spot_img
Tuesday, November 28, 2023
Homeነፃ አስተያየትሆድ ያባውን ሰልፍ ያወጣዋል (በመስከረም አበራ)

ሆድ ያባውን ሰልፍ ያወጣዋል (በመስከረም አበራ)

advertisement

(በመስከረም አበራ)
ሃምሌ 3 ፤ 2010 ዓ.ም

ሃገር እንድትኖረው ሚፈልግ ኢትዮጵያዊ ሁሉ የዶ/ር አብይን ወደ ስልጣን መምጣት ወዶታል ብቻ ብሎ ማለፍ ያስቸግራል፡፡ሰውየው ፈጣሪ ኢትዮጵያን ሊታደግ የተጠቀመበት መለኮታዊ ወኪል አድርጎ የሚወስድም አይጠፋም፡፡የቀድሞ ካድሬነቱም ሆነ የመጣበት ዘውግ ለአብዛኛው ኢትዮጵያዊ ጉዳዩ አይደለም፡፡ጉዳዩ ያለው ይዞት ከመጣው ሃገራዊ አንድነትን የማጉላት ወቅታዊ፣ሁነኛ፣አሸናፊ እና ብዙ ርቀት ተጓዥ ሃሳብ ጋር ነው፡፡ይህ ሃሳብ ራሱ ሰውየው በኦሮሞነታቸው በኩል አልፈው የኢትዮጵያ ጠ/ሚ ከመሆናቸው ጋር ግጭት እንዳለው ተረስቶ አይደለም፡፡ወጣም ወረደ የዶ/ር አብይ መምጣት ብዙ ኢትዮጵያዊን አስደስቷል፡፡በዚህም ሰበብ የድጋፍ ሰልፎች እየተደረጉ ነው፡፡ በድጋፍ ሰልፎቹ መራሄ የአዲስ አበባው ሰልፍ ላይ የተወረወረው ቦምብ ያመጣው ህዝባዊ ቁጣ በሌሎች ከተሞችም የድጋፍ ሰልፉ እንዲጧጧፍ ሳያደርግ አልቀረም፡፡እየተመናመነ ከመጣው አክራሪ የኦሮሞ ብሄርተኞች ካምፕ ዘንድ ውግዝ የበዛበት የባህርዳሩ ሰልፍ የዚሁ የድጋፍ ሰልፍ አካል ነው፡፡

የባህርዳሩን ሰልፍ በትዊተር ገፁ ለመተቼት የፈጠነው ዶ/ር አወል ቃሲም ነው፡፡ “Today’s Bahir Dar rally, healed to support the PM Abiye ‘s reform is more rejection of plurality and diversity than anything else. If this is a really peoples idea of “Medemer”, we have a good problem. There is no glorious past to return to. We have to imagine a new future”. ይህን መፃፉን ተከትሎ የተሰጡትን አስተያየቶች ተከትሎ ደግሞ በፌስ ቡክ ገፁ “Bahir Dar’s Rally,Abiye Ahmed’s Medemer and the Endless Fascination by the past” በሚል ርዕስ ስር ሰፋ ያለ ሃተታ በእንግሊዝኛ ቋንቋ አስፍሯል፡፡ ከዚህኛው ፅሁፉ ውስጥ ለወደፊቱ የሃገራዊ አብሮነታችን ሲባል መፍታታት አለባቸው ብየ የማስባቸውን ክርክሮች እንዲህ ለይቼ አውጥቻቸዋለሁ፡፡

“When Abiye Ahmed comes up with the now famous notion of “medemer”, I thought and hoped that this would be …. an opportunity for us to build a new political community that is not hostage to the historically and culturally defended ideologically ….I thought this would be a moment of to break out of the old ways of being together , to build egalitarian consensuses underpinned by democratic values of equality and liberty. …I hoped a new vision of being together, caring for each other, of solidarity, and inter-ethnic and inter religious coexistence is on horizon. I was wrong…. “Isrilites built Egyptian pyramids, God is the same as Allah, Repeated citation of Jesus Christ, Noha” and more that characterized the some of the speeches and the general environment [of the Bahir Dar Rally]. That is not pluralism. ……..The massive display of the flag, beyond being a total in difference to the effects it has on those marginalized under it; it takes on a form of contempt to this whole idea of change and “medemer”. Many of us do not simply recognize ourselves in this symbol. I am not sure that to what extent those in the unity camp are aware of the views and conversations in other political circles, especially in ethno-national political spheres especially such as of the oromo, Somali, Gambella,Afar, and sidama”

“ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ መደመር የሚለውን ሃሳብ ይዘው ሲመጡ በታሪካዊው እና ባህላዊው አንድ ወጥ እሳቤ ያልታገተ አዲስ የፖለቲካ ማህበረሰብ ለመፍጠር ጥሩ አጋጣሚን ይዞ ይመጣል የሚል ግምት እና ተስፋ ነበረኝ…….ይህ ከአሮጌው የአብሮነት ዘይቤ ሰብረን የምንወጣበት አፍታ እንደ ነፃነት እና እኩልነት ባሉ ዲሞክራሲያዊ እሴቶች ላይ የቆመ እና የፀና አብሮነት የሚመጣበት መስሎኝ ነበር……..የአብሮነት፣የመተሳሰብ፣የወንድማማችነት፣በሃይማኖቶች/ብሄረሰቦች አብሮ የመኖር አዲስ እይታ እንደሚመጣ ተስፋ አድርጌ ነበር…..ተሳስቼ ነበር!….. የግብፅን ፒራሚድ የሰሩት እስራኤላዊያን ናቸው፣እግዚአብሄር እና አላህ ተመሳሳይ ናቸው የሚለው እና በተደጋጋሚ የኢየሱስን እና የኖህን ስም የሚጠራው የተናጋሪዎች ንግግር እና በአጠቃላይ የሰልፉ [ባህርዳሩ] ከባቢ ብዝሃነትን የሚያሳይ አልነበረም…… ረዥም ሰንደቅ አላማ ማሳየቱ በባንዲረው ምልክትነት የተገለሉ ሰዎች ለሚሰማቸው ስሜት ግዴለሽ መሆን ፤መደመር ለሚለው ሃሳብም ንቀት ነው….. ብዙዎቻችን በዚህ ሰንደቅ የመወከል ስሜት የለንም፡፡ የአንድነት አቀንቃኞች በኦሮሞ፣ሶማሌ፣ጋምቤላ፣አፋር ሲዳማ እና ሌሎች የብሄር ፖለቲካ አራማጆች ዘንድ ስላለው ፖለቲካዊ አመለካከት ምን ያህል ትክክለኛ መረዳት እንዳላቸው እርግጠኛ አይደለሁም”::
በእነዚህ ሃሳቦች ላይ የተሰማኝን ለማለት ጊዜ የወሰድኩት ሃሳቡ በዶ/ር አወል ቃሲም በኩል ቢነሳም ሌላ ተጋሪም የማያጣ፣ብንነጋገርበት ብዙ የሚፈቱ ሃሳቦችን የያዘ፣ከመነጋገራችን ደግሞ የምንጠቀምበት መስሎ ስለተሰማኝ ነው፡፡ ከላይ ያስቀመጥኩት ወንድሜ ዶ/ር አወል ቃሲም በትዊተር ገፁ ያስቀመጣት አጭር ሃሳብ በኋላ በፌስ ቡክ ገፁ ሰፋ አድርጎ ያስቀመጠውን ሃሳብ ጨመቅ አድርጋ የያዘች ሃሳብ ነች፡፡ የሁለቱም ሃሳቡ ሲጠቃለል ደግሞ የባህርዳሩ ሰልፍ ለዶ/ር አወል የሃይማኖትን እና የዘውግን ብዝሃነት ሊጨፈልቅ የተነሳ፣መደመር የሚለውን ሃሳብ በመጨፍለቅ በሚለው የተካ፣ ለወደፊቱ አብሮነት አደጋ አዝሎ የመጣ፣አሮጌውን የአብሮነት መልሶ ለማምጣት የታሰበ ሁነት ሆኖ ታይቶታል፡፡ በዚህም ምክንያት በዶ/ር አብይ የመደመር ፖለቲካዊ ላይ የነበረው ተስፋ ተሟጧል ብቻ ሳይሆን በፊት ተስፋ ማድረጉም ስህተት እንደነበር ከትቧል፡፡ለዚህ ከባድ ተስፋ መቁርጥ ያበቃው ደግሞ ወ/ሮ እማዋይሽ እና ጀነራል አሳምነው ፅጌ መፅሃፍ ቅዱሳዊ ሃሳቦች በንግግራቸው መሃል ማንሳታቸው እና አላህን ከኢየሱስ መሳ አድርገው መናገራቸው ነው፡፡ ይህ ነገር በባህርዳር ከተማ ከታየው የ500 ሜትር እርዝመት ካለው ባንዲራ ጋርም ተዛምዶ እንዳለው “ባንዲራው ሃገራዊ ብቻ ሳይሆን ሃይማኖታዊ ምልክትነት አያጣውም፤ነገር ግን እኔ ያዘው እስካልተባልኩ ድረስ ችግር የለብኝም” ሲል ረዘም ባለው የፌስቡክ ፅሁፉ ላይ ጠቅሷል፡፡ ወደኋላ ተመልሰን ልናመሰግነውም ሆነ ልንመልሰው የሚገባ ምንም በጎ ነገር እንደሌለ ነው ዶ/ር አወል የሚያስቀምጠው፡፡

ባህርዳርን ምን ልዩ አደረጋት?

ሁሉም ሰው እንደሚያውቀው የባህርዳሩ የድጋፍ ሰልፍ የአዲስ አበባውን ሰልፍ የተከተለ ነው፡፡ በባህርዳር የተያዘው ባንዲራም አዲስ አበባ ከተያዘው ልሙጡ ባንዲራ የተለየ ነገር ያለው በእርዝመቱ ብቻ ነው፡፡እርዝመቱ ደግሞ ያን ያህል የሚያነጋግር ነገር ያለው አይመስለኝም፡፡ቁምነገሩ የወከለው ነገር ነው፡፡ ይህ ባንዲራ ዶ/ር አወል ሃይማኖታዊ እና ዘውጋዊ ብዝሃነትን የመጨፍለቅ ምልክት አለው ሲል ያልገቡኝ ነጥቦች አሉ፡፡ የመጀመሪያው ይህ ባንዲራ የጭፍለቃ ምትሃቱ የሚወጣው ባህርዳር ላይ ሲውለበለብ ብቻ ነው ወይ? አዲስ አበባ ላይ ሲውለበለብ ዶ/ር አወል ለምን ተመሳሳይ ሃሳብ አላነሳም? ለሁለት ተመሳሳይ ነገሮች ተመሳሳይ ምላሽ ካልተሰጠ ችግር አለ ማለት ነው፡፡ ችግሩ ያለው ደግሞ ባንዲራውን ይዞ ከወጣው ህዝብ እንጅ ከባዲራውም ሆነ ከምልክትነቱ ጋር አይደለም፡፡ ይህ ባይሆን ኖሮ ቢያስ ካህርዳር በፊት አዲስ አበባ ላይ ይህ ባንዲራ ሲታይ እንዲህ አይነት ትችቶችን መስማት ነበረብን፡፡ ከባህር ዳር በኋላ በደቡብ ከተሞች የአንበሳ ምልክት ያለው ባንዲራ ሳይቀር ተይዞ ታይቷል፤ ዶ/ር አወልም ሆነ ሌሎች መሰል ተችዎች ምንም አላሉም፡፡

አዲስ አበባ ሲታይ ምንም ያልተባለው ጉዳይ ባህርዳር ላይ ሲሆን ብዙ የማናገሩ ምንጩ ከወደ አማራ ክልል እና አማራ ህዝብ የሚመጣን ነገር ሁሉ የመጠራጠር፣የማጣጣል፣የመተቸት እና በክፉ የማየት ዝንባሌ ነው፡፡ ለምንጩ ምንጭ ስንፈልግ ደግሞ የአማራ ህዝብን እና የድሮውን ጨቋኝ ስርዓት አንድ እና ያው አድርጎ የማየቱ ሲደጋጋም እውነት የመሰለ ስሁት እሳቤ ነው፡፡ የገረመኝ ነገር ግን ይህ ሃሳብ የመጣው የትግራይ ህዝብን እና ህወሃትን ለዩ እያለ በተደጋጋሚ ሲናገር ከሰማሁት፣በምክንያታዊነቱ እንደምሳሌ ከምወስዳቸው ሰዎች አንዱ ከሆነው ከዶ/ር አወል ቃሲም መሆኑ ነው፡፡

ይህ ስሁት እሳቤ ጥቂት ምክንያታዊ በሚባሉ ምሁራን አእምሮ ጓዳ ውስጥም መሽጎ መገኘቱ የአማራ ህዝብ ፈተና ገና እንዳላበቃ አንድ ማሳያ ሊሆን ይችላል፡፡ ህዝብን እና ስርዓትን ከመለየት አንፃር የትግራይ ህዝብ ከህወሃት ተነጥሎ የመታየት ተገቢነት የሚሟገቱ ሰዎች የድሮውን የፊውዳል ስርዓት ከአማራ ህዝብ እና የአማራ እንደህዝብ የበላይነት ጋር አገናኝቶ ማየት፤የአማራ ህዝብ የቀድሞው ስርዓት የሚመቸው የታሪክ እስረኛ አድርጎ ማቅረብ እያቆጠቆጠ ያለውን የአማራ ብሄርተኝት ወደ ፅንፈኝት የመንዳት አደገኛ ውጤት ይኖረዋል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ የአማራው ህዝብ የቀድሞው ስርዓት ወኪል አድርጎ ማየቱ ራሱ እንደገና ሊጤን የሚገባው ጉዳይ ነው፡፡አማራው ኢትዮጵያ የምትባለዋ ሃገር ፀንታ እንድትኖር የሚፈልገው የቀድሞዋ ፊውዳል ኢትዮጵያ በአልጋ ላይ ስላስቀመጠችው አይደለም፡፡እንደሚታወቀው የፊውዳል ስርዓት ለሰፊው አርሶ አደር የመከራ ህይወትን የሚግት ስርዓት ነው፡፡አማራው ደግሞ አብዛኛው አፈር ገፊ ደሃ አርሶ አደር ነው፡፡በዚህ ስርዓት አማራው በተለይ የተጠቀመው፣የሚጓጓለትም ነገር የለውም፡፡አንድ የተለየ ያገኘው ነገር ቢኖር በቋንቋው የቤተ-መንግስት ስራ ተከውኗል፡፡ይህ ደግሞ ለአብዛኛው የቀለም ትምህርት አልቦ አርሶ አደር የሚጠቅመው ነገር የለም፡፡ በፊውዳሉ ሥርዓት ለቤተ-መንግስት ቀረብ ያለው አማራ ተመሳሳይ እድል የገጠመው ኦሮሞም ሆነ ሌላ የተጠቀመውን ያህል ተጠቅሞ ሊሆን ይችላል፡፡ክርስትና በሰሜን በኩል በመግባቱ የተነሳ አማራው የተሻለ የቤተ-ክህነት ትምህርት የመቅሰም እድል ስለነበረው አማርኛ ማንበብ መፃፍ በመቻሉ በመላ ሃገሪቱ ተበትኖ አነስተኛ ስራዎችን ለማግኘት እድል ነበረው፡፡ይህ ማለት ግን አማራው ሁሉ የቤተ-ክህነት ትምህርት የማግኘት እድል ነበረው ማለት አይደለም፡፡በፊውዳሏ ኢትዮጵያ ምንም ከመሆን በላይ የጦር አዋቂ መሆን ቤተ-መንግስት ጓሮ ለመታከክ ያስችላል፡፡ጦር አዋቂው ካሳ ሃይሉ፣አሉላ አባ ነጋ፣ሃብተጊዎርጊስ ዲነግዴ፣ራስ ጎበና ዳጨ ወዘተ የዚህ ማሳያዎች ናቸው፡፡

የአማራ ህዝብ ለፊውዳሉ ስርዓት ምልክትም ሆነ ጠበቃ የሚያደርገው የተለየ ጉዳይ የለም፡፡ የአማራውም ሆነ ሌላው ህዝብ ኢትዮጵያዊነቱን የሚወደው ኢትዮጵያዊ ከፊውዳሉ ስርዓት ጋር የሚጋራው ነገር የሃገሩን ህልውና አጥብቆ የሚወድ ስለሆነ ነው፡፡የፊውዳሉ ስርዓት ኢትዮጵያ ፀንታ እንድትኖር የሚፈልገው ከተፈጥሯዊው የሃገርፍቅር ባሻገር ግብር የመሰብሰብ ናፍቆቱም ነው፡፡ አማራው እና ሌላው ኢትዮጵያዊ ብሄርተኛ ደግሞ ሃገሩ ከሌለች እንደሌለ ስለሚያውቅ የሃገሩን ህልውና ይወዳል፡፡ ይህ የአማራ ህዝብ ብቻ ከኢትዮጵያ ህልውና ልዩ ተጠቃሚነት ስላለው የመጣ ሳይሆን አማራ ያልሆነው አብዛኛው ኢትዮጵያዊ የሚጋራው ስሜት እንደሆነ የሰሞኑ ሰልፎች አስረጅ ናቸው፡፡

አጠያያቂው ጉዳይ ይህን ነባራዊ ሃቅ በካደ ሁኔታ ሃገራዊ ምልክቶች እና የአንድነት አምሮቶች የአማራው ብቻ ፍላጎት ተደርገው የሚታዩበት እሳቤ ነው፡፡ይህ እሳቤ አማራውን የቀድሞው ስርዓት ልዩ ተጠቃሚ አድርጎ ከማሰብ እስከ የስርዓቱ ባለቤት አድርጎ የደረሰ መጓተት አለው፡፡አማራው የቀድሞው ስርዓት ተጠቃሚ ነው አይደለም የሚለው ልብ አውላቂ ክርክር አንድ እውነት ቢኖረው አማርኛ የሃገሪቱ የስራ ቋንቋ ሆኖ ስለኖረ አማራው/አማርኛ ማንበብ መፃፍ የሚችል ሁሉ በተለያየ ቦታ ተዘዋውሮ ስራ የማግኘት እና የስነልቦና ጥቅም አግኝቶ ይሆናል፡፡ እዚህ ላይ መነሳት ያለበት ጥያቄ ምን ያህሉ አማራ ማበብ መፃፍ ችሎ የስራ እድሉ ተጠቃሚ ሆነ?ምን ያህሉስ አማራ ያልሆነ ሰው አማርኛ ማንበብ መፃፍ እየቻለ አማራ ባለመሆኑ ብቻ አማሮች ከሚያገኙት የስራ እድል ተገልሎ ኖረ የሚለው ጥናት የሚጠይቅ ጉዳይ ነው፡፡

በሌላ በኩል አማራው ሃገሩን የሚወደው ባለፈው ስርዓት ተጠቃሚ ስለነበረ፣በደስታ በፍሰሃ ስለኖረ ነው ወይ የሚለው መጤን አለበት፡፡በሃገራችን ታሪክ ዋነኛ ክስተቶች አማራው የፊውዳሉን ስርዓት በመቃወም፣በመገዝገዝ ከሌላው ኢትዮጵያዊ ቢበልጥ እንጅ የሚያንስ ሚና አልነበረውም፡፡የተመቸው ህዝብ ለምን ያምፃል? ማን ጤነኛ የሰው ልጅ ነው በመልኩ በአምሳሉ የተበጄን ስርዓት ለማፍረስ የሚታገል? የባሌ እና የጌዲኦ ገበሬዎች ሲያምፁ የጎጃም ገበሬ የፊውዳሉ ስርዓት ባለቤት ነኝ ብሎ ዝም አላለም፡፡በአፄው ስርዓት የአውሮፕላን ቦምብ የወረደው በጎጃም እና በትግራይ ህዝብ ላይ ነው፡፡ ትንሽ ወደፊት እንለፍ ከተባለም አትዮጵያን የማበጀቱ መስፋፋት አካል የነበረው የኢምባቦ ጦርነት የጎጃምን ህዝብ አጭዷል፤የአፄ ቴድሮስ ቢለዋ የወሎን፣ አጤ ዮሃንስ ቢለዋ የጎጃምን ህዝብ እጅ ቆርጦ አንገቱ ላይ አንጠልጥሏል፡፡ መለስ ዜናዊ በሥነ-ስርዓቱ ህገመንግስት ፅፎ አማራው ላይ እንደ ኦሪት ለምፃም የመገለል፣የመገደል እና የመጠላት አዋጅ አውጇል፡፡ በአማራ ህዝብ ላይ በር ዘግቶ አነሰም በዛ ሌላውን ህዝብ ወክያለሁ የሚሉ ሰዎችን ሰብስቦ ህገ-መንግስት ፅፎ ግን አማራውም እንዲተዳደርበት አድርጓል፡፡የነገሩ ደራሲ ወያኔ ቀርቶ ለዲሞክራሲ እንታገላለን የሚሉ ተቃዋሚዎች የአማራ ፓርቲ ላለመባል አይሆኑ ሲሆኑ ኖረዋል፡፡ ወያኔ እና ኦነግ በሰለጠነ ዘመን አማራ የተባለን ፍጡር ወደገደል ወርውረዋል፡፡ ኦነግ አላደረግኩም ይላል፤የሚያምነው ካገኘ ቢያንስ ሲቃወም አላየንምና ከተጠያቂነት አይድንም፡፡

ዛሬ ኢትዮጵያን የሚመሩት ኦህዴዶች አማራውን የጎሪጥ የማየቱ በሽታ ያልነካካቸው ሰዎች አይደሉም፡፡ አማራውም በዚህ በሽታ ተሸካሚዎች አልተጠቃም ወይም መጠቃቱን የሚረሳ ነፈዝ ነው ማለት አይቻልም፡፡ ሌላው ቀርቶ ዘረኝነትን የተውት ዶ/ር አብይ የጠ/ሚነት ስልጣን ላይ እያሉ፣ኦቦ ለማ ኦሮሚያን እያስተዳደሩ እንኳን አማራው በኦሮሚያ ይታረዳል፡፡ዶ/ር አብይን ሊደግፍ የወጣው አማራ ላላዝን ቢል የሚያላዝንበት የሌለው፣ከታሪክ ማር ብቻ እየዘነበለት የመጣ ህዝብ አይደለም፡፡አላላዘነም ማለት አልተበደለም ማለት አይደለም፡፡ ይልቅስ ወዳጅ ጠላቱን ለይቶ ስለሚያውቅ ነው፡፡ የሚበድለው ማን እንደሆነ፣ህግ ፅፎ ሊገድለው የተማማለው መሰረታዊ ጠላቱ ማን እንደሆነ ስለሚያውቅ ለማ እና አብይ ላይ መነሳት ሳይሆን መደገፍን መርጧል፡፡የአማራው ህዝብ ኦሮሞውን ዶ/ር አብይን ደግፎ መውጣቱ ዘር ባለመቁጠር፣በደልን በመተው ሊያስመሰግነው ሲገባ መወቀሱ የሚገርም ነው፡፡

የባህርዳር ሰልፍ እና የብዝሃነት ጭፍለቃ

የባህርዳሩ ሰልፍ ዶ/ር አወል በመደመር ፖለቲካ ላይ የነበራቸውን ተስፋ ያጨለመ ብቻ ሳይሆን ተስፋ ማድረጋቸው ራሱ ስህተት እንደ ነበረ እርግጠኛ እንዲሆኑ ድርጓል፡፡ተስፋ ማድረግም ተስፋ መቁረጥም የግለሰቡ መብት ቢሆንም ለዚህ ውሳኔ ያደረሰው ምክንያት በተለይ ዶ/ር አወል በተለያየ አጋጣሚ ሲናገሩ ምክንያታዊነታቸውን ላየ ሰው ግር ማሰኘቱ አይቀርም፡፡ እንደ አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ተስፋ ያደረጉበትን የመደመር ፖለቲካ ተስፋቢስ ያደረገባቸው ምክንያት በባህርዳር ከተማ በተደረገው ሰልፍ ተጋባዥ የክብር እንግዳ ተደርገው የተጠሩት ወ/ሮ እማዋይሽ እና ጄ/ል አሳምነው ፅጌ ያደረጉት ንግግር ነው፡፡ወደ ንግግሩ ይዘት ከመግባቴ በፊት እነዚህ ሰዎች እንግዳ ሆነው ተጋበዙ እንጅ የመደመር ፖለቲካውን የሚዘውሩ ባለስልጣናትም ሆነ የአማራ ህዝብ በአፋቸው የሚናገርባቸው ልሳነ-ህዝብ አይደሉም፡፡ ዶ/ር አወልም በመደመር ፖለቲካው ላይ ተስፋ ያደረጉት ወ/ሮ እማዋይሽ እና በጄ/ል አሳምነው በጉዳዩ ላይ ያላቸውን እሳቤ ተመርኩዘው አይመስለኝም፡፡ ስዚህ የሁለቱን ሰዎች ንግግር እንደሰማሁ ወዲያው ተስፋ ቆረጥኩ ሲባል ተስፋ የመቁረጡ እውነተኛ ምክንያት ሌላ መሆን አለበት፡፡

ወደ ንግግሩ ይዘት ስገባ ሰዎች ነገራቸውን ለማጠናከር ከመፅሃፍ ቅዱስም ሆነ ከቁራን ከኦሾም ሆነ ከዳርዊን ንግግር ሊያጣቅሱ ይችላሉ፡፡ሰው እንደ ንባቡ ግንዛቤው ይቃኛል፡፡መንፈሳዊ መፅሃፍትን የሚያነቡ ሰዎች ከዛው ያጣቅሳሉ፡፡የእስልምና ሃይማኖት ተከታዮች እንዲህ ባለው ስብሰባ ላይ የነብዩ መሃመድን አባባሎች ሲጠቅሱ አጋጥሞኝ ያውቃል፡፡በአዲስ አበባው ሰልፍ “ዘረኝነት ጥንብ ናት ተዋት” የሚለው የነብዩ መሃመድን ጥቅስ በባነር አሰርተው ይዘው የወጡ የእስልምና ሃይማኖት ተከታይ ሰልፈኛ አይቻለሁ፡፡ይህን ያየ የክርስትና ሃይማኖት ተከታይ ሙሾ ሲያስወርድ አላጋጠመኝም፤ሌላ ተሸፋኝ ምክንያት ከሌለው ነገሩ ብቻውን ለዚህ የሚያደርስም አይመስለኝም፡፡ዶ/ር አወልም ንግግሩን ከአማራ ክልል ሌላ ቦታ፣አማራ ካልሆኑ ሰዎች አንደበት ቢሰማው ኖሮ እንዲህ የሚያሳስበው አይመስለኝም፡፡

ባንዲራው እና ምልክትነቱ

500ሜ የሚረዝም ባንዲራ ይዞ መውጣት በባንዲራው ምልክትነት ክፉ ለተደረገባቸውን ህዝባች ብሶት ግዴለሽነት ማሳየት፤ለመደመር ፖለቲካም ንቀት እንደሆነ የሚከሰው ዶ/ር አወል ክርክር በርካታ ጥያቄዎች ያስነሳል፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ ባንዲራው እንዲህ ያለ መልዕክት እንደሚያስተላልፍ የተከሰተለት ባህርዳር ላይ ብቻ ሲያየው ነው? በዚህ ባንዲራ ሃገር ሲገዙ የነበሩ ነገስታት ለአማራ ህዝብ ገነትን ከሰማይ አውረደው ለብቻው ደሴት ላይ አስጠልለውት ነበር?በባንዲራ ምልክት ዙሪያ ከተነሳ ወለጋ ላይ የተውለበለበውን አረንጓዴ፣ቀይ ፣አረንጓዴ ባንዲራ ሲያይ እናት አባቱ፣አክስት አጎቱ፣ዘመድ አዝማዱ በገደል ሲወረወር የሚያሰማው የሲቃ ድምፅ በጆሮው የሚያቃጭልበት አማራ ይጠፋል? ባህርዳሮች የምኒልክ ዘመን ድረስ ርቀው ሄደው ለሰው ስሜት እንዲያስቡ የሚያሳስበው ዶ/ር አወል ትናንት፣በሰለጠነ ዘመን ኢሰብዓዊ በሆነ መንገድ ዘመዶቻቸውን ያጡ አማሮች የወለጋውን ባንዲራ ሲያዩ የሚሰማቸውን ስሜት አጢኖ ትዊት ማድረግ ያልቻለው እንዴት ነው?

በኦሪት ዘመን የሞቱትን አፄ ምኒልክን በጨፍጫፊነታው በመጥላት ባንዲራውንም አታሳዩን በሚባልበት ዘመን ከህወሃት ጋር ግንባር ገጥመው ትናት በደኖ ላይ አማሮችን ያስፈጁት ኦቦ ሌንቾ ለታ አዲስ አበባ ላይ እንደማንኛውም ሰው እየተንጎራደዱ ነው፡፡ በመደመር ዘይቤው ኦቦ ሌንቾ ለታ ሃገራቸው ገብተው እንዲታገሉ የጠራውን ዶ/ር አብይን ሊደግፉ የወጡት አማሮች ደግሞ ግራ ቀኝ ያገናዝባል በተባለው ዶ/ር አወል ሳይቀር እየተወቀሱ ነው፡፡ እንዲህ ያለው ነገርስ የት ያደርሳል? ጥቅሙስ ምንድን ነው? ምሁራን ያላመጡት አስተዋይነት ከየት ሊጠበቅ ይችላል? እንዲህ ያለው የዶ/ር አወል ያጋደለ ክርክር እሱ በባህርዳሮቹ ተናጋሪዎች ላይ ተስፋ እንደቆረጠው በሌላ ፅንፍ ለቆመ ችኩል ተስፋ ቆራጭ ደግሞ የእሱን ክርክር ተስፋ ለመቁረጥ ግብዓት ለመሆን ምን ያንሰዋል?

አይን የፈለገውን ያያል ….

በዶ/ር አወል ቃሲም እይታ የባህርዳሩ ሰልፍ አንዳች በጎ ነገር የሌለው አሮጌውን አብሮነት ለማምጣት ያለመ እና ብዝሃነትን የሚጨፈልቅ ፈንጠዝያ ነው፡፡እዚህ ላይ የረሳው ትልቅ ነገር የባህርዳር ሰው የሚፈነጥዘው የወንዙ ልጅ ደመቀ በኦሮሞው ዶ/ር አብይ ተሸንፎ አብይ ስልጣን ስለያዙ ነው፡፡ ይህ ቢያንስ የባህርዳር ሰልፈኛ ከዘረኝነት ጋር ጉዳይ የሌለው ሃገሩን ካለ ጋር ሁሉ የሚሰለፍ በመሆኑ የሚያስመሰግን ነበር፡፡በአንፀሩ አማራው ደመቀ ተመርጦ፣ከሰማይ ሰባት አክሊል በሚያወርድ መልካምነት ቢመራ እንኳን ተመሳሳዩን በኦሮሚያ ከተሞች ስለማየታችን እርግጠኛ አይደለሁም፡፡ በተጨማሪም ብዝሃነትን በመጨፍለቅ የተከሰሰው የባህርዳር ህዝብ ከዋቆ ጉቱ እስከ አለማየሁ አቶምሳ፤ ከአቶ አሰፋ ጫቦ እስከ አማዳም አና ጎሜዝ የተወደሱበት ነበር ይህ ከብዝሃነት ጋር ግንኙነት ይኑረው አይኑረው ከጥላቻ የፀዳ ሁሉ የሚመሰክረው ነው፡፡በመጨረሻም ዶ/ር አወል ካለፈው ታሪክ እናስተታውሰው ዘንድ አንዳች በጎ ነገር የለም ሲል ያስቀመጠው ነገር የምሁርነት ምክንያታዊነትን ቀርቶ የበጎ አሳቢ ተራ ሰውን ቅንነት የሚመጥን ሆኖ እንዳላገኘሁት ማንሳት ብቻ ይበቃኛል! .

- Advertisement -Early Bird Holiday Deals! Before you know it, the holidays will be right around the corner! Take advantage of our early bird deals today and save up to $40 on our fees with code SPOT40!
Stay Connected
28,789FansLike
13,920FollowersFollow
8,540SubscribersSubscribe
Stacy Adams
Must Read
Related News

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here