ቦርከና
ጥቅምት 9 ፤ 2011
በፖሊስ ቁጥጥር ስር የዋሉንት የሰብአዊ መብት ተሟጋችና ጠበቃ ሄኖክ አክሊሉንና ጓደኛዉን ሚካኤል መላክን መንግስት ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ መፍታት አለበት ሲል አምንስቲ ኢንተርናሽናል አስታወቀ፡፡
ሁለቱ ግለሰቦች ረቡዕ ምሽት ተይዘው ሀሙስ ዕለት ፍርድ ቤት ቀርበዉ አዲስ አበባን የክልል ሰው አይመራትም በማለት ቅስቀሳ በማድረግና ከፍልስጤም ኢምባሲ ጋር በመገናኝት ስልጠና በመዉሰድ ክስ እንደተመሰረተባቸዉ አምንስቲ ትላንት ባወጣዉ መግለጫዉ አስፍሯል፡፡
ከሽብር ጋር በተያያዙ ወንጀሎች የተከሰሱ ሰዎች በመወከል ጥብቅና በመቆም የሚታወቀው ሄኖክ አክሊሉ የአዲስ አበባ ተወላጆች ማህበር ለማቋቋም እየተንቀሳቀሰ ካለዉ ጓደኛው ሚካኤል መላክ ጋር አዲስ አበባ ከሚገኘው ቢሮው በፖሊስ ተይዘዉ መታሰራቸዉን መግለጫዉ ያመለክታል፡፡
የኢትዮጲያ መንግስት የሀሳብ ነፃነትን ለማረጋገጥ ቁርጠኝነት ባሳየበት በዚህ ወቅት የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች አሁንም ተመሳሳይ ፈተና እያጋጠማቸዉ መሆኑን ያሳል ሲል አምንስቲ በመግለጫዉ ያነሳል፡፡
በመቀጠልም መግለጫዉ ሁለቱ ግለሰቦች በአፋጣኝ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ተፈተዉ ሀሳብን በነፃነት የመግለፅ ሰብዓዊ መብታቸዉን እንዲጠቀሙ ብሎም የመደራጀት መብታቸዉም እንዲከበር ያሳስባል፡፡
በሰለሞን ይመር