የኢትዮጵያ ኮሚኒቲ በኦማሃ ነብራስካ
ነሃሴ 30, 2011 ዓ.ም.
የመልካም ስራ ፋና ወጊዎች አቶ ሽመልስ አዱኛ ከያኒያን ቻቺና አበራ ሞላ
በሃገራችን ኢትዮጲያ በጎ ስራ የሚሰሩትን የሚዘክሩ ልዩ ልዩ ድርጅቶች መከሰታቸው የሚመስገን ተግባር ነው:: የዚህ አይነቱ ተግባር ቀጣዩን ትውል የመልካም ስራ ተፈላጊነትን ያምንበትና ይሳተፍ ዘንድ ይረዳል::
በሰለጠኑ ሃገሮች የህዝቡን ችግር ከመንግስት በበለጠ የሚደግፉ ግብረሰናይ ድርጅቶች የተዋቀሩትና ለመላው ኣለም የተረፉት ለሃገራችንም የደረሱት በዚህ መልክ የተሰማሩ ባለበጎ ራእይ ግለሰቦች እጅ ስላለበት ነው::
ባለፉት ዘመናት በልዩ ልዩ መልካም ስራዎች ለሃገራችን የተሳተፉት ሰዎችን ሁሉንም በተለይ ፋናወጊዎችን መዘከር በጣም ያስፈልጋል:: እንደሃገራችን ብሂል የፊተኛውን ባልሽን በምን ቀበርሽው በሻሽ የኋለኛው እንዳይሸሽ የሚለው በሚመክረን መስረት ቀጣዩ ትውልድ በመልካም ስራ ይገሰግስ ዘንድ የቀደሙት በተገቢ ምስጋና መደገፍ ያግዛል::
የሃገራችን በደን መራቆት ያሳሰባቸው ክቡር አቶ ሽመልስ አዱኛ የችግኝ ተከላ በአዲስ ኣበባ ከተማ ዙሪያ ተራሮች ላይ ያስጀመሩ ነበሩ:: ከዚያ በቀደመው ዘመንም አቶ ሽመልስ የሰሜኑ የሃገራችን ረሃብ በከፋበት ወቅት በአለም ዙሪያ በመጓዝ በእምባ ልመና ከፍተኛ እርዳታ ለተጎዱት ወገኖች አስገኝተዋል የተጎዱት ወገኖች ዛሬ በግፍ በሚፈናቀሉባቸው ስፍራዎች ሃገራችው በመሆኑ በሰፈራ የተሻለ ህይወት ለራሳቸውም ለሃገራችውም ያደርጉ ዘንድ አቋቁመዋል::
የጎዳና ተዳዳሪዎች ህይወት ይሻሻል ዘንድ ከያኒ ቻቺ ታደሰ በግንባር ቀደምነት ብዙ ደክማለች የሃገሪቱ ታላላቅ ግብረሰናይ ድርጅቶች ማህበር CRDA ባዘጋጀው ፕሮግራም ላይ ይህ ቅዱስ ድርጊት ይስፋፋ ዘንድ ብዙ ተዋጽኦ አድርጋለች;: ቻቺ በኪነጥበብ ስራዎቿ በዳያስፖራ የኢትዮጲያ የባህል አምባሳደር በመሆን በአሜሪካኖች ዘንድ መልካም አሻራ ኣሳርፋለች:: በቅርቡ ወደሃገር ቤት ለጉብኝት በሄደችበት ወቅት ግን ማንም ዞር ብሎ አላያትም በልጇ ሞት መሪር ሃዘን የሚጠበቀው ማጽናናት አልተደረገላትም ለምን?ይህ ክፉ ወረተኛነት ይሆን?
የትውልድ ከተማችን የአፍሪካ መዲና አዲስ አበባ ከከፋ የንጽህና ጉድለት ይወጡ ዘንድ ብዙ የደከምው አበራ ሞላ (ከያኒ ስለሺ) ፍጹም የማይረሳ ተግባር ለሃገራችን ፈጽሟል:: በቅርቡ በሰጠው ጋዜጣዊ ምልልስ ላይ ግን ሰሚ ያለማግኘቱን የባለስልጣኖቹ የትኩረት አቅጣጫና የደከመበት ሁሉ ከንቱ መቅረቱን በምሬት ተናግሯል:: በከተማ ማስዋብ ዘመቻ ፋና ወጊውን ገለል ያደረገ አካሄድ ተገቢ ኣየደለም::
በአጠቃላይ የሃገራችን በጎ ስራዎች ይዘልቁ ዘንድ ጀማሪዎቹን በኩሮቹን መዘከር ማበረታት ይገባናል:: የራሳችንን ወርቆች መዳብ ማድረጉ ኣይበጀንም:: በልዩ ልዩ ፕሮግራሞቻችን ሊጋበዙ ልምዳቸውን ሊያካፍሉ ይገባል:: የኢትዮጲያ ኮሚኒቲ በኦማሃ በትንሽ አቅሙና በጥቂት አባላቱ እነዚህን መሳይ የመልካም ሃገር ሃሳቢዎችን ባለፈው የሚሞሪያል ዴይ ዘክሯል:: ለከያኒ ቻቺ በአሜሪካ በመሆኗ አድናቆታችን ይተላልፍልን የሚቻል ከሆነም ጉብኝቷና ምክሯን እንደምንፈልግ ይተላለፍልን::
ethiopiancommunityomaha@gmail.com
የኢትዮጵያ ኮሚኒቲ በኦማሃ ነብራስካ
____
ማስታወሻ:በዚህ ጽሁፍ ላይ የተንጸባረቁ ሳሃቦች የጸሃፊውን/የጸሃፊዋን እንጂ የድረገጹን አቋም አያንጸባርቁም። ነጻ አስተያየት ወይንም ሃሳብ በዚህ ድረ ገጽ ለማውጣት ጽሁፍዎትን በ info@borkena.com ይላኩልን።