spot_img
Thursday, November 30, 2023
Homeነፃ አስተያየትየፀጥታ ፈተናችን አንድ መፍትሄ (በመስከረም አበራ)

የፀጥታ ፈተናችን አንድ መፍትሄ (በመስከረም አበራ)

advertisement

(በመስከረም አበራ)

ሐምሌ 30 ፤ 2010 ዓ.ም.

ሃገራችን አሁን ያለችበት ፖለቲካዊ ሁኔታ ህወሃት በሌለበት ብቻ ሊከሰቱ የሚችል በጎ ነገሮችን እያስተናገደ ነው፡፡ይህ ሁሉ በጎ ነገር ህወሃት ከአድራጊ ፈጣሪነቱ እውነትም ገሸሽ እንዳለ ማሳያ ነው፡፡ዶ/ር አብይን ወደ ጠቅላይ ሚኒስትርነት ያመጣውን የኢህአዴግ ውስጠ-ፖርቲ ንጠት ከኋላ ሆነው መንዳት የሚወዱት ህወሃቶች ስንጣሪ አካል ይኖርበት ይሆናል የሚል ጥርጣሬ ነበረኝ፡፡ስለዚህ የለውጥ እንቅስቃሴው የህዝብን እውነተኛ ፍላጎት ያነገቡ ሰዎች የሚመሩት ነው ብሎ ለመቀበል ወሳኝ ፖለቲካዊ እርምጃዎች እስኪወሰዱ መጠበቅ ግድ ነበር፡፡አሁን ላይ ያለው ፖለቲካዊ ድባብ ከሞላ ጎደል የህዝብን ፍላጎት ማዕከል ያደረገ፣ይሆናል ብለን ካሰብነው በላይ መሪዎች የሃገርን ፈተና ለማቅለል እየጣሩ ያለበት ነው፡፡

የሃገራችንን ፖለቲካዊ ታሪክ ሲፈትን የነበረው፣መጋደልን ብቻ መፍትሄ አድርጎ የኖረው በተፃራሪ ፖለቲካ ሃይሎች መሃከል የነበረው ግንኙነት ዶ/ር አብይ/ቲም ለማ ምስጋና ይግባቸውና ወደ ሰለጠነ ቁጭ ብሎ የመነጋገር ዘይቤ ተሸሽሏል፡፡ይህ ራመድ ያለ ጅማሬ በጣም አስደሳች እና ተስፋ ሰጭ ነው፡፡በተፃራሪ የፖለቲካ ቡድኖች መሃከል የኖረው ያልሰለጠነ መስተጋብር የሃገራችን ፖለቲካ ውስብስቦሽ ትልቁ ምንጭ ነበር፡፡ የሃገራችንን የፖለቲካ ለሌሊት ያስረዘመውም እሱው ነበር፡፡ ይህን ክፉ ምዕራፍ ለመዝጋት ፍላጎት ያሳየው የዶ/ር አብይ/ቲም ለማ ስብስብ በሃገሪቱ ፖለቲካዊ ታሪክ መዝገብ ላይ ድንቅ አሻራ አስቀምጧል፡፡

የሃገራችን ሁለንተናዊ ችግር መንስኤው የደደረው ፖለቲካዊ ችግራችን በመሆኑ ፖለቲካዊ ችግሩን ሊፈታ ላይ ታች የሚለው የዶ/ር አብይ ቡድን በኢኮኖሚው፣በማህበራዊ ዘርፉ፣በውጭ ግንኑነቱ ሁሉ ከቀደምቶቹ የተሻለ ውጤት እንደሚያስመዘግብ ተስፋ ተጥሎበታል፤አያያዙም መልካም ነው፡፡ በህዝብ ዘንድ ያተረፈው አመኔታ ለስኬት ተስፋው ስንቅ ነው፡፡ሁሉን እኔ ልፍጄው ከሚለው የቀደምት መሪዎች ዘይቤ ወጥተው “መምራት እንጅ መንዳት አልፈልግም” ያሉት ዶ/ር አብይ ዘመኑን የሚመጥኑ መሪ ናቸው፡፡መምራትን እንጅ መንዳትን ያልመረጡት አብይ መልካምን እድል መርጠዋል፡፡

መንዳትን የሚመርጡት ቀደምቶቻቸው ሁሉን አውቃለሁ ባዮች ናቸውና በህዝብ ላይ በር ዘግተው ሁሉን ያደርጋሉ፡፡ስለዚህ ለሚመጣው ጥፋትም ሆነ ልማት ሃላፊዎቹም ራሳቸው ናቸው፡፡ መንዳት ያልወደዱት ዘመናዊው አብይ ግን በእድሜም በእውቀትም የሚልቋቸው ታላላቆች መኖራቸውን ያምናሉ፡፡ሁሉም ለሃገሩ የሚመበጅ ስንቅ ቋጥሮ ሳለ አሰባሳቢ ፖለቲካዊ ምህዳር በመጥፋቱ ብቻ ሃገር ብዙ እንደ ከሰረች ይገነዘባሉ፤ይህንኑ በየደረሱበት ይሰብካሉ፡፡ከመቅፅበት ታዳሚወቻቸውን ሁሉ ደቀ-መዘሙር የሚያደርግ የመሪነት ብልሃት አላቸው፡፡አድማጭን ያከብራሉ፡፡ከህዝብ እንደ አንዱ ያወራሉ፡፡ይህ መሰለኝ “መሪ እንጅ ነጅ አይደለሁም” ያሉለት ማንነታቸው፡፡መሪ ደግሞ ችግሩንም ቱርፋተንም ለተከታዮቹ አቅርቦ ‘ምን እናድርግ?’ ይላልና እንደ ነጅው በር ዘግቶ ብቻውን ሲፋትር ከችግር ጋር ሞቶ አይገኝም፡፡የመሪ ጉዳይ ሁሉ የተከታየቹም ጉዳይ ነው፡፡

መሪ የመሆንን መልም እድል የመረጡት ዶ/ር አብይ ወቅታዊ ችግር የሃገር ፀጥታ እና ደህንነት ነው፡፡ የሃገራችን ፀጥታ እና ደህንነት ደግሞ በህወሃት የቤተ-ዘመድ ገመድ እጅጉን ተተብትቦ የነበረ ዘርፍ ነው፡፡በዚሁ ዘይቤ ለሃምሳ አመት ሊገዛ ሲያሰላ የኖረው ህወሃት ያላሰበውን ለውጥ ተከትሎ ከዋነኛው እርስቱ በመነሳቱ ጥርስ የሚያፋጭ ነው፡፡ ሃገር ሰላም ውሎ ቢያድር የሚመኝም አይመስልም፡፡ ጭራሽ በተቃራኒው ሊሰራም ይችላል፡፡

ለዚህ የተመቼው ደግሞ የሃገር ባለቤት ሆኖ የፀጥታ እና ደህንነት መስኩን በሚዘውረበት ዘመን ከእርሱ ዘውግ ያልሆኑ የውትድርና ሳይንስ ልሂቃን እና ሃገር ወዳዶችን ክብር በሚነካ መንገድ ሞራላቸውን ሰብሮ፣ማዕረጋቸውን ነጥቆ፣ እስር ቤት ወርውሮ፣ከሃገር አባሮ የእለት ጉርስ እስኪያጡ ድረስ ያጎሳቆላቸው በርካታ መሆናቸው ነው፡፡ዶ/ር አብይ ወደ ስልጣን በመጡ ማግስት ለተወሰኑት ከፍተኛ ወታደራዊ መኮንኖች ቢያንስ ጡረታቸውን እና ማዕረጋቸውን መልሰው እንዲያገኙ በማድረግ በጎነታቸውን አስመስክረዋል፡፡ይህ ብቻ ግን በቂ አይደለም፡፡

እንደሚታወቀው ህወሃት ሃገሪቱን በሚዘውርበት ዘመን በሰለጠነ የሰው ሃይል ድርቅ ካስመታቸው የሃገሪቱ መስኮች አንዱ የውትድርናው እና ፀጥታው መስክ ነው፡፡ዘራቸው እንጅ እውቀታቸው ከቁብ ሳይገባ በሚያሳዝን ሁኔታ ከሙያ ገበታቸው እንዲገለሉ የተደረጉ በርካታ የውትድርናው ሳይንስ ምሁራን ሃገርቤትም በውጭ ሃገርም ይገኛሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች አንድም በጡረታ ሁለትም በሽብር ወይ በሌላ ስም ተለጥፎባቸው ነው ሃገራቸውን በሙያቸው እንዳያገለግሉ የተደረጉት፡፡ በውጭም ሆነ በሃገርቤት ያሉ እነዚህ ወታደራዊ መኮንኖች ለሃገራቸው በጣም የሚያስፈልጉበት ሰዓት አሁን ነው፡፡

የዶ/ር አብይ መንግስት በአሁኑ ሰዓት ለገባበት የሃገር ፀጥታ እና ደህንነት የማስከበር ፈተና እነዚህ ሰዎች ሁነኛ መፍትሄ ይመስሉኛል፡፡ ስለዚህ አብይ ለፖለቲካዊው ፈውስ ጉምቱ ፖለቲከኞች ሃገራቸው ገብተው እንዲሰሩ በጋበዙበት ሁኔታ ለተሰዳጅ ወታደራዊ ሳይንስ ምሁራንን እና ባለሙያዎችንም ተመሳሳይ ጥሪ ማድረግ አለባቸው፡፡የቀድሞው ዘረኛና አግላይ አስተዳደር ያለ አግባብ ተገፍትረው ለስደት የተዳረጉ የውትድርናው መስክ ምሁራን ወደ ሃገራቸው ተመልሰው ውጥንቅጡ እዳይወጣ የሚያስፈራውን የሃገራችንን የፀጥታ ሁኔታ መልክ እንዲያስይዙ ሊጋበዙ ያስፈልጋል፡፡

ይህ ግብዣ በደርግ ስርዓት ለሃገራቸው ሲያገለግሉ የነበሩ የጤናቸው እና የእድሜያቸው ሁኔታ ለአሁኑ የሃገር ጥሪ መልስ በሚያሰጥ ሁኔታ ያሉትንም የሚጨምር መሆን አለበት፡፡ ይህን ጥሪ ማድረጉን ቀላል የሚያደርገው ደግሞ አብዛኞቹ ተሰዳጅ ወታደራዊ ምሁራን በየዘርፋቸው ማህበር ያላቸው መሆኑ ነው፡፡ዶ/ር አብይ እነዚህን መኮንኖች በመጥራቱ ካመኑበት በማህበራቸው በኩል ማናገሩ አካሄዱን ቀላልም መደበኛም ያደርግላቸዋል፡፡

በተመሳሳይ እንደ ጀነራል ሳሞራ ያሉ አዛውንቶች ስልጣን በስልጣን ላይ ማዕረግ በማዕረግ ላይ ሲጨመርላቸው በእድሜም ሆነ በአካላዊ ብቃት ከእነርሱ ወጣት የሚሆኑት ሰዎች ዘራቸው እድሜ ሆኖ ተቆጥሮ በጡረታ እንዲገለሉ ተደርገው ሃገርቤት በችግር እና በቁጭት እንደሚኖሩ ከዶ/ር አብይ የተሰወረ አይደለም፡፡እነዚህ ወታደሮች ይህ ሁሉ የደረሰባቸው ለቀድሞው አስተዳደር የማይመች ነገር ስለተገኘባቸው፣ከግፍ ጋር አናብርም ስላሉ ነው፡፡ እንዲህ ያሉ ሰዎችን ለመልሶ አገልግሎት ቢጠሩ የቀደመው ከፋፋይ ስርዓት እንዳያንሰራራ በቁጭት እና በትጋት ያገለግላሉ ብየ አስባለሁ፡፡

በወጭ ሃገር ያሉቱ በያሉበት ሃገር ቤተሰብ የመሰረቱ፣ጠለቅ ያለ የኑሮ ስር ያላቸው ሊሆኑ ስለሚችሉ በዚህ ወሳኝ እና አስቸኳይ ሰዓት ጓዝ ጠቅልሎ ወደ ሃገርቤት መምጣቱ የሚያስቸግራቸው ቢሆን እንኳን ቤተሰባቸውን በሚመቻቸው ቦታ አድርገው እነርሱ ለተወሰነ ጊዜ ሃገራቸውን የሚያገለግሉበት ከዛም ተመልሰው ወደመጡበት ሃገር መሄድ ከፈለጉ ይህንኑ እነስከ ማመቻቸት መሄድ ይቻላል፡፡

ይህ በጣም አስፈላጊ የሚሆንበት ምክንያት ህወሃቶች ስር ሰደውበት የኖሩበት የፀጥታው ክበብ አልፎ አልፎ በዋነኛ ቦታዎች እንኳን በሌላ ካልተተካ ስልጣን መነጠቃቸው ሞት ለሚመስላቸው አኩራፊዎች ቀዳዳ ማስገኘቱ አይቀርምና የሃገሪትን ፀጥታ የማስከበሩን ፈተና ያወሳስበዋል፡፡
የሃገር ፀጥታ ባልተከበረበት ሁኔታ ደግሞ በህወሃቶች እና ጀሌዎቻቸው እንደ ደመኛ ጠላት የሚታዩ የእውነተኛ ተፎካካሪ ፓርቲ መሪዎች ወደ ሃገርቤት በሚገቡበት ሰዓት እንደልባቸው ተንቀሳቅሰው ለመስራት የደህንነት ስጋት ሊኖርባቸው ይችላል፡፡ ይህ ስጋት ለዶ/ር አብይም የሚቀር አይመስለኝም፡፡የፖለቲካው ፈውስ የሚፀናው ፀጥታ እና ደህንነቱ አስተማማኝ ሲሆን ስለሆነ በዚህ ረገድ ሃገራቸውን እንዲያገለግሉ በቀድሞው አስተዳደር ገለል የተደረጉ በሳል ወታደራዊ ምሁራንን መጋበዙ አስፈላጊም አንገብጋቢም ጉዳይ ይመስለኛል፡፡

በአሁኑ ወቅት በሃገራችን የደህንነት እና ውትድርናው መስክ የተሰገሰጉ ሰዎች እንከናቸው ብዙ ነው፡፡ አንደኛ ይህ ነው የሚባል ወታደራዊ ትምህርት የቀሰሙ ሳይሆኑ ህወሃትን ሳያሰልሱ በማገልገላቸው ወይ ጎሳቸው ከገዥ ጎሳ ስለሆነ ብቻ በማዕረግ ላይ ማዕረግ የተደረበላቸው ናቸው፡፡ የአስራ ሰባት አመቱ የገበሬ ጦር ሽምቅ ውጊያው ስለሰመረላቸው ብቻ ይሄው የውትድርና ሳይንስ እንደመቅሰም ተቆጥሮ ሰማይ የደረሰ ማዕረግ የተሸከሙ ብዙ ናቸው፡፡እነዚህ ሰዎች ከእውቀት ውስንነት ባሻገር አሁን ላለው ለውጥ ታማኝነታቸውም አጠራጣሪ ነው፡፡

የመለስ ዜናዊን ደንነት ለማስጠበቅ የሰው ቆዳ ውስጥ ገብተው መፈተሸ የሚቀራቸው የፀጥታ አካላት ገዳይ በመኪና ቦምብ ጭኖ በህዝብ መሃል አልፎ በመሪ ላይ ሲወረውር አላወቁም ብቻ ሳይሆን ለስኬቱ አልሰሩም ማለት ያስቸግራል፡፡ ስለዚህ እንዲህ የእውቀትም የታማኝነትም ድርብ እንከን ያለበትን የፀጥታ ዘርፍ ቀደም ሲል ተገፍትረው በወጡ ወታደራዊ ባለሙያዎች መበረዝ ችግሩን በአንዴ ባያጠፋው እንኳን ሊያቃልለው ይችላልና በመንግስት በኩል ቢታሰብበት፡፡
____
ማስታወሻ:በዚህ ጽሁፍ ላይ የተንጸባረቁ ሳሃቦች የጸሃፊውን/የጸሃፊዋን እንጂ የድረገጹን አቋም አያንጸባርቁም።
ነጻ አስተያየት ወይንም ሃሳብ በዚህ ድረ ገጽ ለማውጣት ጽሁፍዎትን በeditor@borkena.com ወይንም በ info@borkena.com ይላኩልን።

- Advertisement -Early Bird Holiday Deals! Before you know it, the holidays will be right around the corner! Take advantage of our early bird deals today and save up to $40 on our fees with code SPOT40!
Stay Connected
28,789FansLike
13,920FollowersFollow
8,540SubscribersSubscribe
Stacy Adams
Must Read
Related News

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here