spot_img
Monday, May 29, 2023
Homeነፃ አስተያየትኦነግ ሼኔ- "የንጉስ ልጅ" (በመስከረም አበራ)

ኦነግ ሼኔ- “የንጉስ ልጅ” (በመስከረም አበራ)

- Advertisement -

(በመስከረም አበራ)
ጥር 27 2011 ዓ.ም.

የተቀየረውን ኢህአዴግ ከከራሚው ኢህአዴግ የሚለየው አንድ ቁም-ነገር ለተቀናቃኞቹ የሚያሳየው ሆደ-ሰፊነቱ ነው፡፡ይህ አካሄዱ ብዙ የፖለቲካ ትርፍ የሚሰበስብበት አዋጭ መንገድ ነው፡፡ አዲሱ ኢህአዴግ ሊመሰርተው የሚሞክረው አካታች ፖለቲካዊ ንፍቀ-ክበብ አማራጭ ፖሊሲ ይዞ መጥቶ፣ ሰርቶ ለማሸነፍ ለተፈጠረ የፖለቲካ ሃይል ብቻ የሚመች ነው፡፡የወትሮው ኢህአዴግ ችኩል እና ጠላት ያለመናቅ አባዜ ትንሽንም ትልቁንም ጠላቱን ሲያስር ሲፈታ ሳያውቀው ለትንንሽ ጠላቶቹ የፖለቲካ ኪሎ ሲጨምር፣ የራሱን ኪሎ ደግሞ ሲያመናምን ኖሯል፡፡ራቅ አድርጎ የማያየው የአቶ መለስ ኢህአዴግ ዶሮም ነብርም የሚያክለውን ጠላቱን እኩል ሲያሳድድ እራሱን ግምት ውስጥ ከማስገባት አልፎ አይንህ ላፈር የሚያስብል ጥላቻን አትርፏል፡፡

ይህን ብልሃት እና ብስለት አልቦ፣በአመዛኙ ጫካ ቀመስ የአቶ መለስን ኢህአዴግ አጓጉል የፖለቲካ ጉዞ ሲያጤን የኖረው በለማ/ገዱ/ደመቀ/አብይ የሚመራው አዲሱ የለውጥ ሃይል የጠላትን ስም በመቀየር አዋጭ ጉዞውን ጀምሯል፡፡የአቶ መለስ/በረከት ኢህአዴግ ጠላት የሚላቸውን አካላት አዲሱ የለውጥ ሃይል ግን “ተፎካካሪ” በማለት በመሃከላቸው የነበረውን ውጥረት ስም በመቀየር ብቻ ማለዘብ ችለዋል፡፡የስም ለውጡን በተግባር ለማስመስከር የፖለቲካ ምህዳሩን በመክፈት፣ሚዲያዎችን ነፃ እንዲንቀሳቀሱ ትቷል፡፡ይህ ሁኔታ ለኢህአዴግ ትልቅ ጥቅም አለው፡፡አንደኛ ተፎካካሪ ፓርቲዎች ስለድክመታቸው ኢህአዴግን ተወቃሽ የማድረግ አካሄዳቸውን ያስቀርና ለድክመታቸው ተጠያቂነቱ/ሃላፊነቱ የራሳቸው እንዲሆን ያደርጋል፡፡ይህ የተቃውሞ ፖለቲካውን መንደር ለስራ እንዲነሳ ያስገድደዋል፤የእውነት ለሃገር የሚያስበው እና ለስልጣን ብቻ የሚቋምጠው፣በብቃት/በእውቀት የሚታገለው እና ተቃራኒው፣ምርት እና ግሩዱ ይለያል፡፡

እባብ ያየው ኦነግ ሼኔ

በዶ/ር አብይ የሚመራው የኢህአዴግ የለውጥ ቡድን ሆደ-ሰፊነት መጋረጃቸውን ቀዶ ገበናቸውን አደባባይ ካወጣባቸው ፓርቲዎች አንዱ በምዕራብ ወለጋ እንቀሳቀሳለሁ የሚለው የኦነግ ሼኔ ቡድን ነው፡፡በለውጡ ሃይል የበዛ ትዕግስት የተገለጠው የኦነግ ሼኔ አንዱ ገበና እድሜውን በሚመጥን መንገድ በሃገሪቱ እያታዩ ያሉ ፖለቲካዊ ለውጦችን ተረድቶ በዛው መንገድ ለመሄድ ያለመቻሉ ጉዳይ ነው፡፡እንደሚታወቀው ኦነግ በሽግግሩ ወቅት በተራ ፖለቲካ ሻምፒወኑ መለስ ዜናዊ መጥፎ በሆነ ሁኔታ የፖለቲካ ቁማር የተበላ ፓርቲ ነው፡፡

ይህ የፖለቲካ ቁማር ሽንፈት ምሬት ለዳኦድ ኢብሳ ትናንት የተደረገ ያህል የሚያንገበግብ ቁጭት ውስጥ የከተታቸው ይመስላል፡፡ ዳኦድ ኢብሳ መለስ ብለው ሲያስቡት የፖለቲካ ቁማሩ ሽንፈት የተጀመረውም የተጨረሰውም ኦነግ ወታደሮቹን ካምፕ እንዲያስገባ የተስማማ ቀን እንደሆነ ገብቷቸዋል፡፡ሊረዱ ያቻሉት ትናንት ዛሬ አለመሆኑን፣መለስ ዜናዊ የሚባል የተራ ፖለቲካ ቁማርተኛም ከአፈር በታች እንደሆነ ነው፡፡ዳኦድ የሽግግር ዘመኑ ላይ ቆመው ከመቅረታቸው የተነሳ ሌላው ቀርቶ አሁን በኢትዮጵያ መንበረ ስልጣን ላይ ያለው ኦሮሞ መራሹ ኦዴፓ መሆኑን እንኳን ያሰላሰሉት አይመስልም፡፡ሌላው የዘነጉት ትልቅ ጉዳይ የአቶ መለስ ቁማር አሳዛኝ ተሸናፊ ያደረጋቸው ወታደሮቻውን ካምፕ የማስገባት ያለማስገበት ጉዳይ በወቅቱ የሃገሪቱን ብሄራዊ ጦር ከማደራጀት ጋር የተያያዘ ግጥምጥሞሽ ዛሬ እንደሌለ ነው፡፡

እንደሚታወቀው ህወሃት/ኢህአዴግ አዲስ አበባን ሲቆጣጠር ለዘመናት የተገነባውን፣በስብጥርነቱ ሃገራዊ መልክ የነበረውን የሃገር ብሄራዊ ጦር ሰራዊት “የደርግ ወታደር ነው” በሚል ምክንያት በትኗል፡፡በተበተነው ጦር ምትክ ሃገራዊ ጦር ሰራዊት መገንባት የሃገሪቱን የሽግግር መንግስት የሚመሩ ዋነኛ የፖለቲካ ሃይሎች ፋንታ ሆኖ ነበር፡፡በሽግግር መንግስቱ አባልነት የተሰየሙ ቡድኖች ብዙ ቢሆኑም በጦር ታጅበው የመጡቱ ህወሃት/ኢህአዴግ እና ኦነግ ነበሩ፡፡ከድሮ እስከ ዘንድሮ ጦር ያነገበ በሚፈታት ሃገራችን ህወሃት እና ኦነግ ባለ ጦር በመሆናቸው ሁሉ በእጃቸው ሁሉ በእጃቸው ሆኖ ነበር፡፡እነዚህ ሁለት ሃይሎች የሃገሪቱን ብሄራዊ ጦር በማደራጀቱ ስራ ላይ ያላቸው ሚና የሃገሪቱ መፃኢ ፖለቲካ ለመዘወር ላለመዘወር ዋናው የይለፍ ነበር፡፡ብልጣብልጡ አቶ መለስ ኦነግን ያሸነፉት እና ለቀጣዮቹ ረዥም ዘመናት የፖለቲካ ሜዳውን ብቻቸውን ሊፈነጩበት የሚችሉበትን መላ የመቱት የህወሃት/ኢህአዴግ ጦር ላቅ ያለ ልምድ እና ብቃት ያለው በመሆኑ የሃገሪቱ ብሄራዊ መከላከያ ሰራዊት እንዲሆን፣በአንፃሩ የኦነግ ወታደር ትጥቁን ፈቶ ወደ ትንንሽ ወታደራዊ ካምፕ እንዲገባ ሲያደርጉ፣ኦነግም በዚህ ሲስማማ ነው፡፡

አቶ መለስ ይህን ያደረጉት በቀጣዮቹ አመታት ሃገሪቱን በሚያወሩለት ዲሞክራሲ ሳይሆን በጠመንጃ ጉልበት እንደሚመሯት አሳምረው ስለሚያውቁ ነው፡፡ለዚሁ እንዲመች ወታደራዊ አመራሩን ከላይ ታች በወንዛቸው ልጆች ሞሉት፡፡ወታደሩ “በለው!” ሲባል ያገኘውን በጥይት የሚደፋው ከደደቢት ጀምሮ በተፈተለ ጥብቅ ገመድ ከመለስ መንግስት ጋር ስለታሰረ ነው፡፡ከዚህ በኋላ አስቀድሞ በአቶ መለስ አእምሮ የተፃፈው የኦነግ አገልግሎት ስላበቃ የኦነግ አመራሮች በቦሌ እንዲሸኙ ተደረገ፡፡ይህን አቶ መለስን ወደ ኢትዮጵያ ፖለቲካ ሰገነት ከፍታ ኦነግን ወደ ስደት የዳረገ መበለጥ የዳኦድ ኢብሳ ኦነግ በተለይ ሊረሳው አልቻለም፡፡ሽግግር፣ድርድር፣ትጥቅ መፍታት የተባሉ ነገሮች በተከሰቱ ጊዜ ሁሉ ይሄው ሽንፈቱ ውል እያለበት ሳይቸገር አልቀረም፡፡ቁስሉ ያልዳነለት ሰው ያየው ሰው ሁሉ አቁሳዩ ይመስለዋል፣ማንም በተጠጋው ቁጥር ቁስሉ ይመረቅዛል፡፡ኦነግ እየሆነ ያለው እንዲያ ነው፡፡ስህተት ላለመድገም መጠንቀቄ ብሎት ሞቱን የሚያፋጥን ትልቅ ስህተት ውስጥ እየወደቀ ያለው ለዚህ ነው፡፡

ያ ሌላ ይሄ ሌላ

ከሃያ ሰባት አመት በፊት መለስ ዜናዊን ለመሰለ ሰው ያሳየው ፖለቲካዊ ገራምነቱ ያስበላው ኦነግ(ሼኔ) ዛሬ በገራሙ ዶ/ር አብይ/ አቶ ለማ መገርሳ ፊት ያለ ወቅቱ የአቶ መለስን መሰሪነት ወርሶ አጓጉል ብልጥ ለመሆን እየሞከረ ይገኛል፡፡ብልጥነቴ ብሎ የተያያዘውን ጉዞ አንድ ያለው ኤርትራ ድረስ ሄደው ለተደራደራቸው የአቶ ለማ መገርሳ ቡድን ህወሃትን ለመውጋት በምዕራብ ወለጋ የሰማራውን ሸማቂ ቡድን ደብቆ ኤርትራ ባለው ጦሩ ብቻ ለመደራደር ሲሞክር ነው፡፡ብረት አስቀምጨ በሰላማዊ መንገድ እታገላለሁ ብሎ ሲደራደር ኤርትራ ያለውን ጦሩን ትጥቅ ለማስፈታት ተስማምቶ ነው፡፡

ሆኖም ኦነግ ከድሮም በወለጋ አካባቢ ሲንቀሳቀስ ኖሯል፡፡ይህ ሃይል ህወሃት መራሹን ኢህአዴግ ለመጣል በተነሳው ህዝባዊ ተቃውሞ ወቅት ራሱን በወታራዊ ሃይልም ሆነ በፋይናንስ ለማሳደግ ችሏል፡፡በአሁኑ ሰዓት በኦሮሚያ፣በቤኒሻንጉል፣በደቡብ ክልል የተለያዩ ቦታዎች(አማሮ፣ቡርጅ፣ጌዲኦ፣ሰገን ዞኖች) አካባቢዎች እየተዘዋወረ ሰላም የሚነሳው፣በኦሮሚያ ባንክ የሚዘርፈው የኦነግ ሼኔ ቡድን ይሄው በሃገር ቤት በተለይ ደግሞ በምዕራብ ወለጋ አካባቢ ሲንቀሳቀስ የነበረው የኦነግ ሼኔ ቡድን አካል ነው፡፡ኦነግ ሼኔ ከነ አቶ ለማ ጋር በኤርትራ ባደረገው የሰላም ስምምነት በወለጋ ስለሚያንቀሳቅሰው ታጣቂ ቡድን ምንም እንዳላነሳ ነው የሚነገረው፡፡

ስለዚህ ድርድር ከአቶ ለማ መንግስት በኩል ግልፅ ነገር ያልተነገረ መሆኑ ነገሩን ይበልጥ እንቆቅልሽ ከማድረጉም በላይ ኦነግን ለብጥበጣ ሳይረዳው አልቀረም፡፡የድርድሩ ሁኔታዎች ለህዝብ ግልፅ አለመደረጉ አቶ ለማን (በግሌ ለመጠርጠር በሚቸግረኝ) የኦነግ ወገንተኝነት ጭምር ያስጠረጠራቸው ነገር ነው፡፡በርግጥ ኦነግ(ሼኔ) ከመስመር ወጥቶ ሰው መግደል፣ባንክ መዝረፍ የመሰሉ ተራ የውንብድና ተግባራት ላይ ጥልቅ ብሎ ከገባ በኋላ የአቶ ለማ ኦዴፓ ከኦነግ ሼኔ ጋር ያደረገው ድርድር ከሌሎች ብረት አንጋች ተቃዋሚወች ጋር ከተደረገው የተለየ እንዳልሆነ ደጋግሞ እየተናገረ ነው፡፡ሆኖም ይህ ነገር የአቶ ለማ ኦዴፓ ከኦነግ ጋር ሲደራደር ያደረገውንም ሆነ የፌደራል መንግስቱ ከታጠቁ ሃይሎች ሁሉ ጋር ሲደራደር ያደረገውን ግልፅነት የጎደለው አካሄድ ስህተትነት አይሸፍነውም፡፡

የታጠቁ ተቃዋሚ ሃይሎች ወደ ሃገር ቤት ሲጋበዙ የፌደራል መንግስቱ ጉዳዩን ለፓርላማ ውይይት አቅርቦ የድርድር ሁኔታዎችን ማስወሰን፣እግረ-መንገዱንም ሁኔታዎቹን ለህዝብ ግልፅ ማድረግ ነበረበት፡፡ይህ ባለመሆኑ ሳቢያ ነው በኦነግ ሼኔ በኩል ብዙ ችግሮች እየተከሰቱ ያሉት፡፡የድርድሩ ሁኔታ ግልፅ ባልሆነበት ሁኔታ ኦብነግ እና አርበኞች ግንቦት ሰባት ወደ ትክክለኛው መስመር ገብተው የሃገር ማረጋጋቱን ስራ በማገዝ ላይ ባሉበት ሁኔታ ኦነግ ሼኔ ለማረጋጋት መስራቱ ቀርቶ መበጥበጡን በመተው ሊተባበር አልቻለም፡፡ይህን የኦነግ ሁኔታ ዝም ብሎ በማየት ላይ ያለው የዶ/ር አብይ መንግስት አዝማሚያ ለሌላው ሰው ግራ አጋቢ ሲሆን ለኦነግ ሼኔ ደግሞ የሰፈሩ ሰዎች የሃገሪቱን ስልጣን በመቆጣጠራቸው የፈለገውን ለመሆን የተፈቀደለት የንጉስ ልጅ አድርጎ ራሱን እንዲቆጥር ሳያደርገው አልቀረም፡፡

ኦነግ ሼኔ አሁን እያደረገ ያለውን ብጥበጣ የሚያደርገው የሃገሪቱ መንግስት በትግራይ መኳንንት በሚዘወርበት ዘመን እንደ ቂል ተሸናፊ ተቆጥሮ መናቁ ልክ እንዳልሆነ፣ ይልቅስ አስፈሪ፣ጉልበታም፣ጦረኛ መሆኑን ለማሳየትና ስም ለመቀየር ነው፡፡ ኦነግ ሼኔ የረሳው ነገር የአሁኑ የኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ዘመን ከተኳሽነት ይልቅ ታጋሽነት ጀግና የሚያስብልበት መሆኑን ነው፡፡ ከዚህ አንፃር እንደ ኦነግ ሼኔ ከዘመን ጋር የሚተላለፍ አሳዛኝ ፓርቲ ያለ አይመስለኝም፡፡ ጦር ዋና በሆነበት ዘመን ጦሩን ለመለስ ዜናዊ አስረክቦ፤ዛሬ የሰላም ያለህ በሚባልበት ጊዜ “ተኳሽ ነኝ!” ማለት ከዘመን ጋር ክፉኛ መተላለፍ ነው፡፡

ማለባበስ ይቅር

የዳኦድ ኢብሳ ኦነግ (ሼኔ) በሰላም ለመታገልተስማምቼ መጣሁ ብሎ አዲስ አበባን ከረገጠበት ሰሞን ጀምሮ በችግር ፈጣሪነት ስሙ እየተነሳ ነው፡፡ከቡራዩው አሰቃቂ፣አስከፊ እና አሳዛኝ ግድያ እስከ ዛሬው የሰገን ግድያ ድረስ የኦነግ ስም ይነሳል፡፡የኦነግ “መሳሪያየን እንዳዘልኩ ለሰላማዊ ምርጫ ልወዳደር” እንደ ማለት የሚቃጣው ክርክር ሰሚን ሁሉ ሲያስቅ የሰነበተ ነገር ነው፡፡ዋል አደር ብሎ በባንክ ዘረፋ ላይ እንደተሰማራም እየተዘገበ ይገኛል፡፡ ኢሳት እና ዋዜማ እንደዘገቡት ኦነግ አስር ቀን ባልሞላ ጊዜ አስራ ሰባት ባንኮችን ዘርፈፏል፡፡

ሌላው የዳኦድ ኢብሳ ኦነግ አስቂኝ ነገር “ከዛሬ ሃያ ምናምን አመት በፊት በሃገሪቱ ምርጫ ቦርድ ባህር መዝገብ ውስጥ የታወቅኩ ፓርቲ ስለሆንኩ ድጋሜ በምርጫ ቦርድ መመዝገብ አያስፈልገኝም” ያለው ነገር ነው፡፡አንድ ፓርቲ በሃገሪቱ ምርጫዎች በተከታታይነት ካልተሳተፈ እንደሌለ የሚቆጠር ሆኖ እንደገና መመዝገብ እንዳለበት ማወቁ የአንድ አዛውንት አመት በትግል ላይ ለኖረው ኦነግ ቀርቶ ለሌላውም ቀላል ነገር ነው፡፡በተጨማሪ የዛሬ ሃያ ምናምን አመት የነበረው ኦነግ በትንሹ ወደ አምስት ክልፋዮች ተቀይሯል፡፡እንዲህ ግዙፍ ለውጥ በላዩ ላይ የተካሄደበት ኦነግ አንዱ ስንጣሪ ታዲያ በድሮው ኦነግ ስም መመዝገቤ ከእሩብ ምዕተ አመት በኋላ ለብዙ ተሰነጣጥቄ ስመለስም የሚሰራ ነገር ነው ብሎ ማሰቡ ግራ የሚያጋባ ነገር ነው፡፡

የኦነግ መቅበጥበጥ እና የመንግስት የበዛ ትዕግስት በተለይ ኦሮሞ ባልሆነው ሰው ዘንድ ጥርጣሬ እየፈጠረ ይገኛል፡፡በሃገሪቱ ዳርቻ ታጥቆ እየተንጎማለለ ልቡ በል ባለው ሰዓት የሚተኩሰውን ኦነግ ሼኔን እመራለሁ የሚሉትን አቶ ዳኦድ ኢብሳን አዲስ አበባ ላይ ቁጭ አድርጎ ማኖሩ በተለይ ኦዴፓ መራሹን መንግስት ለትዝብትም ለጥርጣሬም ዳርጎታል፡፡የሚብሰው ደግሞ ከሰሞኑ ፍሪዳ ተጥሎ ከኦነግ ሼኔ ጋር ኦዴፓ አደረገው የተባለው እርቅ ነገር ነው፡፡አስታራቂዎቹ ኦነግ ባንክ ሲዘርፍ፣እየተዟዟረ ሰው ሲገድል አንዳች ማለት ያልቻሉት አባገዳዎች እና የኦሮሞ ሽማግሌዎች ናቸው፡፡ሽማግሌዎቹ ኦነግ በብዙ ሲያጠፋ ዝም ብለው ከኦዴፓ ጋር እናስታርቅ ባሉበት መድረክ ኦሮሞ ለኦሮሞ መጣላት እንደሌለበት ሲማፀኑ ተደምጠዋል፡፡ኦነግ ሼኔ ከኦሮሚያ ክልል ወጥቶ ኦሮሞ ያልሆኑ ዜጎችን በጥይት መቁላቱ ለሸምጋዮቹ የሚሰጠውን ትርጉም ያወቀ የለም!ከሁሉም በላይ አሁን ኦነግ ሼኔ እያጠፋ ያለውን ጥፋት አርበኞች ግንቦት ሰባትም ሆነ ኦብነግ ቢያደርጉት ኖሮ ከመንግስት ተመሳሳዩ ትዕግስት ይኖር ነበር የሚለውን መጠየቅ እሻለሁ፡፡የአዲስ አበባ ወጣቶችን ያለ ጥፋታቸው እያፈሰ ያሰረው የዶ/ር አብይ መንግስት በባለ ብዙ ጥፋቱ በኦነግ ላይ ተመሳሳዩን ለማድረግ ለምን እንደተቸገረ ግልፅ አይደለም፡፡

አጥፊውን ኦነግ ሼኔን አርዶ ጋርዶ የታረቀው የአቶ ለማ ኦዴፓም ቢሆን ከዚህ ቀደም ሲሸማገል የቆየ እና “አሁን ትዕግስቴ ስላለቀ የሃይል እርምጃ ወስጄ የኦነግ ሼኔን የወለጋ አምባ እያፈራረስኩ ነው” ሲል የሰነበተ ነበር፡፡”ትግስቴ ስላለቀ ወታደራዊ እርምጃ ጀምሬያለሁ” ያለው ኦዴፓ በመሃል ደግሞ “ልታረቅ” ማለቱ ክፉ ነገር ባይሆንም ለእርቅ ሲቀመጥ እርቁ የሚፈታው ነገር ምንድን ነው የሚለውን ትልቅ ጥያቄ አለመመለሱ አጠያያቂ መሆኑ አይቀርም፡፡እርቅ የሚጠላ ነገር አይደለም፡፡ሆኖም ከኦነግ ጋር የሚደረግ እርቅ መልክ ሊያስይዛቸው የሚገባ ጉዳዮች አሉ፡፡

አንደኛው በምዕራብ ወለጋ ያሰማራቸው ታጣቂዎች በአነግ ሼኔ ሰላማዊ ትግል ላይ ያላቸው ሚና ምን እንደሆነ ቁርጥ አድርጎ ማሳወቅ አለበት፡፡ከቁጥራቸው ጀምሮ፣ትጥቅ አውርደው ካምፕ የሚገቡበትንም ሆነ ሌላ ሁኔታ ካለ የዚህን የጊዜ ገደብ በውል ማሳወቅ አለበት፡፡በተጨማሪም ከባንክ ዘረፈ የተባለውን ገንዘብ መጠን ተገልፆ፣ በአስቸኳይ ይቅርታ ጠይቆ እንዲመልስ መደረግ አለበት፡፡ካልሆነ ነገ ኦነግ ሼኔም እንደ ህወሃት “ስታገል የቋጠርኩት የግል ጥሪቴ ነው” ብሎ ከሃገሪቱ ባንኮች በዘረፈው ገንዘብ ኦሮሟዊ ኢፈርት ልመስርት ሊል ይችላል፡፡ከሁሉም በላይ መንግስት ሆኖ ሃገር የሚመራ አካል ባንክ ከዘረፈ ብድን ጋር በድፍኑ ታርቄያለሁ ማለቱ የሚያስተላልፈው መልዕክት ሌብነትን ማውገዝ ሊሆን አይችልም፡፡ይህ ነገር ተጨማሪ የባንክ ዘራፊወችን ሊፈጥር እንደሚችል ማሰብ ያስፈልጋል፡፡የድሃን ሃገር ገንዘብ የወንበዴ ሲሳይ እያደረጉ በየምዕራብ ሃገሩ ምፅዋት መለመኑ ምን ትርጉም አለው?
ሁለተኛው ነገር ከኦነግ ጋር የተደረገው እርቅ ፓርቲው ነውጠኝነቱን በሰላማዊነት ተክቶ፣ከሃያ ሰባት አመት በኋላ በላዩ ላይ የተከሰተውን ለውጥ አጢኖ በአዲስ መልክ በምርጫ ቦርድ ለመመዝገብ ዝግጁ መሆኑን ያረጋገጠ ነው ወይ የሚለው ነው፡፡”ማን ትጥቅ ፈቺ ማን አስፈቺ ሊሆን ነው” ያለው ኦነግ ሼኔ “እኔን ልመዝግብህ የሚል ደፋር ምርጫ ቦርድ ማን ነው” እንደማይል እርግጠኛ መሆን አይቻልም፡፡

ሌላው እና ዋነኛው ነገር የኦነግ ነገር የኦሮሚያ ጉዳይ ብቻ ባለመሆኑ ጉዳዩ የሚመለከተው ተደራዳሪ ኦዴፓ ብቻ መሆን የለበትም የሚለው ነው፡፡ኦሮሞን ነፃ ለማውጣት እታገላለሁ የሚው ኦነግ ሼኔ ውጅግራውን አንግቦ የሚንቀሳቀሰው በኦሮሚያ ምድር ብቻ አይደለም፡፡ይልቅስ ኦሮሚያን በሚያጎራብቱ ክልሎች እየዘለቀ የንፁሃንን ሰዎች ህይወት እያጠፋ ይገኛል፡፡በዚህ ምክንያት የአጎራባች ክልሎች መንግስታትም በኦነግ አደብ መግዛት ዙሪያ ሊነጋገሩ እርቅ ካስፈለገም ሊታረቁ ያስፈልጋል፡፡ኦነግ ከኦሮሚያ በተጨማሪ የደቡብ ክልልን እና ቤኒሻንጉል ክልሎችን እያመሰ ይገኛል፡፡ይህ ማለት ደግሞ የፌደራል መንግስቱም በእርቅ ድርድሩ ውስጥ ሊወከል ያስፈልጋል ማለት ነው፡፡ለእርቅ ሲቀመጡ እንዲህ ያሉ ወሳኝ ጉዳዮችን ሳይነካኩ በየወሩ ፍሪዳ እያረዱ መታረቅ የሚፈይደው ነገር አይኖርም፡፡ለዚህ ምስክሩ ኦነግ እና ኦዴፓ ታረቁ በተባለ ማግስት ኦነግ ሼኔ በደቡብ ክልል ሰገን ዞን ዘልቆ ሃገር ሰላም ብለው የሚጓዙ አራት የኮሬ እና አማሮ ወጣቶችን ከመኪና ላይ በአሳዛኝ ሁኔታ ህይወታቸውን መቅጠፉ ነው፡፡

____
ማስታወሻ:በዚህ ጽሁፍ ላይ የተንጸባረቁ ሳሃቦች የጸሃፊውን/የጸሃፊዋን እንጂ የድረገጹን አቋም አያንጸባርቁም። ነጻ አስተያየት ወይንም ሃሳብ በዚህ ድረ ገጽ ለማውጣት ጽሁፍዎትን በ info@borkena.com ይላኩልን።

- Advertisement -Early Bird Holiday Deals! Before you know it, the holidays will be right around the corner! Take advantage of our early bird deals today and save up to $40 on our fees with code SPOT40!
Stay Connected
28,789FansLike
12,864FollowersFollow
8,540SubscribersSubscribe
Stacy Adams
Must Read
Related News

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here