spot_img
Thursday, November 30, 2023
Homeነፃ አስተያየት"የዶሮ ሻኛ አምጣ" የሚባለው ኤርሚያስ አመልጋ(በመስከረም አበራ)

“የዶሮ ሻኛ አምጣ” የሚባለው ኤርሚያስ አመልጋ(በመስከረም አበራ)

advertisement

(በመስከረም አበራ)
የካቲት 19ቀን 2011 ዓ.ም.

ኢትዮጵያችን በፖለቲካ ጣሯ ላይ የኢኮኖሚ ደዌ የደረበች ጎስቋላ ሃገር ነች፡፡”አፍርሻት ልፍረስ” የሚለው የፖለቲካ ዛሯ ተሻለው ሲባል የሚብስበት መሆኑ ብቻ አይደለም ክፋቱ-ኢኮኖሚዋንም ይዤ ልሙት ማለቱ እንጅ፡፡ፖለቲካ እና ኢኮኖሚ ሲጠፉም ሲለሙም አብረው የሆኑ መንትያዎች በመሆናቸው አንዱን ለይቶ ጤናማ ማድረግ አይቻልም፡፡ፖለቲካው ካለመፈወሱ የተነሳ ኢኮኖሚውም እንዲሁ በህመም ላይ ይገኛል፡፡ፖለቲካውን የተጣባው ዘረኝነት ፣ኢፍትሃዊነት፣ሴረኝነት ፣ማስሰመሰል፣እውቀት አልቦነት ሁሉ በኢኮኖሚው ላይም ይንፀባረቃል፡፡ነግዶ ለማትረፍ፣ተናግሮ ለመሰማት፣ወጥቶ ለመመግባት ወሳኙ ነገር መርጠን ያልተገኘንበት ዘር፣መቼ መናገር እንደ ጀመርን እንኳን የማናውቀው ቋንቋ ሆኗል፡፡

እንዲህ ባለው እጅግ ኋላቀር የፖለቲካ ከባቢ ውስጥ የኢኮኖሚ እድገት ከማምጣት ግመል በመርፌ ቀዳዳ ብትሾልክ ይቀላል፡፡በውስብስቡ ድህረ-ዘመናዊ ዘመን እየኖርን በቅድመ-የድንጋይ ዘመን ነጠላ የኑሮ ዘይቤ መኖር መርጠናል፤የሰው ነጠላ ማንነቱ የሚናገረው ቋንቋ ብቻ ይመስለናል፡፡ስለዚህ አሁን ያለንበትን ውስብስብ ዘመን የሚመጥን ፖለቲካ እና ኢኮኖሚ እንዲኖር የሚፈልጉ ሰዎችን እስከ አድማስ ዳርቻ እናሳድዳለን፡፡ህልማቸውን፣አበርክቷቸውን፣ወደፊት ደግሞ ሊጠቅሙ የሚችሉትን አስበን መንገዳቸውን ከማቅናት ይልቅ ትንሳኤ የሌለው ሞት እንዲሞቱ እንሰራለን፡፡ይህን ለማድረግ ደምባደምቦችን፣መመሪያዎችን እንደገፋለን፡፡ፖሊሲዎቻችን፣ህጎቻችን እንዴት እንደሚሳካ ሳይሆን እንዴት እንደማይሳካ ይደነግጋሉ፡፡አለማስቻልን በህግ ደንግገን እንኖራለን፡፡ይህን ጉዳይ በተግባር የሚያሳይ አንድ ገጠመኜን ላጋራ፡፡

በቅርቡ ቪዥን ኢትዮጵያ በአዲስ አበባ ባዘጋጀው የጥናት መድረክ ተገኝቼ ነበር፡፡የአዲስ አበባን የትራንስፖርት ችግር የማቃለል ስራ ለመስራት ከአሜሪካን ሃገር የመጣ አንድ ወጣት በዚሁ ጉዳይ ላይ ስላሉ ችግሮች ጥናት ሊያቀርብ ተገኝቶ ነበር፡፡ስራውን ለመስራት ወደ ተግባር ሲገባ የገጠመውን በመመሪያ እና ደምባደምብ የተጠቀለለ መሰናክል ሲያቀርብ መስማት ራሱ ራስ ያዞራል፡፡ልጁ በጥናቱ የሃገራችንን በህግ፣መመሪያ እና ምባደምብ የተደገፈ ያለማስቻል ከባቢ ከሌሎች ሃገሮች ጋር እያወዳደረ ሲያቀርብ ሁለት ውስጤ የቀሩ ለአንባቢም ላጋራ የምወደውን ምሳሌዎችን አመጣ-የፌስ ቡክን እና የማይክሮ ሶፍትን ጉዳይ፡፡

ፌስቡክን እና ማይክሮ ሶፍትን የፈጠሩ ስራ ፈጣሪዎች (ማክዙከምበርግ እና ቢልጌትስ) ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ኢትዮጵያዊያን ቢሆኑ ኖሮ አንድ እርምጃ ሳይራመዱ በደምባደምብ ዱላ እግራቸውን ተቀልጥመው እንደሚቀሩ አስረዳን፡፡ነገሩ እንዲህ ነው የኢትዮጵያ ህግ አንድ ሰው የሆነ ሥራ ለመስራት ፈቃድ ለማግኘት በሚሰራበት ስራ የመጀመሪያ ዲግሪ ሊኖረው ያስፈልጋል ይላል፡፡በተጨማሪ በድሃዋ ሃገራችን ኢትዮጵያ አንድ ስራ ለመጀመር መንግስት እንዲፈቅድለት ስራ ፈጣሪው ምን የመሰለ ቢሮ፣ከነ ሙሉ ቁሳቁሱ ማሳየት ግድ ይለዋል፡፡ማክከምበርግ አና ቢልጌትስ ደግሞ ከሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ ሳይመረቁ አቋርጠው የወጡ፣ሥራ ሲጀምሩ ቢሮ የሚባል ነገር ያልነበራቸው ሰዎች ናቸው፡፡ስለዚህ የፌስቡክንም ሆነ የማይክሮ ሶፍትን ሃሳብ ያመጣው ሰው ኢትዮጵያ ውስጥ የሚኖር ኢትዮጵያዊ ቢሆን ኖሮ ፌስቡክ እና ማይክሮ ሶፍት የሚባሉ ካምፓኒዎች በዓም ላይ አይኖሩም ነበር ሲል ጥናት አቅራቢው በቀላል ምሳሌ የሃገራችንን ከድህነት ጋር በህግ መተሳሰር በደምብ አስረዳን፡፡

በሃገራችን የሚወጡ ህጎች፣መመሪያዎች እና ደምቦች ሃገሪቱን በሚመራው ካድሬ የእውቀት ልክ የተሰፉ ናቸው፡፡ከካድሬ እውቀት አድማስ ሻገር ያለ ነገር ያመጣ ሰው ሃሳብህ ከህግ ማዕቀፍ ውጭ ስለሆነ የምናስተናግድበት ህግ፣መመሪያ እና ደምብ የለንም እና ሃሳብህን ይዘህ ቁጭ በል ወይ ወደ መሄጃህ ሂድ ይባላል፡፡በዚህ ላይ ሃሳቡን ያመነጨው ሰው የተወለደው “ከትምክህተኛ” ይሁን “ከጠባብ” ዘር መሆኑ ደግሞ ዋናው ነገር ነው!በዚህ ምክንያት ሃገራችን ሃሳብ ያለው ሁሉ መጥቶ አይቷት ላይመለስ ጥቁር ድንጋይ ወርውሮባት የሚሄድ ሃገር ሆናለች፡፡የሆላንድ ካርስ ባለቤት፣የኢትዮጵያ አማልጋሜትድ ሊሚትድ ባለቤት አቶ ገብረየስ ቤኛ ሃገራችን ካስመረረቻቸው ባለሃብቶች እና ስራ ፈጣሪዎች መካከል ናቸው፡፡እነዚህ ሰዎች ሃገራችን የታሰረችበት ለእድገት የመይመች ትብታብ አላላውስ ሲላቸው ነገር አለሙን ትተው ስደትን የመረጡ ሰዎች ናቸው፡፡የልብ ሃኪሙ ዶ/ር ፍቅሩ ማሩም ሌላ ተጠቃሽ ሰው ናቸው፡፡

ሌላው የካድሬ ፖለቲካ መረብ እጅግ ካወካቸው ሰዎች ውስጥ ተጠቃሹ ታዋቂው ስራ ፈጣሪ አቶ ኤርሚያስ አመልጋ ናቸው፡፡አቶ ኤርሚያስ ከዓመታት በፊት ወደ ሃገራቸው በመጡበት ወቅት ያዩት የሃገሪቱ ኋላቀርነት እዚሁ ቀርተው እውቀት ልምዳቸው በሚችለው አቅም የሃገር እድገት ለማገዝ በድንገት እንደወሰኑ ተናግረዋል፡፡በሃገር ውስጥ ቆይታቸው የሰሯቸው የስራ ፈጠራዎች በሃገሪቱ ተሰርተው የማያውቁ አዳዲስ ሃሳቦችን የያዙ ችግር ፈቺ ስራዎች ናቸው፡፡ስራ ፈጠራ ከችርቻሮ ንግድ የሚለይ መሆኑን በተግባር ያስመሰከሩ ሰው አቶ ኤርሚያስ ናቸው ቢባል ማጋነን አይሆንም፡፡በሃገሪቱ ለዘመናት ሲፈስ የኖረውን የምንጭ ውሃ አሽጎ ለአገልግሎት የማዋልን ሃሳብ ለመጀመሪያ ጊዜ ያመጡት አቶ ኤርሚያስ ናቸው፡፡አሁን ከሰማኒያ የሚልቁ ውሃ አሽጎ ሻጭ ነጋዴዎች በሃገራችን ችርቻሯቸውን ሲያጧጡፉ የስራው ጀማሪ አቶ ኤርሚያስ ከስራው እጣ ፋንታ እንዲያጡ ተደርገዋል፡፡ለዚህ ደግሞ የተለያዩ ስም ማጥፋቶች እና ቢሮክራሲያዊ ጦርነቶች ተደርጎባቸዋል፡፡

በግላቸው በቢዝነሱ ዓለም ያላቸውን እንቅስቃሴ ለማሳለጥ ሲንቀሳቀሱ በባንክ ኢንዱስትሪው ላይ ያስተዋሉትን እጅግ የተንቀራፈፈ ኋላ-ቀር አሰራር ተመልክተው ዝም ብሎ ከማማረር ይልቅ ዘርፉን ለማዘመን የበኩላቸውን ለማበርከት በመወሰን ዘመን ባንክን መሰረቱ፡፡ዘመን ባንክን ሲመሰርቱ በአንድ ቅርንጫፍ ተገልጋይ ያለበት ድረስ በመሄድ አገልግሎት የመስጠት እና ሌሎች ዘመናዊ የባንክ አሰራሮችን ለማስተዋወቅ ነበር ህልማቸው፡፡አቶ ኤርሚያስ አመልጋ ዘመን ባንክን በመመስረታቸው ብዙ ግፍ የደረሰባቸው ቢሆንም ሰውየው ወደ ባንክ ኢንዱስትሪው ፊታቸውን በማዞራቸው ብቻ በሚገርም ሁኔታ የሃገራችን የባንክ ኢንዱስትሪ እንዲዘምን ረድተዋል፡፡

አቶ ኤርሚያስ ወደ ባንክ ኢንዱስትሪው ከመግባታቸው በፊት የሃገራችን ባንኮች ምሳ ሰዓት ላይ ይዘጋሉ፣ከዘጠኝ ሰዓት በኋላ የውስጥ ስራ ስለምንሰራ ለደምበኛ አገልግሎት አንሰጥም ብለው መስኮት በራቸውን ጠርቅመው ይቀመጡ ነበር፡፡ቅዳሜ አይሰሩም፣ማታ መስራት አይታሰብም፡፡የመክፈያ መንገዳቸው በቢሯቸው መስኮት ላይ ሰው አሰልፎ ገንዘብ ማደል፣ቢበዛ ቼክ ፅፎ መስጠት ነበር፡፡ቅዳሜን ጨምሮ በምሳ ሰዓት መስራትን፣በመስኮት አስልፎ ከመክፈል ባለፈ ደምበኛው ድረስ ወርደው የሚደረጉ የተለያዩ ቀልጣፋ የክፍያ አይነቶችን(ለምሳሌ እነ ኤም ብር አይነት) በስራ ላይ የማዋልን ሃሳብ ያመጡት አቶ ኤርሚያስ አመልጋ ናቸው፡፡ዘጠኝ ሰዓት ላይ የውስጥ ስራ ለመስራት በሚል ለደምበኛ ይከረቸሙ የነበሩት የባንክ ቤት በሮች የተከፈቱት አቶ ኤርሚያስ ለዘመን ባንክ አሰራር ካመጡት ዝመና ጋር አብሮ ለመራመድ ነው፡፡አሁን የእስር ድግስ እየተገሰላቸው በነበረበት ሰሞን ደግሞ አቶ ኤርሚያስ አሊባባ ከተባለው ታዋቂ ኩባንያ ጋር በመተባበር ማንም ያላሰበውን የኢ-ፋይናንስ አሰራርን በሃገራችን ለማስተዋወቅ እየጣሩ ነበር፡፡ይህን ህልማቸውን እንዳረገዙ ነው እስርቤት የተወረወረሩት፡፡

በሪል ስቴት ኢንዱስትሪው በኩልም ቢሆን አቶ ኤርሚያስ ያበረከተው አዲስ ነገር አለ፡፡ከከተማ ዳር ወጥቶ ቪላ ቤት አንጣሎ መኖርን የሚችል አቅም ለሌላቸው፣ከሃገር ሳይወጡ መሃል ከተማ ላይ አፓርትመንቶችን ሰርቶ ለተጠቃሚ በተመጣጣኝ ዋጋ የማቅረብን ሃሳብ አመንጭተው ስራ የጀመሩ የመጀመሪያው ሰው አቶ ኤርሚያስ ናቸው፡፡ሥራ ፈጣሪው ይህን ሲያስቡ ለራሳቸው መኖሪያቤት የሌላቸው በኪራይ ቤት የሚኖሩ እንደሆኑ ተናግረዋል፡፡የቸርቻሪ ነጋዴ እና እንደ አቶ ኤርሚያስ ንግድን በእውቀት የሚያስኬድ ስራ ፈጣሪ ልዩነታቸው ይህ ነው፡፡ቸርቻሪ ነጋዴዎች ለደምበኛ የመኖሪያ ቤት የሚያቀርብ ንግድ ውስጥ የሚገቡት ለራሳቸው እና ለልጅ ልጆቻቸው አንድ ቀበሌ የሚያክል ግዛት ላይ ቤተ-መንግስት የሚመስል ቤት ከደረደሩ በኋላ ነው፡፡እንዲህ ያሉት “ራስ ደህና” ባይ ነጋዴዎች እስርም፣ክስም አጠገባቸው አይደርስም፡፡በአንፃሩ ስራ ፈጣሪው አቶ ኤርሚያስ የዶሮ ሻኛ አምጣ እየተባለ ፍርድቤት ይመላለሳል፡፡የመንግስት ቢሮክራሲ አዝግሞ እስኪደርስ ድረስ ቀድሞ ስራውን አጠናቆ መጠበቅም ኤርሚያስ ጋር ሲደርስ ወንጀል ሆኖ ያስከስሰዋል፡፡ሰውየውን ከዘመን ባንክ እጣፋንታ ያጎደለው ባንኩን ለመመስረት የተያዘው ገንዘብ ሁለት አመት በመንግስት ቤት ተዘግቶበት እስኪቀመጥ ድረስ እሱ ስራ ከመፍታት ብሎ የራሱን ገንዘብ አውጥቶ የሰራተኛ ቅጥርን ጨምሮ ለባንኩ የሚያስፈልጉ ነገሮችን ቀድሞ በማሟላቱ ነበር፡፡

ብዙ ብዙ ያየበት፣እጅግ ስሙ የተነሳበት የአክሰስ ሪል ስቴት ግንባታ መዘግየት መነሻ ሰበቡ የመንግስት ብድግ ብሎ ግንባታ ማገድ ነው፡፡ግንባታው ሲታገድ ለደምበኛ ሰርቶ ለማስረከብ የተገባውን ቃል በቀነ ቀጠሮው ማድረስ የማይቻል ነገር እንደሆነ ግልፅ ነገር ነው፡፡ከዚህ በኋላ ችግር ችግርን እየወለደ፣የአንድ ወገን ብቻ እውነት እየተሰማ ስለቀጠለ ኤርሚያስ ከጥፋቱ በላይ ጥፋተኛ ሆኖ ብዙ ችግር ደረሰበት፡፡በዚህ ሁኔታ የኤርሚያስ ጥፋት ተደርጎ ሊወሰድ የሚችል አንድ ነጥብ ግንባታው ሲታገድ የገንዘብ ዲፕሪሽየሽንን ለመቀነስ ሲል የመሬት ግዥ ውስጥ መግባቱ ነው፡፡ይህ እጁ ላይ ያለው ገንዘብ እንዲያልቅና ገንዘብ ይመለስልን ለሚሉ ደምበኞቹ ቃል በገባው መሰረት ገንዘቡን መመለስ እንዳይችል አደረገው፡፡ይህ ራሱ ጥፋት ነው ለማለት አስቸጋሪ የሚሆነው ደግሞ አንድም የቻለውን ያህል ለደምበኞቹ ገንዘባቸውን ለመመለስ መሞከሩ፣ ሁለትም ወደ መሬት ግዥ የገባው ግንባታው ሳይካሄድ በቆየ መጠን ሊመጣ የሚችለውን የገንዘብ ዲፕሪሽየሽኑን ለመከላከል ነበር፡፡እንዲህ ያለ የዕቅድ መዛባት ሲገጥመው ሌላው የሃገራችን ነጋዴ ሪስኩን ሁሉ ጠቅልሎ የሚጭነው ደምበኛ ላይ ነው፡፡ ኤርሚያስ ግን ይህን ማድረግ ስላልፈለገ ነበር መሬት ግዥ ውስጥ የገባው፡፡

ሌላው የኤርሚያስ ጥፋት ተብሎ ሊነሳ የሚችለው ጉዳይ በመጀመሪያ ወደ ገበያው ሲገባ አለቅጥ ለደምበኞቹ ያደላ ቃል በመግባቱ ነው፡፡ከደምበኞቹ ጋር ውል ሲገባ አንደኛ ደምበኞች በማንኛውም ሰዓት ቤቱን አንፈልግም ብራችን ይመለስ ካሉ ብራቸውን እንደሚመልስ ቃል ገብቷል፡፡ሁለተኛ ቤቱን ሰርቶ ለማስረከብ ቃል በገባው ጊዜ ገደብ ሰርቶ ማስረከብ ካልቻለ የደምበኞችን ብር ከነወለዱ እንደሚመልስ ቃል ገብቷል፡፡እነዚህ ሁለት አለቅጥ ለደምበኛ ያደሉ ሁኔታዎችን ማድረግ ያስፈለገው ያለምንም ማዛባት ቤቶቹን ሰርቼ አስረክባለሁ የሚል መተማመን በኤርሚያስ ጋር ስለነበረ ሁለትም የቤት ሽያጩ ዋጋ ለገዥ እጅግ አጓጊ በመሆኑ ገዥ ገንዘቤን መልስልኝ ሊል አይችልም ከሚል መተማመን ሊሆን ይችላል፡፡ትልቁ ስህተት ያለው እዚህ ጋ ነው፡፡

ህወሃትን የመሰለ ዘረኛ እና አምባገነን ቡድን በሚመራት ሃገር ሁሉም ነገር ሙሉ እና ዝግጁ ሆኖ ስራየን እሰራለሁ ብሎ ማሰብ ኢትዮጵያን አለማወቅ ነው፡፡ኤርሚያስ ያየው የራሱን ስራውን ዳር የማድረስ ጉጉት እና እሱ ሊቆጣጠራቸው የሚችላቸውን ጉዳዮች መሰናዳት ነው፡፡ዋናው ነገር ያለው ግን ከሱም ከመላው የኢትዮጵያ ህዝብም አቅም በላይ በሆነው ህወሃት እጅ ነበርና የሆነው ሆነ፡፡በዚህ ላይ የራሳቸው ርካሽ አጀንዳ ያላቸው የሚዲያ ባለቤቶች አዛኝ መስለው ቀርበው በኤርሚያስ እና በደምበኞቹ መሃከል ያለውን ግንኙነት አበለሻሹት፡፡መደማመጥ ጠፋ!ፍረጃው በረከተ፡፡ ይሄኔ ድሮም ይፈልገው የነበረው ህወሃት ቢለዋዉን ስሎ መጣ፡፡

ህወሃቶች ኤርሚያስን የሚያሳድዱት የሚሰራው ነገር ሁሉ ከአቅማቸው እና ግንዛቤቸው በላይ ስለነበረ ነው፡፡በዚህ ላይ የጎጣቸው ሰው ስላልሆነ ይፈሩታል፡፡የሚሰራውን ነገር ሁሉ ከጭንቅላታቸው በላይ ስለሆነ በዚህ ላይ ብዙ አመት ከሃገር ውጭ ያውም በወልስትሪት ሲሰራ የኖረ ሰው በመሆኑ በሆነ እነሱ በማይደርሱበት መንገድ የተቃውሞውን ፖለቲካ የገንዘብ ዝውውር የሚረዳ መስሎ ሳይሰማቸው አይቀርም፡፡ስለዚህ እያንዳንዱን እንቅስቃሴውን በእውቀት አልቦ ፍርሃት ይከታተላሉ፡፡በተለይ በባንክ ኢንዱስትሪው ውስጥ እንዳይገባ የፈለጉት ለዚህ ነው፡፡ለዚህ ማመሳከሪያው አንድን የብሄራዊ ባንክ ሰው ለምን እንዲህ እንደሚያንገላቱት ሲጠይቅ በግልፅ “ኤርሚያስ እኛኮ አንተ የምትሰራውን ነገር በደምብ ስለማናውቀው በጣም እንፈራሃለን አሉኝ” ሲል ራሱ ኤርሚያስ አመልጋ ለJTV የተናገረው ነው፡፡ለሃገር የሚያስብ መንግስት ቢኖር ኖሮ ኤርሚያስ የሚያመጣቸውን ነገሮች ባለማወቁ የሰውየውን እግር አልነበረም የሚያስረው፡፡ይልቅስ ከኤርሚያስ ጋር በእውቀት የሚተካከሉ አዋቂዎችን አማካሪ አድርጎ ጉዳዩን መከታተል ይቻል ነበር፡፡

ግራም ነፈሰ ቀኝ የኤርሚያስ አመልጋ ጥፋት ኢትዮጵያን አለማወቁ ነው፡፡ኢትዮጵያ በድህነቷ ሃብታም መሆን የሚፈልጉ፣ከእውቀት የተጣሉ ሰዎችን በላይዋ ላይ ሾማ የምትንፏቀቅ ሃገር ነች፡፡እነዚህ ሰዎች እንደ ኤርሚያስ አይነት ስራ ፈጣሪዎችን የሚፈልጉት ሃሳባቸውን ዘርፎ እነሱን እስርቤት ለመወርወር እንጅ ህልማቸውን እንዲኖሩ አይደለም፡፡ለእነዚህ ሰዎች ህልም መሳካት የሚሰራው የገንዘባቸው እና የክላሻቸው ምርኮኛ ደግሞ ብዙ ነው፡፡ኤርሚያስ በበኩሉ እዚህ ሃገር በተለይ በአገልግሎቱ ዘርፍ ያለውን ስር የሰደደ ችግር ለመቅረፍ ህልሙን ብቻ ተከትሎ የሚነጉድ ህልመኛ ሰው ነው፡፡ህልም ደግሞ ህልም ብቻ ነው-እውን የሚያደርገው ስርዓት ካልተዘረጋ በቀር፡፡

ኢትዮጵያን ሳያውቅ ህልሙን ብቻ ተከትሎ የተጓዘው ኤርሚያስ ጥፋት ካጠፋም የጥፋቱ ስር መሰረት መበለጥን የማይፈልገው የኢህአዴግ መንግስት አሰራር ነው፡፡ኢህዴግን አይነት እንቅፋት ባይገጥመው ኖሮ ኤርሚያስ ሊያጠፋ የሚችለው ማንኛውም የሚሰራ ሰው ሊሰራቸው የሚችሉ ውስን ጥፋቶችን ነበር፡፡በግሌ የሚገርመኝ ነገር ኤርሚያስ ኢህአዴግን የመሰለ እንቅፋት ተቋቁሞ ለመኖር እንጅ ተመልሶ ወደ መጣበት ለመሄድ አለማሰቡ ነው፡፡በዚህ ሁሉ ውስጥ ኤርሚያስ ከበደለው የተበደለው ይበልጣል፡፡አምጦ ከወለደው ዘመን ባንክ እንደዋዛ ተባሯል፣የአገልግሎት ዘርፉን ለማዘመን አስቦ የሞከረው በጎ ምኞቱ ከዘራፊ አስቆጥሮታል፡፡የእርሱ እውነት ታፍኖ የአንድ ወገን የሸር ጩኽት ብቻ ሲሰማ በመኖሩ “በአጭበርባሪነቱ” ስምምነት ተደርጓል፡፡ይህ ትልቅ የሞራል ስብራት ያመጣል፡፡የኤርሚያስ ፈተና ህወሃት ከስልጣን ሲነሳም አለማብቃቱ በጣም አሳዛኝ ነገር ነው፡፡

የህወሃትን ከስልጣን መነሳት ተከትሎ የዶ/ር አብይ መንግስት መልካም ዘመን ለመምጣጡ ምልክት ይሆነን ዘንድ እስረኞችን ፈትቷል፣ከስራ ተባርረው የነበሩ ምሁራን ወደ ሥራቸው መልሷል፣ማዕረጋቸው የተወሰደባቸውን ውትድርና ባለሙያዎች ማዕረጋቸውን መልሷል፡፡በዚህ ሁሉ ውስጥ ምርኮው ያልተመለሰለት ኤርሚያስ አመልጋ ነው፡፡ከዘመን ባንክ ጀምሮ ቢወራ የማያልቅ ግፍ ተሰራበትን ሰው ጉዳዩን በአግባቡ መርምሮ የሚገባውን እንዲያገኝ እርሱም ያጠፋውን እንዲያስተካክል ሁኔታዎችን ማመቻቸት ሲገባ ለሌላ ዙር እስር ተዳርጓል፡፡አሁን የታሰረው ደግሞ “ሆቴልህን ለምን በውድ ዋጋ ለሜቴክ ሸጥክ” በሚል የዶሮ ሻኛ አምጣ አይነት አስገራሚም፣አሳዛኝም ነገር ተከስሶ ነው፡፡

ለዚህ አቶ ኤርሚያስ ለፍርድቤት መልስ ሲሰጥ ኢምፔሪያል ሆቴልን የገዛው በ18 ወር ተከፍሎ በሚያልቅ 47 ሚልዮን ጥሬ ብር ሊከፍል እና ሆቴሉ ያለበትን 23 ሚሊዮን ባንክ እዳ ሊከፍል ተስማምቶ እንደነበር፡፡በመሃል ሜቴክ ሆቴሉን መግዛት ሲፈልግ ኤርሚያስ የተስማማበትን የሆቴሉን እዳም ሆነ ጥሬ ገንዘብ ከፍሎ ስላልጨረሰ የሆቴሉ ስመ-ሃብት በኤርሚያስ ስም አልዞረም ነበርና ግዥ እና ሽያጩ የተፈፀመው በመጀመሪያው የሆቴሉ ባለቤት እና በሜቴክ መሃከል ነበር፡፡አሁን አቶ ኤርሚያስ እስርቤት የተወረወረው በሌለበት ግዥ እና ሽያጭ ሁኔታ ነው፡፡በዚህ ላይ አስወድደህ ሸጠሃል የተባለው ሆቴሉ የነበረበት የባንክ እዳ ግንዛቤ ውስጥ ሳይገባ ነው፡፡ከዚህ የምንረዳው ህወሃት ከስልጣን ቢወርድም አዋቂን የማይወደው የፓርቲው ባህል አሁንም በተግባር ላይ እንዳለ ነው፡፡ሁለትም ኤርሚየስ የታሰረው የታሳሪ ሙሰኞችን የብሄር ተዋስኦ ለማብዛት እና ከወደ ትግራይ የሚመጣውን “የብቻችንን ታሰርን” ጩኽት ለማርገብ ነው እንጅ ኤርሚያስ ሰባ ሳባት ቢሊዮን ብር አመድ ካደረጉ ባለስልጣናት የበለጠ ጥፋት ስላጠፋ አይደለም፡፡በዚህ ላይ ኤርሚያስ በመታሰሩ ግር ብሎ ወጥቶ መንገድ የሚዘጋለት የዘሩን ጎረምሳ ቀድሞ ያላደራጀ የስራ ሰው ስለሆነ ነው እስሩ እምብዛም የማያስፈራው፡፡

እንደ ኤርሚያስ ያሉ ከጥፋታቸው ልማታቸው የሚበልጥ ስራ ፈጣሪዎችን እስርቤት እየዶለ ያለው መንግስት እድገት ማምጣትም የሚያምረው መሆኑ ነው አስቂኙ ነገር፡፡ብናውቅበት ኤርሚያስ ሃገሩ ብትመቼው ብዙ ደረጃ የሚደርስ አቅም እና እውቀት ያለው ሰው ነበር፡፡ኑልን እያልን የምንለምናቸው አፍሪካዊ ኢንቨስተሮችን እነ ዳንጎቴን እና ሞኢብራሂምን አይነት ባለሃብት ሊወጣው የሚችል ሰው ነበር ኤርሚያስ አመልጋ አያያዙን ብናውቅበት፡፡የሆነ ሆኖ ገና የምንመራበት ስርዓት ከዘር ቆጠራ የኋሊት ጉዞ ያልተፈወሰ ነውና ማር እንደማይጥማት እንስሳ ደህና ነገር አይወድለትም፡፡ሰው የደረሰበት መድረስ የሚፈልግ ዘመኑን የሚመጥን የእድገት ደረጃ ላይ የደረሰ ዜጋ ሁሉ ግን ይህን የመንግስት አካሄድ ሃይ ማለት አለበት፡፡በውሃ ቀጠነ የሚታሰረው ኤርሚያስ አመልጋ ለሃገር የሚጠቅመው ከእስርቤት ውጭ ሆኖ በመሆኑ በአስቸኳይ መፈታት እንዳለበት አጥብቆ መጠየቅ መራመድ የሚፈልግ ዜጋ ሁሉ የሞራልግዴታ ነው፡፡
__
ማስታወሻ:በዚህ ጽሁፍ ላይ የተንጸባረቁ ሳሃቦች የጸሃፊውን/የጸሃፊዋን እንጂ የድረገጹን አቋም አያንጸባርቁም። ነጻ አስተያየት ወይንም ሃሳብ በዚህ ድረ ገጽ ለማውጣት ጽሁፍዎትን በ info@borkena.com ይላኩልን።

- Advertisement -Early Bird Holiday Deals! Before you know it, the holidays will be right around the corner! Take advantage of our early bird deals today and save up to $40 on our fees with code SPOT40!
Stay Connected
28,789FansLike
13,920FollowersFollow
8,540SubscribersSubscribe
Stacy Adams
Must Read
Related News

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here