spot_img
Thursday, November 30, 2023
Homeነፃ አስተያየትስለ አዲስ አበባ ከተማ አመሰራረት (ከፕሮፍስር ሪቻርድ ፓንክረስት የታሪክ መጽሃፍ የተተረጎመ)

ስለ አዲስ አበባ ከተማ አመሰራረት (ከፕሮፍስር ሪቻርድ ፓንክረስት የታሪክ መጽሃፍ የተተረጎመ)

advertisement

ከአገሬ አዲስ
መስከረም 23ቀን 2011ዓም (03-10-2018)
(ጽሁፉን በፒዲ ኤፍ ለማንበብ ይሄን ይጫኑ)

የአዲስ አበባ ከተማ መመሥረት እንደ ቀድሞው ከተሞች አክሱምና ጎንደር በአገሪቱ ታሪክና ሂደት ላይ ትልቅ ለውጥና አስተዋጽኦ አምጥቷል።የአዲስ አበባ በከተማነት መመሥረት ምኒሊክ የሸዋ ንጉስ በነበሩበት ጊዜ የተቀመጡበትን አንኮበርን ለቀው በአንጦጦ አካባቢ ውቃቃ በተባለው ኮረብታ ላይ ከመስፈራቸው ጋር የተያያዘ ነው።ምንም እንኳን በእንጦጦ ላይ ከተማቸውን ለመመሥረት ፍላጎት ቢኖራቸውም፣ ልባቸው ቢከጅልም የእንጦጦ መልከዐ ምድርና ተራራማነት ለመገናኛና ለመጓጓዣ አዳጋች፣ በተጨማሪም ነፋሻና ብርዳማ ስለነበር ለከተማነት አመቺ ሆኖ አልተገኘም። ስለሆነም ወደ ሌላ ቦታ ለመንቀሳቀስ ፍላጎት ነበር።እቴጌ ጣይቱ ብጡል የንጉስ ምንሊክ ባለቤት ዐይናቸውን የጣሉበትና የተማረኩበት ከባቢ ከእንጦጦ ባሻገር ከዝቅተኛው/ከረባዳው/መሬት ላይ ነበር።ቦታው ላይ ፊኒን እያለ(እየፈነነ)የሚወጣ ውሃ/ጠበል/በመኖሩ ምክንያት በሕዝቡ አጠራር ፊኒኔ ወይም ፊንፊኔ ይባል እንደነበረ ታሪኩን የሚያውቁ ሰዎች ይመሰክራሉ።አሁንም በቅርቡ የአዲስ አበባ ከተማ ጥንት ሸገር ተብሎ ይጠራ እንደነበር ለመታወቅ ተችሏል።ለዚህ ፍንፊኔ ለሚለው አጠራር እንደማስረጃ ያህል ለማቅረብና ለማስታወስ ከጽሁፉ መጀመሪያ ላይ ስለ ቦታ ስያሜና አጠራር የተገለጸውን ማስታወሱ ይረዳል፤ በተጨማሪም ጨዋታን ጨዋታ ያነሰዋል ይባላልና በተመሳሳይ መንገድ እኔ የተወለድኩበት መንደር ስም እንዴት እንደመጣ ታሪኩን ጠቀስ አድርጌ ባልፍ ለአንባቢው የበለጠ ግንዛቤ ይሰጣል ብዬ አምናለሁ።

የተወለድኩት ደሴ ከተማ ሳላይሽ ተብሎ በሚጠራው ሰፈር ውስጥ ነው።የሰፈሩ አጠራር የመጣው በአደዋ ዘመቻ ጊዜ የአፄ ምኒሊክ ጦር ወሎ ውስጥ ወረኢሉ በሚባለው ቦታ እንዲሰበሰብና ጉዞውን ወደ ሰሜኑ እንዲቀጥል በወጣው አዋጅና ጥሪ መሠረት የጦር አበጋዞችና መሪዎች በዛው በተባለው ቦታ ተሰበሰቡ።ወደ ሰሜኑ የጦር ሜዳ ለመሄድ የግድ በደሴ ከተማ በኩል ማለፍ ነበረባቸው።ከዘማች መሪዎቹ መካከል አንዱ እራስ (ለጊዜው ስማቸውን አላስታወስኩትም)አድዋ ደርሰው በድል አድራጊነት ሲመለሱ እንደመጀመሪያው ጊዜ በደሴ ማለፍ ሳይሆን አዳርም አድርገው ነበር።ድንኳናቸው የተተከለውና እረፍት ያደረጉበት ቦታ እኔ የተወለድኩበት መንደር ነበር።ደጃዝማቹ ከመንገድ እንዳረፉ የሚጠጣ ውሃ ይጠይቃሉ፤የቀረበላቸውን ውሃ ጭልጥ አድርገው ከጠጡ በዃላ እንዲደገማቸው ይጠይቃሉ ፣ተደገማቸው። ከዛም እንዲህ ያለው ጣፋጭና የሚያረካ ውሃ ከየት መጣ? ብለው ሲጠይቁ ከዚሁ ሠፈር ከሚመነጭ ምንጭ የተቀዳ ነው የሚል መልስ አገኙ፤ ለካስ ወደ አድዋ ስሄድ ትልቅ ነገር አምልጦኝ ኖሯል፤ ምንም እንኳን በቦታው ባልፍም ቦሩ ሜዳ ገብቶ ለማደር በመገስገሴ ይህን የመሰለ ጣፋጭና የሚያረካ ውሃ ለመቅመስ አልቻልኩም፣ሳላየውና ሳልቀምሰው አልፌዋለሁ፤በሉ ከአሁን በዃላ ምንጯን “ሳላይሽ” ብላችሁ ጥሯት አሉ ይባላል።ከዚያ በዃከተማም አልፎዝማቹ በተሰየመችው ምንጭ በሳላይሽ ለመጠራት በቃ።ይህን ታሪክ የነገረችኝ ወላጅ እናቴ ነች።ሌሎችም ታሪኮች ማታ ማታ እሳት ዳር ሆነን ቆሎ እየቆረጠምን ነግራኛለች።

የአዲስ አበባ ከተማም አልፎ አልፎ ፊንፊኔ በሚለው አጠራር የሚታወቀው በአሁኑ ፍልውሃ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ፊኒን እያለ በመውጣቱ በሕዝቡ ፊኒኔ ተብሎ ይጠራ በነበረው ውሃ/ጠበል/ አካባቢ የመጀመሪያዎቹ ቤቶች በመሰራታቸውና መንግሥታዊ ተቋም በመመስረቱ ነው።ለዚህም አጠራር በአብዛኛው መልኩ ከላይ ከጠቀስኩት የሳላይሽ መንደር ስያሜ ጋር ይመሳሰላል። የነበረውን አጠቃላይ መልክ የታሪክ መዝጋቢው ገ/ሥላሤ እንዲህ ሲሉ ያቀርቡታል፦

በክረምቱ ወራት በ1886 ዓ.ም. ንጉሥና ንግሥቲቱ ለሁለተኛ ጊዜ ወደ ፍል ውሃ ለጠበል ሄደው በከባቢው ብዙ ድንኳኖች ተተከሉ።ንግሥት ጣይቱ ባላቸውን አፄ ምንሊክን በዛ ከባቢ ቤት ለመሥራት እንዲችሉ ፈቃድ ጠየቁአቸው።ንጉሡም አሁን የቤት መሥሪያ ቦታ በዃላ ደግሞ አገር እሰጥሻለሁ ሲሉ ፈቀዱላቸው።ንግሥቲቱም የት ቦታ ላይ ልሥራ ብለው ባላቸውን ቢጠይቋቸው፣ምኒሊክ በእጃቸው እየጠቆሙ፣ከዛ አባቴ፣ንጉስ ሣህለ ሥላሤ በአጥር ከልሎ ካስቀመጠው ቦታ ላይ ሥሪ አሏቸው። ብለው ጸሃፊው ይገልጻሉ። ቀጥለውም ምንሊክ ስለአባታቸው ምኞትና ትንቢት አብረዋቸው ለነበሩት መኳንንት “አባቴ ከዛ ዛፍ ስር ገበጣ እየተጫወቱ በነበረበት ጊዜ እንደ ትንቢት አንተ ቦታ ወደፊት የልጅ ልጄ ከተማ ይመሠርትብሃል” ብለው ተናግረው እንደነበር ገ/ሥላሤ ገልጸዋል።

በሌላም መጽሃፍ ላይ አጼ ምንሊክ አገር ለማሰባሰብ በሚጥሩበትና በሚዘምቱበት ወቅት በሓረር ሰፍኖ የነበረውን በጎሰኛ ባላባቱ በሱልጣን አብዱላሂ መዳፍ ስር የነበረውን አስተዳደር ለማሶገድ በቦታው እንደነበሩ ከባለቤታቸው ከእቴጌ ጣይቱ አንድ ደብዳቤ ደረሳቸው።እቴጌዋ በጻፉላቸው ደብዳቤ ለሁሉም የተመቼ ጥሩ መሬት አግኝቻለሁ፤ከተማ ልቆረቁር አስቤአለሁና ቤት እንድሠራ ይፈቀድልኝ፣ቦታውንም አዲስ አበባ ብዬዋለሁ የሚል ነበር።ባላቸውም አጼ ሚኒሊክ በሃሳቡ ተስማምተው ቤት እንዲሠሩ ፈቀዱላቸው የሚል ታሪክ ነው።ግራም ነፈሰ ቀኝ በመሰረታዊው የአዲስ አበባ ከተማ አመሰራረት ላይ የሚጋጭ አይደለም።

በማግስቱ እቴጌ ጣይቱ የሚፈልጉት ቤት እንዲሠራ ትዕዛዝ ሰጡ።በሚቀጥለውም ዓመት በ1887 ዓ.ም.የቤቱ ሥራ ተጠናቆ እቴጌ ጣይቱ ከእንጦጦ ለቀው ከጠበሉ በላይ ከተሠራው ወደ አዲሱ መኖሪያ ቤታቸው ተንቀሳቀሱ።አብሯቸው የተንቀሳቀሰው አጃቢ እንደየማዕረጉ እያራራቀ የግል መኖሪያውን ሠራ።የከባቢው መልክ ተለወጠ።የሚያምር መንደር ሆነ።በዚያም ወቅት ነው የከባቢውን ማማርና ለውጥ የተገነዘቡት እቴጌ ጣይቱ አዲስ አበባ የሚል መጠሪያ ስም ያወጡለትና መጠራት የጀመረው።

ከግማሽ መቶ ዓመት በዃላ የወጣው የአዲስ አበባ ከተማ ማዘጋጃ ቤት መግለጫ እንደሚያሳየውና የመጀመሪያው ከንቲባ ፊታውራሪ ደምሴ ወ/አማኑኤል እንደገለጹት በፊንፊኔ ዙሪያ የነበረው መሬት እንደ ግለሰቡ የሥልጣን ደረጃና ለንጉሡ እንዳለው አቅርቦት እንደሚከተለው ተደልድሎ ነበር።
ልዑል ራስ መኮነን፣ንጉስ ሚካኤል፣ራስ ወልዴ፣ፊታውራሪ ሀብተ ማርያም፣ራስ ደረጀ፣ደጃ.ወ/ገብርኤል፣እቴጌ ጣይቱ፣የቤተመንግሥት ጥበቃ ክፍል፣የሠንጋ ማረጃ ክፍል/ቄራ/፣ሊጋባ ጣሰው፣አፈንጉስ ነሲቡ፣ጽሃፌትዕዛዝ ገ/ሥላሤ፣ራስ ናደው፣እጨጌ ገ/ሥላሤ፣በጅሮንድ ፍቅረሥላሤ፣ራስ አባተ(በዃላም እቴጌ ሆቴል)፣ደጃ.ገርማሜ፣ፊታውራሪ አባኮራን፣ነጋድራስ አግደው፣የሠራተኞች ክፍል(ማድ ቤቶች)፣ደጃ.ውቤ፣ደጃ.ብሩ ሀ/ማርያም፣ፊታውራሪ ገበዬሁ፣ጎላ ሠፈር፣ንጉስ ወ/ጊዮርጊስ፣አዛዥ ግዛው፣ራስ ቢትወደድ ተሰማ፣ደጃዝማችበሻህ አቦዬ፣ሊቀመኳስ አድነው፣ጠመንጃ ያዥ ሠፈር፣ራስ ልዑል ሰገድ፣ደጃዝማች ገነሜ፣ራስ ጎበና ዳጨ…ሌሎቹም ከነባለሟላቸው እንደየማዕረጉ የመኖሪያ ቤት እየሠሩ ከተማዋን አደመቋት።
የአዲስ አበባ ከተማ ሰፋፊ ቦታ በነዚህ ከዚህ በላይ በተገለጹት ባለሥልጣኖች ይዞታ ሥር ውሎ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ አሁንም አንዳንዱ ከባቢ በስማቸው ለመጠራት ችሏል።

የአዲስ አበባ ከተማ እያደገ ሲሄድ፣የውጭ አገር ተወላጆችም እየመጡ መኖር ጀመሩ።የጆርጅያ ተወላጅ የነበሩት ሃኪም፣መድሃኒት ቀማሚ/ፋርማሲስት/ዶር.መረብ እንደገለጹት፣-

በ1891 ዓ.ም.ምኒሊክ የንጉሡ ከተማ ወደ ሌላ ቦታ ዳግም እንደማይንቀሳቀስ ቃል በመግባት ቁጥራቸው ከ15 ለማያንሱ የውጭ አገር ተወካዮች/ዜጎች/የመኖሪያና የመሥሪያቤት መገንቢያ ቦታ እንዲሰጣቸው በመወሰናቸው ግንባታው በአጭር ጊዜ ውስጥ ተጠናቀቀ።
ከጊዜ በዃላ ግን በከተማዋ ውስጥ ችግር እየተከሰተ መጣ፤የብዙ ነገሮች እጥረት ተፈጠረ።በተለይም ለማገዶ የሚሆን አንጨት ጠፋ።በከባቢው የነበረው ጫካ አለአግባብ በግፍ በመጨፍጨፉ፣ለተቆረጠውም መተኪያ ስላልተተከለ፣ጭራሮና ሣር ሳይቀር እየተመነጠረ ለማገዶ ስለዋለ ችግሩ ጣራ ነካ።በኢትዮጵያኑ ዘንድ ለተቆረጠው ዛፍ ምትክ የመትከሉ ልማዱም፣እውቀቱም፣ፍላጎቱም አልነበረም።በችግሩ የተነሳ አዲስ አበባን ለቆ ወደ ሌላ ቦታ ለመስፈር ሃሳብ ቀርቦ ነበር።ሆኖም ግን በውጭ አገሩ ተወላጆች ምክርና ተቃውሞ ለመንቀሳቀስም የሚያመጣውን ድካምና የንብረት ውድመት በማየት ለማገዶ የሚሆን እንጨት ከሩቅ እያመጡ ለመጠቀም ተወስኖ የከተማው ምስረታ እንዲቀጥል ሆነ።በጫካውና በዛፉ ምክንያት መናገሻ፣ሜጫና፣አዲስ ዓለም ለከተማነት ታጭተው ነበር።በንጉሱ የመጨረሻ ውሳኔ አዲስ አበባ የመንግሥቱ መቀመጫ ዋና ከተማ ሆነች።የመጀመሪያዎቹ ያውሮፓውያን የድንጋይ ቤቶች መሠራት ተጀመሩ።የችግሩ መከሰት ኢትዮጵያኑን በተለይም ምኒሊክን የጫካን ልማት ጥቅም እንዲረዱና እንዲስፋፋ፣ዛፍ አለአግባብ እንዳይቆረጥ የሚያግድ አዋጅ እንዲያወጡ ገፋፋቸው።ለአገሩ እንግዳ የሆነውም ባሕር ዛፍ(ከባህር ማዶ ስለመጣ)በሰፊው እንዲተከል መመሪያ ወጣ።በ1910 ዓ.ም.የአዲስ አበባ ነዋሪ ቁጥር ከ60-100 ሽህ እንደሚሆን ይገመት ነበር።

የንጉሳዊ ቤተሰቦችና የቅርብ መሳፍንቶች የሚበልጠውን ሠፋፊ የከተማ ቦታ ሲይዙ ከከተማው 58% የሚሆነው ቦታ በ1768 በሚሆኑ ባለቤቶች ማለትም ከ10.000-71.000 ካሬ ሜትር በነፍስ ወከፍ ተይዞ እንደነበር በዃላ የተመረመረው ማስረጃ ያሳያል። ከዚያም ሌላ 24.590 የሚሆኑ ዝቅተኛ ባለይዞታዎች 7.4% ሚሆነውን ቦታ ሲይዙ፣12.7% ለመንግሥትና ለውጭ አገር ኤምባሲዎች,12% ለቤተክህነት፣ቀሪው 9.9% በስውር ለቤተመንግሥቱ ቤተሰቦች ተከፋፍሎ ተይዞ ነበር።

የከተማ ቦታ ምሪት በ19ኛው መቶ መጀመሪያ ዓመት ላይ የባለቤትነትን የሚያረጋግጥ አዲስ መልክ ያዘ።ይህም በመሬቱ ባለቤቶች ላይ የነበረውን ስጋት ሊፍቀው ቻለ።ምንም እንኳን ንጉሥ ምኒሊክ የቦታው፣የመሬቱ ባለቤትና ሰጭ ነሹ እራሳቸው ሆነው ሳለ በቋሚነት ለሌሎቹ መብት አሳልፎ መስጠቱ ቢያሰጋቸውም በውጭ አገር አማካሪዎች ግፊት ሙሉ በሙሉ ባያምኑበትም የሚከተለውን 32 አንቀጽ የያዘ ሕግ በማህተማቸው ተረጋግጦ በ1907 ዓ.ም.በአዋጅ ወጣ።

አንቀጽ 1- እኔ ምኒሊክ ሁለተኛ የኢትዮጵያ ንጉሥ ለአገሬና ለውጭ አገር ተወላጆች ሕጉን እስካልጣሱ ድረስ በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ መሬት የመግዛት መብት የሚያስችላቸውን ልዩ ሕግ ፈቅጀ አሳልፌአለሁ።

አንቀጽ 2- መንግሥት ለመሬቱ የሚከፈለውን የዋጋ ተመን ያወጣል።

አንቀጽ 3- ግለሰብ የመሬት ባለቤቶች/ባለይዞታዎች/በሕጉ መሰረት የያዙትን መሬት ለመሸጥ ይችላሉ።

አንቀጽ 4- የመሬቱ ልክ በካሬ ሜትር ይሆናል።አንድ ካሬ ሜትር ማለትም አንድ ሜትር በአንድ ሜትር ነው።

አንቀጽ 5- መሬቱን የሚሸጥና የሚገዛ የመሬቱ ስፋት በምስለኔ(በባለሥልጣን) የተረጋገጠና መሃንዲስ በካርታ ያስቀመጠው መሆን ይኖርበታል።

አንቀጽ 6- የካርታው ግልባጭ ለመንግሥት ቢሮ ቀርቦ በአዲስ አበባው የካርታ ዝርዝር ካድስትራል ውስጥ መካተት ይኖርበታል።

አንቀጽ 7- የድንበሩ፣የዋጋው መጠን፣የመሬቱ ስፋት በሁለት መሃንዲሶች የሚወሰን ሲሆን ከሁለቱ አንዱ ወይም ሁለቱም መሃንዲሶች የመንግስት ተቀጣሪዎች መሆን ይኖርባቸዋል።እነሱም ለመቃኘትና ለመመዝገብ አላፊነት ሲኖርባቸው ለሥራቸው አበላቸውን የሚከፍለው መንግሥት ነው።

አንቀጽ 8- የመንግሥት መሬት በሚሸጥበት ወቅት የመሃንዲሱን ዋጋ ገዥው ይከፍላል።የተለዬ ሁኔታ ሲገጥም ወጭውን ማን መክፈል እንደሚኖርበት ገዥውና ሻጩ ተስማምተው ይወስናሉ።

አንቀጽ 9- የመንግሥት ተወካይ የመሬቱን ዋጋ የመተመን ሥልጣን አለው።መንግሥትም ለገዢ ቀብድ የመክፈል መብት ይሰጠዋል። ሆኖም ግን በሙሉ ተከፍሎ የሚያልቅበት የጊዜ ገደብ በግልጽ መቀመጥ ይኖርበታል።በተወሰነው ቀን ተከፍሎ ካላለቀ መንግሥት መሬቱን መልሶ የመውሰድ መብት አለው።ለገዥውም የከፈለው ገንዘብ ያለ ወለድ ተመላሽ ይሆናል።

አንቀጽ 10- መንግሥት ለመሬት ገዡ የባለቤትነት የምስክር ወረቀት በመስጠት ለመስራት የሚፈልጉትን ነገር በሕጉ መሰረት እንዲሰሩ ፈቃድና እውቅና ይሰጣል።ነገር ግን ይህን የምስክር ወረቀት የሚያገኙት የገዙበትን ገንዘብ ሙሉ ለሙሉ መክፈላቸውን በሕጉ መሰረት የተደነገገውን ማክበራቸው ሲረጋገጥ ነው።

አንቀጽ 11- የምስክር ወረቀቱ ኮፒ በመዝገብ ቤት ውስጥ መኖር ሲገባው ቁጥሩ፣የሻጩ ስም፣የገዡ ስም፣የመሬቱ ስፋት፣በቦታው ላይ ያለ ቋሚ ንብረት፣ድንበሩ፣የጎረቤቶቹ ስም፣የከባቢው ስም፣የመሬቱ ዋጋ፣እንዲሁም የተሸጠበት ዓመት ወርና ቀን ተተንትኖ መቀመጥ ይኖርበታል።

አንቀጽ 12- የሚሰጠው የምስክር ወረቀት የመንግሥት ማህተም የሰፈረበት ሲሆን ለማህተሙ 10 ብር በተጨማሪም ቀረጥ 1መቶኛ(1%) ብር ከጠቅላላው የመሬቱ ዋጋ ተተምኖ ለመንግሥት ይከፈላል።

አንቀጽ 13- አንድ ግለሰብ መሬት ሲሸጥና ሲገዛ የመንግሥት ተወካይና ሁለት እማኞች መገኘትና በምስክር ወረቀቱ ላይ መፈረም ይኖርባቸዋል።

አንቀጽ 14- ግለሰብ መሬት በሚሸጥበትና በሚገዛበት ወቅት ሽያጩ(ውሉ)በመንግሥት ማህተም ተረጋግጦ ከመንግሥት መዝገብ ውስጥ መመዝገብ ይኖርበታል።በአንቀጽ 12 መሰረትም የተደነገገው የ 10 ብር ክፍያና የጠቅላላው የመሬቱ ዋጋ የመቶ አንደኛ(1%)ክፍያ ገቢ ይሆናል።

አንቀጽ 15- ገዥና ሻጩ የተስማሙበትን እውነተኛ የገንዘብ ልክ ሸፍነው የተሳሳተ ዋጋ ለመንግሥት ካቀረቡና ከተደረሰበት ገዢው አራት እጥፍ ለመንግሥት የሚገባውን ገቢ ይከፍላል።ሻጭና ምስክሮቹ የገዢው ተያዦች ይሆናሉ።ነገር ግን ወንጀሉ ሳይታወቅና ሳይጋለጥ ሁለት ዓመት ከሞላው ማንም በጥፋቱ አይጠየቅም።

አንቀጽ 16- የውጭ አገር ተወላጆችና ኩባንያዎች በሕጉ መሰረት መሬት የመግዛት መብት ሲኖራቸው መጠኑ ግን ከአስር ሄክታር አይበልጥም።ሆኖም ግን መንግሥት ለመጨመር መብት ይኖረዋል።ይህን ሕግ የሚጥስ ከፍተኛ ቅጣት ይቀጣል።መሬቱ ይወረሳል።የገዛበት ዋጋ ብቻ ተመላሽ ይሆናል።

አንቀጽ 17- የመሬቱ ባለቤት መሬቱን ከገዛበት ጊዜ በ25 ዓመት ውስጥ መልሶ በትርፍ ሲሸጥ ለመንግሥት ከትርፍ አንድ ሶስተኛውን(1/3)የመስጠት ግዴታ አለበት።ይህን ሕግ ጥሶ የተገኘ በ15 አንቀጽ የተገለጠው ሕጋዊ እርምጃ ይፈጸምበታል።

አንቀጽ 18- ከመንግሥት የተገዛ መሬት ዋጋው ሙሉ ለሙሉ ተከፍሎ ሳያልቅ ቢሸጥ ሻጭና ገዢ ቀሪውን ማን እንደሚከፍል ለመንግሥት ማሳወቅ/መግለጽ/ ይኖርባቸዋል።ይህም የውል ስምምነት በመንግሥት መዝገብ ውስጥ ይሰፍራል።

አንቀጽ 19- ለመንግሥት የሚከፈል የመሬት ማለትም የሽያጭና የግብር ዕዳ ከሁሉም ቅድሚያ ይኖረዋል።

አንቀጽ 20- መሬቱን የገዛው ግለሰብ የምስክር ወረቀቱን/ሰርቲፊኬቱን/ለመረከብ የሚያስችለው የሚጠበቅበትን ክፍያ ሙሉ ለሙሉ ከከፈለ በመሬቱ ላይ የፈለገውን የማድረግ መብት አለው።ሙሉ ለሙሉ ወይም ቀንሶ ለመሸጥ፣አሳልፎ ለመስጠት፣ወይም በማስያዝ ገንዘብ ለመበደር ይችላል።የሚሸጠው ቦታ በከተማ ውስጥ ከሆነ ግን የሚሸጠው ቦታ ከአራት መቶ(400) ካሬ ሜትር ማነስ የለበትም።

አንቀጽ 21- የመሬቱ መጠን እንዳለ ተከብሮ ይቆያል።ከሕጉ ውጭ መክፈልና መሰንጠቅ አይቻልም።

አንቀጽ 22- ገዢው እዳውን ከመክፈሉ በፊት ቢሞት ወራሹ ይከፍላል።ወይም ከመንግሥት ጋር በመነጋገር ዘዴ ይፈጥራል።ይህን ለማሟላት ካልቻለ በአንቀጽ ዘጠኝ በተጠቀሰው መሰረት መንግሥት ቦታውን ይወስዳል።በቦታው ላይ ቤት ተሰርቶበት ከሆነ ቤቱና መሬቱ ተሸጦ ከእዳው የተረፈው ገንዘብ ለባለቤቱ ገቢ ይሆናል።

አንቀጽ 23- የመሬቱ ወራሽ መሬቱን ለመካፈል ከፈለገ ይችላል።ሆኖም ግን ድርሻውን ከአራት መቶ(400)ካሬ በታች ለመቀነስ ከፈለገ የመንግሥት ፈቃድ ማግኘት ይኖርበታል።

አንቀጽ 24- ወራሽ ለመንግሥት የወረሰውን የመሬቱን ግምት ሁለት በመቶ(2%)መክፈል ይኖርበታል።

አንቀጽ 25- መንግሥት ለከተማው ልማትና እድገት አስፈላጊ ሆኖ ካገኘው መሬቱን በመውረስ ለባለቤቱ የመንግሥት ባለሙያዎች በወሰኑት መሰረት ካሳው ይሰጠዋል።

አንቀጽ 26- መንግሥት ለሥራ የሚፈልገው መሬት ካነሰ ወይም ስፋቱ ከሁለት ሜትር በታች ከሆነ መንግሥት ለባለቤቱ በቀድሞው የመሬት ዋጋ ተመን መሰረት ካሳ ይከፍላል።ሆኖም ግን ይዞታው ከአስር ዓመት በላይ ከሆነ የመንግሥት ባለሙያ በገመተው መጠን መሰረት ካሳ ይሰጣል።

አንቀጽ 27- በመሬቱ ላይ ህንፃ ከቆመበት መንግሥት የመሬቱን ግምት ይሰጣል።ወይም በስምምነት ሌላ ቦታ በምትክ እንዲያገኝ ይሆናል።

አንቀጽ 28- የንብረቱ ባለቤት የሆነ የውጭ አገር ዜጋ ቢሞት ወራሽና ታዛቢ ወይም ጉዳይ ፈጻሚ ከሌለው መንግሥት ቦታውን ወስዶ ያከራያል።ሆኖም ግን በማንኛውም ጊዜ ወራሽ ነኝ ባይ በሚቀርብበት ጊዜ መንግሥት

1.የመንግሥት ዕዳ ቢኖርበት

2.መንግሥት ለቦታው ማሻሻያ ያወጣው ገንዘብ ካለ

በመሬቱ ዋጋ ግምት ሁለት ከመቶ(2%)የሚከፈለው ግብር ተደምሮ ለመንግሥት ገቢ ይሆናል።

አንቀጽ 29- እስከ ሰላሳ ዓመት ድረስ ወራሽ ነኝ ባይ ካልቀረበ መንግሥት መሬቱን ይወስዳል።ያገባኛል ጥያቄም ሊነሳ አይችልም።

አንቀጽ 30- ሟች ወራሽ ከሌለው መሬቱ የመንግሥት ንብረት ይሆናል።

አንቀጽ 31- በመሬት ዙሪያ ለሚነሳ ጭቅጭቅና ውዝግብ ዳኛ በሕጉ መሰረት ፍርድ በመስጠት ጠቡን ሊያሶግድ ይችላል።ነገር ግን ያንን ለማድረግ የሚያግዝ ሕጋዊ አንቀጽም ሆነ ሕጋዊ መንገድ ከሌለ ዳኛ በመሰለው (ናፖሊዮኒክ)ይፈርዳል።

አንቀጽ 32- ይህ ሕግ በጽሁፍ በከተማው መጋቢና በአመቺ ቦታዎች ላይ ይለጠፋል።

ተጻፈ ጥቅምት 20 ቀን 1900 ዓ.ም.አዲስ አበባ

በዚህ አዋጅ ሕግ መሰረት በዓመቱ በእቅዱ ቀስቃሽ በሆኑት የውጭ አገር ተወላጆች በጃኮብ ማርና በፈረንሳዊው ሊዮን ሽፍኬ መሪነት በመሃንዲሱ ያውም እርዳታ የመጀመሪያው የአዲስ አበባ ቅየሳና ምዝገባ/ ካዴስትራል ሰርቬ/በ1909 ዓ.ም.ተጀመረ።ቀጥለውም ንጉሡ በአዲሱ ካደስትራል መሰረት የባለቤትነት መብት እንዲረጋገጥ አዘዙ።በትእዛዙም መሰረት በቅድሚያ

1ኛ.መሬቱ እርስት ወይም የግል ይዞታ መሆኑ እንዲረጋገጥ
2ኛ.ከቀድሞ ባለቤቱ ጋር የተደረገውን ውል የሚያረጋግጥ ማስረጃ እንዲቀርብ
3ኛ.በንጉሡ ወይም በቤተክህነቱ የተሰጠ ለመሆኑ የስጦታውን ማስረጃ ማቅረብ
4ኛ.ከባለ እርስቱ በውርስ ወይም በስጦታ የተወሰደ መሆኑን ማረጋገጥ

ይህ ከተሟላ በዃላ የመሬቱን ባለቤትነት የሚያረጋግጠው በአማርኛና በፈረንሳይኛ የተጻፈው የርስት ወረቀት የአጎራባቹ ዝርዝር በስዕል የተነደፈበት የምስክር ወረቀት ይሰጣል።

ይህን የምስክር ወረቀት ለማግኘት የበቃ የመሬት ባለቤት የቅየሳውን ዋጋ፣እንዲሁም በመሃንዲሱ በተገመተው ጠቅላላ የመሬት ዋጋ በሽህ ብር አምስት ብር እንዲከፍል መመሪያው ወጥቶ በሥራ ላይ ዋለ።

ይህ ዋስትና ከተረጋገጠ በዃላ የውጭ አገር ዜጎች ቤታቸውን በድንጋይ መሥራት ጀመሩ።አንድም የእንግሊዝ ኩባንያ ለውጭ ሰዎች መኖሪያ ሠፈር ለመሥራት/ለመገንባት/ፈቃድ በጠየቀ ጊዜ ዳግማዊ ምኒሊክ ቤቱ ከሚያርፍበት ቦታ ላይ ዙሪያው በስፋት የዛፍ ተክል እንዲያጠቃልል ትዕዛዝ ሰጡ።ከሕጋዊው ምዝገባ ጋር ተያይዞ የአቢሲኒያ ባንክ በ1905 ተቋቁሞ ግዴታውን ለሚያሟሉ ጠያቂዎቹ ለቤት መሥሪያ የሚሆን ብድር?ሞርጌጅ/ለመስጠት በቃ።

የውጭ አገር ሰዎች ሁኔታ

እንደተወላጁ በልማድ የውጭ አገር ዜጎች ቦታ የመያዝ መብት ነበራቸው።ሕንዶች፣ አውሮፓውያንና አርመናውያን በአገሪቱ ውስጥ ልዩ ልዩ ቦታ ይኖሩና መሬትም ይይዙ ነበር።ሆኖም ግን ከስጋት የተላቀቁ አልነበሩም።በ1901-1902 የነበረ አንድ ሚሲዮናዊ ሲናገር”በአውሮፓ እንደምናውቀው የመሬት /የንብረት/ትርጉም በኢትዮጵያ ውስጥ የለም።በአዲስ አበባ ውስጥ ቦታ ይዘው የተቀመጡትም ቢሆኑ በንጉሱ የተሰጣቸው መሬት በጊዜያዊነት የሚጠቀሙበት እንጂ በቋሚነት አይደለም”ሲል ተችቷል።

ለውጭ አገር ዜጎች የመሬት መግዛቱ መብት በልጅ እያሱ ጊዜ በ1910 ዓ.ም. ተሰረዘ።ኪራይም ከ30 ዓመት በላይ እንዳይሆን ታገደ።
ዶር.ሜራብ በ1908 ዓ.ም.ላይ እንደገለጸው፤-በከተማ ዋና ቦታ፣በገበያው ከባቢ በካሬ ሜትር ስሙኒ የሚያወጣው መሬት አንድ ብር ደረሰ፣ከከተማው ውጭ/ጠርዝ /ላይ በሚገኘው ከባቢ ግን ተመሳሳይ መሬት የብር አንድ አስራ ስድስተኛ (1/16 ብር) ከሰባት ሳንቲም በታች ማውጣቱን ሲገልጽ ፣አንድ ብር ያወጣ የነበረው መሬት ከ15 ዓመት በዃላ በ1923 ዓ.ም.አራት ብር መድረሱን ገልጿል።ቀጥሎም የአርመኑ ነጋዴ ጋራቤድ በ1929 ዓ.ም.የገበያው ከባቢ ከ5-8 ብር ድረስ ማውጣቱን፣ከከተማው ጠርዝ ደግሞ ከ50 ሳንቲም -አንድ ብር ማውጣቱን በመግለጽ በሃያ ዓመታት ውስጥ የዋጋው እድገት ከ8-32 እጥፍ መጨመሩን መስክሯል።ዶር.መረብም አስተያየቱን በመቀጠል አራትና አምስት ክፍል ያለው የአውሮፓውያን ቤት ከነበረንዳው የሚያሰራ ቦታ ከነአትክልት ጓሮው አንድ ሽህ ብር ሲያወጣ የቤቱም ኪራይ በወር ከ30-60 ብር ይደርስ እንደነበረ ገልጿል።

ከአጼ ሚኒሊክ ቀጥለው ለሶስት ዓመት ስልጣኑን ይዘው የነበሩት ልጅ እያሱ ሚካኤልም የከተማ ቦታንና መሬትን በሚመለክት የራሳቸው መመሪያ ነበራቸው።ከመመሪያቸው ውስጥ የውጭ አገር ድርጅትም ሆነ ዜጋ ከ30 ዓመት በላይ የመሬት ባለቤትነት መብት እንደማይኖረው የሚከለክል ነበር።

አፄ ሃይለሥላሴም የሚወክሉት ስርዓት ምንም እንኳን ከቀድሞው የተለዬ ባይሆንም ሥረመሰረቱ ያው የባላባታዊ ቢሆንም፣ አሳቸውም በየጊዜው ለሚነሳው የመሬት ጥያቄ ምንም እንኳን ስር ነቀል ባይሆንም በጥገና መልክ መልስ ለመስጠት ሙከራ አድርገዋል።በተለይም ሕዝቡን አስመርሮት የነበረውን ግብር በሚመለከተው ዙሪያ የሚከተለውን ማሻሻያ አዋጅ በ1940 ዓ.ም.አወጡ።

አንቀጽ 1- ማንኛውም የሚከራይ የከተማ መሬት ልኩ /መጠኑ/በካሬ ሜትር ይሆናል፣የገጠሩ መሬት ግን የሚመለከታቸው በሚስማሙበት ልኪት ይመጠናል።

አንቀጽ 2- የመሬቱ ግብር የመሬቱ ልማትና ሌላውም ታይቶ ሁለቱ አካላት በተስማሙበት መጠን ይሆናል።

አንቀጽ 3- አንድ የውጭ አገር ዜጋ ኮንተራቱ ባለቀ ጊዜ በመሬቱ ላይ ያሰፈረውን ቋሚ ንብረት /ቤትና ህንፃ/ለባለቤቱ ለመመለስ/በነፃ ለመስጠት/ከተስማማ የሚፈልገውን ያህል ህንፃ ሊገነባ ይችላል።ካልሆነ ግን ውሉና ገደቡ በቅጡ መቀመጥ ይኖርበታል።

አንቀጽ 4- ከሰላሳ ዓመት በላይ መከራየት አይቻልም።ሆኖም ግን መ ንግሥ ት ከፈቀደ ሊራዘም ይችላል።

አንቀጽ 5- በእርሻ ላይ የተሰማሩ የውጭ ዜጎች የተለመደውን /ተገቢ ው ን/አንድ አሥረኛ (1/10)ምርትና በተጨ ማ ሪ የገቢ ግብር መክፈል ግዴታው ነው።አስቀድሞ ፈቃድ ካልተሰጠ በስተቀር ምርቱን ወደ ውጭ አገር ሊልክ አይችልም።በምርቱ ላይ በአገሪቱ ሕግ መሰረት ቀረጥ ይጣልበታል።

አንቀጽ 6- ታሪካዊ ቅርስና የተፈጥሮ ሃብት የሚገኝበት መሬት የመንግሥት ሃብት ሲሆን እንዳጋጣሚ በውጭ አገር ተወላጅ ይዞታ ስር ከዋለ ው ጤ ቶቹን ያለፈቃድ በድብቅ ከአገር ሊያስወጣ አይችልም።መንግሥት ተከራዩ ያወጣ ው ን ወጭ ከፍሎ መሬቱን ይወርሳል።

አንቀጽ 7- በው ጭ አገር ዜጋ በያዘው ግቢ አቋርጦ የሚሄድ የመስኖ ውሃ ቢኖር ሊያግድና ሊከላከል አይችልም ።ሆኖም ግን በው ሃው ሊደርስበት የሚ ችል ጉዳት ካለ ካሳ ሊጠይቅና ሊያገኝ ይችላል።

አንቀጽ 8- መ ንግሥ ት ለገበያ፣ለቤተክርስቲያን፣ለወታደራዊ ተቋም፣ለባቡር ሃዲድና መንገድ፣ለተመሳሳይ አገልግሎት ሊውሉ የሚ ፈለጉ መ ሬቶችን ካሳ በመስጠት መ ው ረስ ይችላል።

አንቀጽ 9- የውጭ አገር ዜጋ በተከራየው መሬት ላይ የሚኖሩ ሰዎች ጋር ጭቅጭቅ ቢነሳ ጉዳዩ በአገሪቱ ሕግ መሰረት ይታያል።

አንቀጽ 10- ለማንኛው ም የኪራይ ው ል ማ ስፈጸሚ ያ ም ዝገባ መ ክፈል ሲገባው የመሬቱ ባለቤት ከዓመት ገቢው አንድ መ ቶኛ (1%)ግብር ይከፍላል።

አንቀጽ 11- የውሉ የጊዜ ገደብ ሲያበቃ አከራይና ተከራይ በሚ መ ርጣ ቸው፣በየእራስ ሁለት ተወካዮች በባለቤቱ ፈቃድ በመሬቱ ላይ የተሰሩትን ቤቶች የዋጋ ተመን ይመረምራሉ።አራቱ ለመ ስማ ማ ት ካልቻሉ አምስተኛ ሰው በመ ጨ መ ር ለሚ ያሳልፈው ውሳኔ ተገዥ ይሆናሉ።ውሳኔውም የመ ጨ ረሻና የጠ ና ይሆናል።ካለባለመሬቱ ፈቃድና እውቀት በውጭ አገር ዜጋው የተገነቡ ቤቶች ባለመሬቱ በግዥ መልክ ለማ ስቀረት ካልተስማ ማ እንዲፈርሱ ይደረጋል።/ይፈርሳል/

ከላይ እንዳየነው በአጼ ሃይለሥላሴ መንግሥት የተቀመጠው ደንብ በተለይም በውጭ አገር ተወላጆች ስለሚ ያዝ መሬት የወ ጣ ው ሕግ ከሃያ አምስት ዓመት በዃላ በደርግ ከወ ጣ ው ና አሁን ከ60 ዓመት በዃላ የህወሃት/ኢሕአዴግ ካወጣው የመሬት ስሪት ሕግ ጋር ሲነጣጠር ምን ያህል ለአገሪቱ ክብርና ለሕዝቡም ቅድሚ ያ የሰጠ እንደነበር ለመረዳት እንችላለን።ዃላ ቀር ተብሎ የሚጠራው ዘውዳዊ አገዛዝ አሁን ካለው የበለጠ ለአገሪቱ የሚ ቆረቆር ነበረ።በተራ ቁጥር አንቀጽ 5፣6፣7 ላይ የሰፈረውን ብንመለከት ለዚያ በቂ ማስረጃ ነው።የአሁኑ መሪዎች የአገሪቱን ለም መሬት በርካሽና በነጻ ለውጭ አገር ተባባሪዎቻቸው አሳልፈው ሰጥተዋልቸብችበዋል፤በመቸብቸብም ላይ ናቸው።የውጭ ምንዛሬ በሚል ፈሊጥ የአገር ቋሚ ንብረቶችና ጥሪቶች ለገባያ ቀርበዋል።

የልጅ እያሱና የቀዳማዊ ሃይለስላሴ መንግስት ለውጭ ዜጎች የመሬት መብት ከሰላሳ ዓመት አይበልጥም ነበር፤በአሁኖቹ ግን ዘጠና ዘጠኝ ዓመት ሆኗል።የመሬት ባለቤት ሕዝብ ሳይሆን መንግስት ሆኗል፡፤ሕዝብ የመ ንግስት ጭ ሰኛ ነው ማ ለት ነው።ሕዝብ በግዥና በውርስ ለብዙ ዓመታት የያዘውን መሬት ካለምንም ልዋጭ ና ካሳ እየተነጠ ቀ ሜ ዳላይ እንዲወድቅ ሆኗል።ተለዋጭም ቢሰጠው ጠፍና ከነበረው የመሬት መጠን በአስር እጅ ያነሰ ነው።ሌላው ዘዴ ነዋሪው በማይችለው የግንባታ ፕላን ማስጨነቅና ቦታውን በስበብ ባስባቡ ነጥቆ በማባረርና ለባለሃብት መሸጥ የመንግሥት ባለሥልጣኖቹ አንዱና ዋናው የገቢ ምንጭ ሆኗል። በስልጣን ላይ ያለው ቡድን ከአገሩ ደሃ ሕዝብ ይልቅ ዋስትና የሚ ሰጠ ው ና የሚ ጠ ቅመ ው የአግር ውስጥና የውጭ አገር ባለሃብቶችን ነው ። የወንዝና የመስኖ ውሃዎች እንዲበከሉ ወይም አቅ ጣ ጫ ቸውን እንዲቀይሩ፣የውጭ አገር ባለሃብቱ እንደሚ ፈልገው እንዲያዝባቸው ተፈቅዶለታል፡፤የሚ ያመ ርተው ንም ምርት ካለምንም ገደብና ቁጥጥር እንዲሁም ግብር ሳይከፈልበት ወይም ለይስሙላ ትንሽ ግብር ከፍሎ ወደ ፈለገው አገር አውጥቶ የመሸጥና የመጠቀም መብቱ ተጠብቆለታል። ሕዝቡ ግን የበይ ተመልካች ሆኖ፣የሚ መ ረተው ን ሳይቀምስ በርሃብ እንዲያልቅ ተፈርዶበታል።የምርት አቅርቦቱ በመመናመኑ የገባዬው ግሽበት ጣራ ነክቷል።ከሕዝቡ የመግዛት አቅም ጋር አይመጣጠንም።በወሬ ደረጃ ግን አገሪቱ ከ11% በላይ እድገት አምጥታለች እዬተባለ ይደሰኮራል።የሆቴሎች መስፋፋትና እዚህና እዚያ የተገተሩ ሕንጻዎች፣ጥራታቸውና ጥንካሬያቸው እንዲሁም አዝላቂነታቸው ያልተረጋገጠላቸው መንገዶችና ድልድዮች የመሸፈኛ ካባ ሆነው ሕዝቡንና የውጭውን ዓለም ሕዝብ እያደናገሩት ነው።እንደእውነቱ ከሆነ የሕዝቡ ኑሮ ያው በገሌ ነው።bb,ልቶ የማደሩ ሳይሆን እንደ ሰው በአገሩ መሬት ላይ የመኖሩ ዋስትናው በጎሳ ፖለቲካ ምክንያት አደጋና ፈተና ውስጥ ገብቷል።
ሕዝብ ቤት ሳይኖረው ብርድና ሙቀት፣ክረምትና በጋ እዬተፈራረቀበት ይኖራል።ይህም ኑሮ ሆኖ በጎሳ ማንነቱ ከኖረቤት ቦታ እየተፈናቀለና ደሳሳ ቤቱን እየተነጠቀና እየተመዘበረበት ካለበት ደረጃ ላይ ደርሰናል።አዲስ አበባ በደምና በላባቸው የመሰረቷት የኗሪዎቿ ሳትሆን፣በኢትዮጵያ ሕዝብ ሃብትና ወጭ የተገነባች መሆኗ ተዘንግቶ፣ የእኔ ብቻ ነው ባይ የጠባብ ጎሰኞች ወንበዴ የሚፈነጭባት ከተማ ሆናለች።

አዲስ አበባ የኢትዮጵያ ሕዝብ መዲና ነች!

አዲስ አበባ የአንድ ነጠላ ጎሳ ንብረት አይደለችም!!

የአዲስ አበባ ኑዋሪ መብቱ ይከበር!!!

አገሬ አዲስ

- Advertisement -Early Bird Holiday Deals! Before you know it, the holidays will be right around the corner! Take advantage of our early bird deals today and save up to $40 on our fees with code SPOT40!
Stay Connected
28,789FansLike
13,920FollowersFollow
8,540SubscribersSubscribe
Stacy Adams
Must Read
Related News

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here