በዛብህ ናፍቆት
መጋቢት 17 2011 ዓ.ም.
በለንደን እንደራሴ ጽህፈት ቤት የተደረገው ቀዳሚና ህዝባዊ ጉባኤ – መጋቢት ፯፡ ፪ሺ፲፩ ዓ.ም.
ጉባኤው ሊጀመር ዐሥራ አምሥት ደቂቃ ሲቀረው፤ ለንደን ከሚገኘው የኢትዮጵያ እንደራሴ (Embassy) ደጃፍ ላይ ተገናኘን። በቀጠሯችን መሠረት ቃላችንን አክብረን በሰዓቱ መገናኘት በመቻላችን፤ በየበኩላችን ሳንደሰት አልቀረንም። ጉባኤው ይጀመራል ተብሎ የተነገረን ከቀኑ ኹለት ሰዓት ነው። ወንበር ለማግኘት ተስፋ ይኖረናል ተባባልን። ኩራት ብጤም ተሰምቶናል።
ኃይለኛ ነፋስ ይነፍሳል። ውርጩ አንገት ያስደፋል። የስደት ዓመታት ሲጨምር፤ ከቅዝቃዜው መላመዱ እንዲሁ በተጓዳኝ የሚሄድ ይመስለኝ ነበር። ዛሬ ላይ በተቃራኒ መኾኑን ሳልረዳ። ይኽም ኹኖ ከወዳጄ የሞቀ ሰላምታ ከመለዋወጥ አልገተንም።
‘ሽቅርቅር ብለህ የይሖዋ ምስክር መስለሀል።’
አልኩት በተለይ ያጠለቀውን ነጭ ጫማ እየተመለከትኩ።
ኹኔታችንን በጥንቃቄ ሲመለከቱ ለነበሩት የህንጻ ጠባቂዎች፤ በያዙት መሣሪያ ይዳብሱን ዘንድ እጆቻችንን እንደምርኮኛ ወደላይ ሰቀለን። ግራና ቀኝ ጎናችንን ደባብሰው ከሚጠበቀው ነፃ መሆናችንን ካረጋገጡ በኋላ ወደውስጥ እንድንገባ ፈቀዱልን።
የእንደራሴው ጽህፈት ቤት እደሳ የተጠናቀቀው በቅርቡ (ባለፉት ወራት) ውስጥ እንደነበረ ተመልክቻለሁ። መቼም ጥሩ ባለሞያ የሰራው ማንኛውንም የሥራ ፍጻሜ መመልከት ደስ ያሰኛል። የተደረገለት እድሳት ከቀድሞው በበለጠ ንጽሁ አድርጎታል። እንደወዳጄ ጫማ ተመልካችን ይስባል። በወቅቱ አፄ ኃይለስላሴ ፳ሺ የእንግሊዝ ፓውንድ እንደገዘቱ አንብቢያለሁ። ዛሬ ቢተመን ዋጋው ጣራ ይነካል። ሥፍራው አስፈላጊና አመቺነቱ ከሚወሳላቸው የለንደን አካባቢዎች አንዱ ነው። የማወቅ ጉጉት ውስጤ አደረበት። አንድ ሰሞን ወያኔዎች ሊሸጡት እንደሆነ ተናፍሶ ቆሽቴ አርሮ ነበር። እንዴት ሰው የሀገር ቅርስ ሊሸጥ ይደራደራል? ይሁዳ! በገንኩኝ። ለነገሩ ንብረት ከሰው ልጅ እልቂት አይበልጥ። ይመስለናል እንጂ። በኋላ ሳጣራ ሀሰት ነው ተባለ። መጠራጠሬን ግን አላቆምኩም። አትፍረዱብኝ! ኢትዮጵያዊ አይደለሁ? ያልጠረጠረ ተመነጠረ እንዲሉ መጠራጠር ልዩ መብታችን ኹኗል። ተሞክሮ ሳይሰምር ቀርቶላቸው ይሆናል በማለት ደመደምኩኝ።
ሙሉውን ጽሁፍ በ ፒ ዲ ኤፍ ለማንበብ እዚህ ይጫኑ
___
ማስታወሻ:በዚህ ጽሁፍ ላይ የተንጸባረቁ ሳሃቦች የጸሃፊውን/የጸሃፊዋን እንጂ የድረገጹን አቋም አያንጸባርቁም። ነጻ አስተያየት ወይንም ሃሳብ በዚህ ድረ ገጽ ለማውጣት ጽሁፍዎትን በ info@borkena.com ይላኩልን።