድርጎ ትክሻው ላይ ያደረገው ልጅ ብቅ ሲል አይኔ የመገረም ፈገግታ ፈገግ ካለው አንዳርጋቸው ፅጌ ፊት ላይ ተሰካ፡፡ አይኔን በዙሪያው በሚራኮተው ሰው ከተከበበው ከአንዳርጋቸው ላይ ነቅየ ወደ ታላቁ አምላክ መንበር ወደ ሰማይ አነሳሁ!! የአንዳርጋቸው ፈገግታ ትርጉም ያለው፣አፍ አውጥቶ የሚናገር አይነት ነበር፡፡ በፈገግታው ውስጥ ህክምና አየሁ! ያችን ሰዓት በአይኔ ከማየት ስላልጎደልኩ ደስ አለኝ፡፡

አንዳርጋቸው ግርግር የሚወድ፣ጭብጨባ ሞተር ሆኖ የሚነዳው ሰው እንዳልሆነ አውቃለሁ፡፡ ሆኖም ከመኪና ሲወርድ፣አፈፍ ተደርጎ ትክሻ ላይ ሲደረግ በወገን መሃል የመሆን ፍቅር የሚያመጣው፣የአላማ ተጋሪ የማግኘት መፅናናት የወለደው ፈገግታ አየሁ! ማመን እና አለማመን በሚታገሏት ነፍሴ ውስጥ የአንዳርጋቸው መንፈስ ሲታከም አስተዋልኩ፡፡ ህልም መሰለኝ፡፡

ሆኖም የአንዳርጋቸው ስጋ ከስቶ ጎስቁሎ ሳይ የሆነ የሃገር መርገም ታየኝ፡፡ ይህንኑ መርገም አንዱአለም አራጌ እና እስክንድር ነጋ ፊት ላይ አይቻለሁ፡፡ እነዚህ ሰዎች እጣ ወድቆባቸው የሃገር ምጥ ያምጣልሉ፡፡ ወደው ‘የሃገር መርገም በእኔ ላይ ይሁን’ ብለው የፖለቲካችንን ህማም ይቀበላሉ፡፡አንዳርጋቸውን ሳየው ልክ ባልሆነ ሁኔታ የሃገር መርገም በትቂቶች ላይ ብቻ ወድቆ ሌሎቻችን ለቅሶ ቤት የምንዘፍን ዓለመኞች እንደሆንን ተሰማኝ፡፡ ልስላሴያችን፣ምቾታችን ሁሉ የነሱን ያህል ትልቅ ነፍስ ከማጣታችን የመጣ መስሎ ተሰማኝ፡፡ ከማየው አንዳርጋቸው ፅጌ በተጨማሪ፣አንዱዓለም አራጌ፣እስክንድር ነጋ ፊቴ ላይ ድቅን አሉ፡፡የበታችነት ተሰማኝ፡፡ታላቅነታቸው ጎላብኝ፡፡ በአንፃሩ ሸክም ያለመጋራት ሃፍረት ነገር ወረረኝ፡፡

የሆነ ሆኖ አንዳርጋቸውን ከእስር ተፈቶ ሳየው ሃገሬ የተፈታች መሰለኝ፡፡ ፅናቱ ገረመኝ፡፡ (በነገራን ላይ አንዳርጋቸውን ነፃ ያወጣው የራሱ ፅናት ነው፡፡ ከዚህ ላይ ሸርፈን ለራሳችን የምንወስደው ፀጋ የለም! ሲኦል ደርሶ እስኪመለስ የፀና ሰው ‘ያስፈታሁት እኔ ነኝ፣ የእኔ ዘር እንዲህ ስላደረገ ነው’ ማለት ይሉኝታ ቢስነት ነው፡፡)እንደምንም ተጋፍቼ፣ “የት አለች?” በሚሉ ወዳጆቼ ፍለጋ ታግዤ አጠገቡ ደረስኩ:: የማደርገው ጠፋኝ፤ደመ-ነፍሴ የመራኝን ካደረግኩ በኋላ አጠገቡ ተቀመጥኩ፡፡ የጤንነቱን ነገር ጠየቅኩት “ደህና ነኝ” አለኝ ፈገግ ብሎ፡፡ በፈገግታው አልፌ በከሳ ፊቱ ውስጥ ያለችውን የምንወዳትን ወፍራም ነፍሱን አየኋት፡፡ ደስ አለኝ!!!! አጠገቡ አንገቴን ደፍቼ እንደተቀመጥኩ አንድ አባት መጥተው “እንዴት ነው ሞራልህ? እሱ ነበር ያሳሰበን ገላ ይመለሳል” ሲሉት ፈገግ ብሎ እያያቸው “እንዲህ በቀላሉ” ሲል ልቤ በደስታ ዘለለች፤ አንዲ ያልተቀነሰበት የሃገሬ ፖለቲካ ውበቱ ታየኝ- ሰማይ ሙሉ ደስታ!!!!!! የአራት አመት የእግር እሳት በአንድ ቀን ደስታ ሲሸነፍ ሳይ የመልካም ነገር ጉልበቱ ታወቀኝ፡፡

እውነት ለመናገር የአንዳርጋቸው ፅጌ መታሰር የማልፈልገውን አይነት ማንነት እንዲቆራኘኝ አድርጓል፣ብዕሬን ቁጡ ስሜቴን ስስ አድርጎት ኖሯል፡፡ አንዳርጋቸው ፅጌ ከመታሰሩ በፊት ወደ ሁለት አመት ገደማ በፕሬስ ሚዲያው ላይ በአምደኝነት እሳተፍ ነበር፡፡ በተቻለ መጠን የግል ስሜቴን ገትቼ የታየኝን እና ከስሜት ይልቅ ምክንያት የበዛበት የመሰለኝ ነገር ለመጠቆም እሞክር ነበር፡፡ገዥዎች የሚያደርጉት ነገር ከስሜታዊነትም በላይ የሚያሳብድ ነገር እንደማያጣው ባውቅም መሰዳደቡ፣ስሜታዊነቱ፣አለመከባበሩ፣እንደ ጠላት መተያየቱ፣ በምንጠላው የገዥዎች መንገድ መሄድ ነው፡፡ የሚያመጣልን ነገር አልታይ ስለሚለኝ በተለይ ብዕር ሳነሳ ንዴቴን ዋጥ አድርጌ ራሴን ለመግዛት እሞክር ነበር፡፡ይህ በገዥዎች ዘንድ ሳይቀር በበጎ ይታይ እንደነበር ቅርበት ያላቸው ወገኖች ይነግሩኝ ነበር፡፡

አንዳርጋቸው ፅጌ መያዙን ከሰማሁባት እርጉም ቅፅበት ጀምሮ ግን ውስጤን ቂመኝነት ሞላው፡፡ የገዥዎችን ስህተት ከዚህ ቀደም ከምረዳው በተለየ መረዳት ጀመርኩ፡፡ ቀደም ሲል የገዥዎች ስህተት ሁሉ በብዛት ካለማወቅ፣ በትቂት ከራስ ወዳድነት እና የአለማወቅ ውላጅ ከሆነው ዘረኝነት የሚመነጭ በመሆኑ በጊዜ ሂደት ከልምድ እና ከእውቀት ሊስተካከል ይችላል የሚል እምነት ነበረኝ፡፡ለዚሁም ነው የበኩሌን ለማለት ወደ ሚዲያው የወጣሁት፡፡ አንዳርጋቸውን ለመያዝ የተኬደውን ርቀት፣ የተከፈለውን ዋጋ ፣የተሴረውን ሴራ ትብትብ ሳይ ነገሩ ተራ አለማወቅ ሳይሆን አውቆ የሃገር አለኝታ የማጥፋት አደገኛ እና ክፉ አካሄድ እንደሆነ ገባኝ፡፡ሳልፈልግ ጥላቻ ቋጠርኩ፡፡ሳልወድ ንዴታም ሆንኩ፡፡ንዴትና ቁጭት አብሮኝ የሚጓዝ፣ከዚህ መንግስት ጋር የወገነ ሁሉ የሚያንገሸግሸኝ ፣ንግግራቸውን ባልሰማ፣አይናቸውን ባላይ የምመርጥ ፅንፈኛ ሆኘ ቁጭ አልኩ! ይህን ስሜቴን አልወደውም፤ አንዲ ሲፈታ እኔም ከዚህ ስሜት በመፈታቴ ደስ ብሎኛል፡፡

አጠገቡ እንደተቀመጥኩ ነኝ፡፡ ከአክብሮቴ ብዛት ቃላት ከአፌ መውጣት አቅቷቸዋል፡፡ ዝም ብየ እሱን መስማት አሰኘኝ፡፡አንድ ቤተሰብ የሆነ ሰው መጥቶ አባቱን በደንብ ማግኘት እንዳለበት ይነግረዋል እሱ ደግሞ ውጭ ያለውን ሰው ወጥቶ ሰላም ማለት እንዳለበት አጥብቆ ይወተውታል፡፡ቤት የገባው በትልቅ ግፊያ በሰው ሸክም ነው፡፡ ነገሩን የምናስተባብር ሰዎች ሁሉ ነገር ከቁጥጥራችን ውጭ ሲሆን ደህንነቱ በጣም አሳሰበንና ነገሩ እስኪረጋጋ ድረስ ቤት አስገብተን በሩን መዝጋቱን መረጥን፡፡ እሱ ግን አልፈለገም ወጥቶ ማናገር ፈለገ፤ “ለህዝብ አስቡ እንጅ ዝናብ ላይ ቆሞ እንዴት እኔ ቤት እቀመጣለሁ፤ አመስግኜ ልሸኝ አስወጡኝ” አለ፡፡ ይዘነው ስንዎጣ “ካልተረጋጋችሁ አይወጣም” ብለን አስፈራርትን ወደኋላ የመለስነው ህዝብ እሱን ይዘን እስክንወጣ በር ላይ ደርሶ ጠበቀን፡፡የጠጠር መጣያ የለም፡፡ ብቅ ሲል “እጅህን ብቻ” የሚል ድምፅ ሲሰማ በእኛ ላይ ተንጠራርቶ እጁን ሰደደ አንዱ ሲለቅ አንዱ እየያዘ ጎትተው መሃቸወ ሊከቱት ሲሆን በማንኛውም ሰዓት የሚያሳስበን ደህንነቱ ወደቤት መልሰን እንድንወስደው ግድ አለ፡፡ ተመልሶ መግባቱን ያየ ሰው ራሱ ወደኋላ ሆኖ መውጫውን አመቻቸልን፡፡ ወጥቶ አመሰገነ፣የማይሰበር መንፈሱን ያስመሰከረ ንግግር አደረገ፣ እንዲህ ያለ አቀባበል እንዳልጠበቀ ተናገረ፡፡ “ይገባሃል ያንስሃል እንወድሃለን አንዲ የእኛ” የሚል ጩኽት አቋረጠው፡፡ “እንደምትወዱኝማ አየሁ” ሲል መለሰ፡፡

ተናግሮ ሲጨርስ ልብስ እንዲቀይር ወደ ውስጥ ሲገባ ውጭው በጭፈራ ጦፈ! ለወትሮው ጭፈራ ብዙም የሚያስደስተኝ ባልሆንም በዝናብ ውስጥ ሆኖ የሚጨፍረው የሃገሬ ሰው ድምፅ ለአንዳርጋቸው የመንፈስ ምግብ ስለመሰለኝ ካለሁበት ሆኜ በልቤ አብሬ ጨፈርኩ፡፡ልብሱን ለብሶ ሲወጣ ህዝቡን ፊት ለፊት ማግኘት በመፈለጉ እኛ ደግሞ ደህንነቱ ስላሳሰበን እንዴት አድርገን እንደምናጣጥም ስናስብ “የፎቁ ሰገነት ላይ እናድርገው” የሚል የተባረከ ሃሳብ ከአንዱ የኮሚቴ አባል ተነሳ፡፡ ወደዛው ተጣደፍን፡፡

እንደሚገባው ከፍ ብሎ ቆሞ የሃገሩን ህዝብ ፍቅር በገሃድ ተመለከተ፤ጭብጨባ ሆነ፣ጭፈራው ደራ፣መሬቷ ጠበበች፡፡ የእሱ ስሜት ግን ያው የረጋ ነው፡፡ ወደ ቁምነገሩ ገባ፣ ሃገር ነፃ እስክትወጣ ድረስ ትግሉን እንደማያቆም ተናገረ፣እስር ቤት እያለ ተቆርጦ የተጣለውን ንግግሩን በህዝብ ፊት ተናገረ፡፡ እኔ እንደተያዝኩ “ልቀቁኝ ብየ አልለምናችሁም የፈረዳችሁብኝን የሞት ፍርድ ተግብሩት፣ለህዝብ እየሳቁ መሞትን አሳያችኋለሁ፤ለእኔም እንዲህ ባለ ሃገር ከምኖር ሞቴ ይሻለኛል” ብየ ነበር ሲል መቀስ የቆረጠውን ጣፋጭ እውነት ለህዝቡ ተናገረ፡፡ ቀጠለ “አሁን ባሳሪዎቻችን ፊት የማናወራው ብዙ ነገር አለ፡፡ እኔን መውደድ ብቻ ትግል አይሆንም ሃገር አስሮ የያዘውን መከራ ምክንያት ማጥፋቱ ላይ ነው ማተኮር ያለባችሁ” ሲል እስትንፋሱ እስካለች ድረስ ለህዝብ ከማሰብ፣ለሃገሩ ፖለቲካ ፈውስ ከመልፋት እንደማይመለስ የሚያስመሰክር ንግግር አደረገ፡፡ ህዝቡ በደስታ ሰከረ፡፡ እኔም አምላኬን አመሰገንኩ፡፡ አንዳርጋቸው ያለበት ፖለቲካ ጣዕሙ ታየኝ…….!

ወደ ልጆቹ ሊበር ሰዓታት ሲቀሩት የአቀባበል ኮሚቴ አባቱን ለአስራ አምስት ደቂቃ አግኝቶን ነበር፡፡ በበኩሌ ብዙ ቁም-ነገር ጨብጫለሁ፣ከጎኔ የተቀመጠው ወንድሜ ዳንኤል ሽበሽ ከመጠጋት በላይ ተጠግቶ ሲሰማው አስተውያለሁ፡፡ሆኖም በንግግሩ መሃል ታጋይ አርበኛ መሳፍንትን(ገብርዬ) አንስቶ መናገር ሲጀምር ከሃዘን፣ቁጭት እና ንዴት አልፎ እንባ ሊታገለው ሞከረ፡፡ “እንዴት እኔን አምኖ ትግሉን የተቀላቀለ ልጅ መሰላችሁ?” ብሎ ስሜቱን ዋጥ አድርጎ ወደ ሌላ ጉዳይ ገባ፡፡ ሆኖም ሃዘን ቁጭቱ ተለይቶን እስኪወጣ ድረስ አብሮት እንደነበረ አስተዋልኩ፡፡ የመታመን እዳ ለሚያንገበግበው፣ለተጨማሪ ደቂቃ አብረውት በተቀመጡ ቁጥር ለሚማርክ፣ቢናገሩለት ለማያሳፍር ሰው መቆም የሆነ ስሜት አለው- ኩራት ኩራት የሚል !

በመስከረም አበራ
meskiduye99@gmail.com

- Advertisement -Early Bird Holiday Deals! Before you know it, the holidays will be right around the corner! Take advantage of our early bird deals today and save up to $40 on our fees with code SPOT40!
Stay Connected
28,789FansLike
13,920FollowersFollow
8,540SubscribersSubscribe
Stacy Adams
Must Read
Related News

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here