ቦርከና
መስከረም 22 2011 ዓ.ም.
ኢንጅነር ክፍሌ ሆሮ የታላቁ ኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ስራ አስኪያጅ ሆነው ተሸሙ፡፡ የግድብ ስራ አስኪያጅ የነበሩት ኢንጂነር ስመኘው በቀለ ሞትን ተከትሎ ላለፉት ሁለት ወራት ኢንጂነር ኤፍሬም ወ/ኪዳን የግድቡን ግንባታ በጊዚያዊነት ሲመሩ ቆይተዋል፡፡
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሀይል ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈፃሚ ኢንጂነር አብርሃም በላይ (ዶ/ር) በትናንትናዉ ዕለት ለግድቡ ግንባታ ስራ አስኪያጅ እና ሁለት ምክትል ሥራ አስኪያጆች መሾማቻን የኢቲቪ ዘገባ ያመላክታል፡፡
በዚህም መሰረት ኢንጂነር ክፍሌ ሆሮ የታላቁ ኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ስራ አስኪያጅ እንዲሁም ኢንጂነር ኤፍሬም ወልደኪዳን እና አቶ ፍቃዱ ከበደ ምክትል ሥራ አስኪያጅች ሁነው እንዲሰሩ ተመድበዋል፡፡
የግድቡ ዋና ሥራ አስኪያጅ የነበሩት ኢንጂነር ስመኝው በቀለ ሐምሌ 19 ቀን 2010 ዓ.ም ማለዳ በመስቀል አደባባይ በሚያሽከረክሩት መኪና ውስጥ ሞተው ከተገኙ በኋላ የአሟሟታቸውን ዝርዝር ሪፖርት በሕዝብ ዘንድ በጉጉት ሲጠበቅ ቆይቶ፣ ዓርብ ጳጉሜን 2 ቀን 2010 ዓ.ም በፖሊስ ይፋ መደረጉ ይታወሳል፡፡
የተደረገው ሪፖርት ራሳቸውን ማጥፋታቸውን የሚያመላክት መሆኑን የፌደራል ፖሊስ ጀኔራል ኮሚሽነር ዘይኑ ጀማል በወቅቱ መናገራቸውን ተከትሎ አሟሟታቸው በህዝብ ዘንድ ይበልጥ መነጋገሪያ ሁኖ ቀጥሏል፡፡ መንግሥት ቀጣይ ምርመራዎችን በማድረግ ስመኘው (ኢንጂነር) ራሳቸውን ያጠፉበትንምክንያት ለህዝብ እንደሚያሳውቅም ቃል ገብቷል፡፡
መጋቢት 24 ቀን 2003 ዓ.ም ቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልላዊ መንግሥት ጉባ ተብሎ በሚጠራዉ አካባቢ የመሰረት ድንጋዩ ተጥሎ በአባይ ወንዝ ላይ የተጀመረዉ የሀይል ማመንጫ ግድብ የግንባታ ወጭ ሙሉ በሙሉ በኢትዮጵያ ህዝብና መንግሥት የሚሸፈን ነዉ፡፡
ግድቡ በሰባት አመታት ዉስጥ ተጠናቆ ኃይል ማመንጨት ይጀመራል ቢባልም ግንባታዉ በተባለለት ቀን እንደማይጠናቀቅና መጓተት እንደታየበት የተለዩ ዘገባዎች ያመለክታሉ።
በሰለሞን ይመር
___
ወቅታዊ እና ሚዛናዊ መረጃን ለማግኘት ቦርከናን በፌስ ቡክ ላይክ ያድርጉ።