ቦርከና
ጥቅምት 1 ፤ 2011 ዓ.ም
በትላንቱ ሚኒስትሮች ምክር ቤት ውሳኔ መሠረት የካቢኔ አባላት ቁጥር ላይ ማሻሻያ መደረጉንና በፌደራል የሚኒስትር መስራቤቶች ላይ የአደረጃጀት ለዉጥ መደረጉን ከጠቅላይ ሚኒስተር ፅ/ቤትየወጡ መረጃዎች ያመለክታሉ።
በዚህም መሰረት ከዚህ ቀደም 28 የነበረዉ የሚንስትሮች ምክር ቤት የካቢኔ አባላት ቁጥር ወደ 20 እንዲቀንስ መወሰኑን መረጃዉ አመላክቷል፡፡
በመሆኑም የተለያዩ አዳዲስ የሚኒስትር መ/ቤቶችና ተቋማት እንደሚዋቀሩ የተነገረ ሲሆን ከዚህበፊት በተለያዩ የሚኒስትር መስሪያ ቤት ስር ተካተዉ የነበሩ የስራ ክፍሎችና ዘርፎች በአዲስመልክ መደራጀታቸዉን ፅ/ቤቱ ገልጿል።
እንደ ፅ/በቱ መረጃ ከሆነ የንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር፣ የኢኖቬሽንና የቴክኖሎጂ ሚኒስቴር፤የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽ ሚኒስቴር፤ የሰላም ሚኒስቴር ፤የከፍተኛ ትምህርትና የሳይንስ ሚኒስቴር ፤የጉምሩክ ኮሚሽን የተሰኙ አዳዲስ የሚኒስትር መ/ቤቶችና ተቋማት እንደሚጨመሩ ታዉቋል፡፡
ረቂቅ አዋጁ በሚቀጥለው ሳምንት ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርቦ ይጸድቃል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን ይህን ተከትሎም በጠቅላይ ሚኒስትሩ አቅራቢነት የሚኒስትሮች ሹም ሽር እንደሚኖር ይጠበቃል።
በተጨማሪም የሚኒስትሮች ምክር ቤት የአስፈጻሚ አካላትን ስልጣንና ተግባር ለመወሰን በቀረበው ረቂቅ አዋጅ ላይ በትላንትናው ዕለት ተወያይቶ ማሻሻያዎችን በማከል ወደ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ማስተላለፉን ማሳለፉ ታውቋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ መንግስታቸዉ የሀገረቱን ሀብት በአግባቡ ለመጠቀምና ሀብትን ሰብሰብ አድርጎ ልማት በማዋል የመንግስትን ወጭ ለመቀነስ እንደሚሰራ በተደጋጋሚ ሲናገሩ ይሰማል፡፡
በተጨማሪም በትላንትናዉ ዕለት ከመገናኛ ብዙሀን ጋር በነበራቸዉ አጭር ቆይታ ተቋማትንና መስሪያ ቤቶችን በመቀነስ የሀብት ብክነትን በመከላከል የተሻለ እድገት ለማስመዝገብ እንደሚሰራ ገልፀዋል፡፡