ጥቅምት 12 ፤ 2011 ዓ.ም.
በሰሜን ሽዋ ዞን ባለፉት ሁለት ቀናት በደረሱ ሁለት የትራፊክ አደጋ የ18 ሰዎች ህይዎት ማለፉን የዞኑ ፖሊስ መምሪያን ጠቅሶ ኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ድርጅት ዘግቧል፡፡
በትላንትናዉ ዕለት በአንጎለላና ጠራ ወረዳ ጨፋና ቀበሌ የህዝብ ማመላለሻ ሚኒባስ ከጭነት መኪና ጋር ዛሬ በመጋጨቱ የ12 ሰዎች ህይወት ማለፉን የዞኑ ፖሊስ መምሪያ የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ ምክትል ኮማንደር ወርቅአገኘሁ ሽዋ ለኢዜአ ተናግረዋል፡፡
አደጋውም ከቀኑ 6፡30 ላይ የደረሰው ከደብረብርሃን ከተማ ወደ አዲስ አበባ ይጓዝ የነበረ ኮድ 3-12315 አማ ሚኒባስ ከጫጫ ወደ ደብረብርሃን ይጓዝ ከነበረ ኮድ 3-00229 ጭነት መኪና ጋር በመጋጨቱ ነው፡፡
በአደጋው የሚኒባሱ አሽከርካሪ ህይወት ወዲያኑ ሲያልፍ የጭነት መኪናው ሹፌር ለጊዜው በመሰወሩ በፖሊስ ክትትል እየተደረገበት መሆኑን አመልክተዉ የሟቾች አስክሬን ወደየቤተሰቦቻቸው እየተላከ መሆኑንና ከባድና ቀላል ጉዳት የደረሰባቸዉ ሰዎች ደግሞ በደብረብርሃን ሪፈራል ሆስፒታል ህክምና እየተደረገላቸው መሆኑን ዘገባዉ ጠቁሟል፡፡
በተመሳሳይ እሁድ ዕለት ከቀኑ 10 ሰዓት ከ30 አካባቢ በሀገረማሪያም በደረስ የትራፊክ አደጋ የ6 ሰዎች ህይወት ማለፉን ኮማንደር ወርቅአገኘሁ አስታውቀዋል ሲል ኢዜአ ዘግቧል።
በአደጋው 11 ሰዎችም ከባድና ቀላል የአካል ጉዳት ደርሶባቸው በደብረ ብርሃን ሪፈራል ሆስፒታል የህክምና እርዳታ እየተደረገላቸው እንደሚገኝ ገልፀዋል።
በሰለሞን ይመር