(በመስከረም አበራ)
ግንቦት 23 ፤ 2012 ዓ ም
የሰው ልጅ ስላጠፋው ጥፋት ካልተጠየቀ ጭራሽ ተበዳይነት እንደሚሰማው የታወቀ ነው፡፡ህወሃቶች እየተሰማቸው ያለው እንዲያ ነው፡፡ስላደረሱት ዘረፋ፣የሰብዓዊ መብት ጥሰት፣ስላወደሙት የሃገር እሴት ስላልተጠየቁ ዘረፋን ህጋዊ ያደረጉበትን፣የኢትዮጵያን ህዝብ ደም እምባ ያስለቀሱበትን ስልጣን የያዙበት ቀን ግንቦት ሃያ አሁንም እንደ ድሮው ደምቆ ካልተከበረ ብለው እንደተበደለ እያማረሩ ነው፡፡የግንቦት ሃያ ዕለት ማታ በትግራይ ቲቪ ቀርበው የዶ/ር አብይን መንግስት እንዳይበላ እንዳይዘራ አድርገው ሲያራክሱ አምሽተዋል፡፡ሌላው ቀርቶ የእነሱ ልብስ በሆነው ዘረፋ፣ሃገር ክህደት ሳይቀር ዶ/ር አብይን ሲያብጠለጥሉ አምሽተዋል፡፡ “የባንክ አካውንታችን ከዶ/ር አብይ የባንክ አካውንት ከበለጠ እንቀጣ” አይነት የተለመደ ሰሚን የመናቅ ለበጣቸውን ያለምንም ሃፍረት አዝንበዋል፡፡ በጣም የሚገርመው አቶ ስዩም መስፍን የዲፕሎማዊ ልሂቅ ሆነው የቀረቡበት ድፍረት ነው፡፡
አቶ ስዩም መስፍን በትጥቅ ትግሉ ዘመን በምን ተመርጠው እንደሆነ በማይታወቅ መንገድ ከሃገር ሃገር እየዞሩ የሸማቂውን ፓርቲያቸው የውጭ ጉዳይ ሲያስተናብሩ ኖረዋል፡፡ በህወሃት ቤት በጫካ ቆይታ የተደረገ ነገር ሁሉ በየትኛውም ዩኒቨርሲቲ ገብቶ ከመማር የበለጠ እውቀት እና ድፍረት የሚሰጥ ነገር ከመሆኑም ባሻገር የትዕቢትም ምንጭ ነው፡፡በመሆኑም የጫካው ቆይታ አክትሞ ህወሃት ስልጣን ሲይዝ ስዩም መስፍን አስራ ዘጠኝ አመት ሙሉ ያለምንም ተቀናቃኝ የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሆነው ኖረዋል፡፡
በዚህ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርነት የስልጣን ቆይታቸው ባድመ ለኢትዮጵያ ተፈርዳለች ብለው ህዝብን በነጭ ውሸት አስጨፍረዋል፡፡ዛሬ አቶ ስዩም ዶ/ር አብይን ግብፅን በአንዴ ባለመርታት የዲፕሎማሲ አላዋቂነት ይከሳሉ፡፡ግብጽ እንደ አንድ ዓይኗ በምታየው አባይ ዙሪያ ድርድር ሲደረግ ስንት ውጣ ውረድ እንደሚኖር ግልፅ ነው፡፡ይህን የሚያውቁት አቶ ስዩም መስፍን አብይን በአንዴ ግብፅን አሳምነው የአባይን ግድብ ሙሊት ያለ ምንም ሁከት ማድረግ ባለመቻላቸው የፍርደ-ገምድል ክስ ይከሳሉ፡፡ጭራሽ አብይ ግድቡን ለግብፅ መሸጣቸውን “ወላሂ አልነካችሁም” ብሎ ምሏል ብለው የህፃን ክርክር ያመጣሉ፡፡
አብይን በተወሳሰበው የአባይ እና የግብፅ ዲፕሎማሲያዊ ጉዳይ ወዲያው እልባት ባለመስጠት የሚከሰው አቶ ስዩም መስፍን እርሱ የሃገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እያለ ሃገሪቱን ሲመራ የነበረው መንግስት አስራ ሰባት አመት በነበረው የጫካ ትግል በረባሶ እየተቀያየ፣ወታደር እየተለዋወጡ ደርግን ከተዋጉት፣ እንደ እጅ መዳፍ ከሚያውቁት ባልንጀራቸው ኢሳያስ አፈወርቂ ጋር እንኳን ቁጭ ብለው ተደራድረው የሰባ ሽህ ኢትዮጵያዊያንን ህይወት የበላውን የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ማስቆም ያልቻሉ ሰዎች ናቸው፡፡
የሚብሰው ደግሞ እነ አቶ ስዩም የሚመሩት ዲፕሎማሲ በጦርነት ያሸነፈችውን ሃገራችን ተሸናፊ መንግስት እንደሚያደርገው ተሸቀዳድማ ‘ይግባኝ የሌለው ፍርድ እቀበላለሁ፣ያሻችሁን ጣሉብኝ’ ስትል የተሸናፊ በር እንድትይዝ ማድረጉ ነው፡፡ይግባኝ የሌለው ፍርዱ ደግሞ ሰባሽህ የሃገራችን ወጣት ያለበቀትን ግዛት ወደ ኤርትራ ማካለሉን እያወቁ ሃፍረተቢሱ አቶ ስዩም “ግዛቶቹ ለእኛ ተፈርደዋል” ብለው ያመናቸውን የሃገራችንን ቅን ህዝብ ሲያስጨፍሩ መሰንበታቸው ነው፡፡ ይህ የተረሳ መስሏቸው ዛሬ ፈርጥጠው በመሸጉበት በመቀሌ፣የኢትዮጵያን ህዝብ ዘርፈው ባከማቹት ገንዘብ ባቋቋሙት የቴሌቭዥን ፕሮግራም ላይ ቀርበው “ከእኔ በላይ ዲፕሎማት ላሳር” ዓይነት መመጻደቅ ሲያሰሙ ሰሚን ያሳፍራሉ!
የአቶ ስዩም ጉዳይ በዚህ አያበቃም፡፡በተራዛሚው የ19 ዓመት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርነት ዘመናቸው የዲፕሎማሲውን ዘርፍ ከእርሳቸው ዘውግ የመጡ ሰዎች መናኽሪያ አድርገው የኖሩ ሰው ናቸው፡፡በዘር ተቧድነው ከአታሼ እስከ አምባሳደር በዓለም ዳርቻ የተበተኑ የአንድ ዘውግ ሰዎች በተበተኑበት ሃገር ንግድ የሚያጧጡፉ፣ለዘመዶቻቸው የውጭ ንግድ በር የሚከፍቱ፣አለፍ ካለም በሃገር ውስጥ የተዘረጋው የዘረኝነት መንግስት አላስቀምጥ ብሎት ሃገር ጥሎ የሄደውን ኢትዮጵያዊ የሚሰልሉ ነበሩ እንጅ እንደ ዲፕሎማት ለሃገራቸው ሰዎች የሚቆሙ ጠበቆች አልነበሩም፡፡ ይህ አልበቃ ብሎ ወደ ውጭ ሃገር የሚሰደዱ ኢትጵያዊያንን ከሃገር የሚያስወጡ ኤጀንሲዎቸ ሳይቀሩ ከአንድ የአቶ ስዩም ዘውግ አባላት እንዲሆኑ ያደረጉ ፍፁም ዘረኛ ሰው ናቸው ዛሬ ከእኔ በላይ ላሳር እያሉ ፀጉር የሚሰነጥቁት-አቶ ስዩም፡፡እነዚህ ሰዎች ደግሞ በየተሰየሙበት ኢምባሲ ኢትዮጵያዊያን ላይ ጥይት እስከመተኮስ የሚደርስ ጥጋብ ያንገላታቸው ነበሩ፡፡ በአረብ ሃገር ኢምበሲዎች የተሰየሙት ደግሞ ኢትዮጵያዊያን በዘይት ሲጠበሱ፣ከፎቅ ሲወረወሩ፣ህይወታቸውን ጠልተው በገመድ ተንጠልጥለው ሲሞቱ ኮሽ ያለ የማይስላቸው ልበ-ደንዳች ናቸው፡፡
አቶ ስዩም መስፍን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትርነታቸው፣ፓርቲያቸው ህወሃትም ከአድራጊ ፈጣሪነቱ ላይመለስ ሊነሳ ጥቂት ወራት ሲቀሩት የአቶ ስዩም ጉድ ከቤት ወደ ውጭ የወጣበት ወቅት ነበር፡፡ ይኽውም በአቶ ስዩም የተመራው የኢትዮጵያ ዲፕሎማሲ በቤት የለመደውን ወገንተኝነት ተሸክሞ የደቡብ ሱዳን መሪዎችን (ሪክ ማቻርን እና ሳል ቫኪርን) ለማስታረቅ ሲሞክር ሳልቫኬር እንድም ሁለቴ ነገሩን ካዩ በኋላ ‘ስዩም በሚመራው የዲፕሎማሲ ቡድን ገለልተኝነት አለ ብየ ወደ አዲስ አበባ እግሬንም አላነሳ’ ብለው ነገር አለሙን ትተው ሃገራቸው ቁጭ ማለትን መርጠው እንደነበር የዜና አውታሩ ሁሉ የዘገበው የአቶ ስዩም ቅሌት ነው፡፡ይህ ቅሌት ነው እንግዲህ ከእኔ በላይ ላሳር በሚል የሚል እያኩራራ ያለው !
የአቶ ስዩም መኩራራት ምን ያህል ጭፍን እንደሆነ የሚያስታውቀው ከጫካ ጀምረን በውጭ ግንኙነታችን መርህ የተሞላን፣ከኢትዮጵያ ጥቅም ዘነፍ የማንል ነን ሲሉ ሲኩራሩ ነው፡፡አቶ መለስ ይቅርታ የጠየቁበትን ከዚያድ ባሬ ጋር ወግነው ሃገራቸውን የወጉበትን ጉዳይ ሳይቀር በተቃራኒው ገልብጠው ሊነግሩን ሞክረዋል፡፡ዛሬ አይናችሁን አያሳየኝ የሚለውን የአቶ ኢሳያስን ሻዕብያን ትርፍራፊ ለማግኘት ሲሉ ሃገራቸውን በቅኝ ገዥነት ማብጠልጠላቸውን የምንረሳ ይመስል እኛ ከትናት እስከ ዛሬ በመርህ የመርህ የተሞላን የሃቅ ሰዎች ነን ሲሉ መስማት ያሳቅቃል፡፡ሃገርን በውሸት ታሪክ ላይ ቆሞ የቅኝ ገዥነት ክፉ ስም መስጠት ለሃገር ጥቅም መቆም ነው ነው የሚሉት አቶ ስዩም !
ሃገር ጠቅልሎ ለመጉረስ የደረሰውን የዘረፋ አባዜ እንኳን እንደ አቶ ስዩም ያለውን የፊት ወንበር ሰልፈኛ ቀርቶ እሱን የተጠጋን ሳይቀር በአንድ ሌሊት ሚሊየነር ማድረጉ እየታወቀ እስከ ሰባት ጉልበታችን አንድ ስባሪ ሳንቲም ያልነካን ቅዱሳን ነንና አካውንታችን ከጠ/ሚ አብይ አካውንት ጋር ይነፃፀር፡፡ ተነፃጥሮ የእኛ በልጦ ከተገኘ እንቀጣ ያሉት ነገር ህወሃት በሞቱ ብቻ የሚፈወስ ክፉ በሽታ እንደተጠናወተው አስረጅ ነው፡፡ የሆነው ሆኖ አፅናኙ ነገር የህወሃት የትዮጵያን ህዝብ በመንታ ጥርሱ የሚነክስበት ዘመን ማክተሙ ነው!
በጥጣም ከሚያሳዝነኝ እንዲ አይነት ሰዎች አገር አስተዳድረዉ ነበር ተብሎ በታሪክ ለቀጣዪ ትዉልድ ሲዘከር ነው ።