ቦርከና
ሐምሌ 30 ፤ 2010 ዓ.ም
ባለፉት ጥቂት ቀናት በጂጂጋ ፤ በድሬዳዋ ፤ ቀብሪድሃር እና ሌሎች በሶማሌ ኢትዮጵያ ክልል ባሉ ከተሞች የተቀናበረ በሚመስል ሁኔታ ቢያንስ 29 ያህል ሰዎች መገደላቸውን ፤ በመቶዎች የሚቆጠሩ ቆስለው በርካቶች መፈናቀላቸውን ተከትሎ የክሉሉ ርዕሰ መስተዳደር መሃመድ አብዲ ኢሌ ዛሬ በፈቃዱ ስልጣኑን እንደለቀቀ ተሰምቷል።
ከስልጣኑ እንደለቀቀ የዘገበው የኢትዮጵያ ሶማሊያ የዜና አገልግሎት ነው።
የቢቢሲ የአማርኛ አገልግሎት ዛሬ እንደዘገበው በአካባቢው በተነሳው ግጭት ምክንያት ሰባት የኢትዮጵያ ኢርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት እንደተቃጠሉ ፤ ከእነዚህም አንዱ በ7 ሚሊዮብ ብር ወጭ ተገንብቶ የተመረቀው የኪዳነ ምህረት መንበረ ጸባኦት ቤተክርስቲያን እንደሆነ ዘግቧል ፤ አገልጋይ ካህናትም ተገድለው እንደተቃጠሉ ተሰምቷል።
በርካታ የፕሮቴስታንት አብያተ ቤተክርስቲያናትም እንደተቃጠሉ ተዘግቧል።
የኢትዮጵያ መንግስት የዜና ተቋማት በአካባቢው ችግር መኖሩን የሚያመካላከት ሪፓርት ትላንት እና ዛሬ አውጥተዋል።
በድሬዳዋ ብቻ ትላንት በተነሳ ግጭት 9 ሰዎች መሞታቸውን እና ከእነዚህም 4 ቱ ህጻናት እንደሆኑ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ዘግቧል፤
የክልሉ ተወላጂ የሆኑት የፌደራል መንግስት ኮሚኒኬሽን ሚኒስተር አህመድ ሸዴ ዛሬ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ በአካባቢው በነበረው ችግር ምክንያት በህይወት እና በንብረት ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰ ገልጸው ፤ አካባቢውን ከኢትዮጵያ እንገነጥላለን በሚል በተወሰኑ ባለስልጣናት እንቅስቃሴ እንደነበረ ፤ ከሃረር ወደ ድሬዳዋ እና ወደ ጂቡቲ የሚውስደውንም መንገድ ለመዝጋት ተሞክሮ እንደነበረ ገልጸዋል።
ይህንኑም ተከትሎ የፌደራሉ መንግስት የዜጎችን ህይወት ፤ ንብረት እና ድህንነት ለመጠበቅ የመከላከያ ሰራዊት በአካባቢው እንዳሰማራም አክለው ገልጸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በአካባቢው በደረሰው ውድመት ማዘናቸውን ገልጸው ሁኔታው ባስቸኳይ መቆመ እንዳለበት አሳስበዋል በጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽህፈት ቤት ኃላፊ የሆኑ አቶ ፍጹም አረጋ በትዊተር ገጻቸው እንዳሳወቁት።
__
ወቅታዊ እና ሚዛናዊ መረጃን ለማግኘት ቦርከናን በፌስ ቡክ ላይክ ያድርጉ።