
ሰኔ 25 ቀን 2012ዓም(02-07-2020)
የኢትዮጵያ ክፍላተሃገር ህብረት ከሁለት ቀናት በፊት በገዳዮች እጅ ህይወቱ ባለፈው በታዋቂው ድምጻዊ አጫሉ ሁንዴሳ ሞትና ያንን ተከትሎ የወንጀለኞቹ ግብረአበሮች በንጹሃን ኢትዮጵያውያን በተለይም በአማራው ህብረተሰብ ተወላጆች ላይ በተለያዩ ቦታዎች ባደረሱት የጭፍን እርምጃ ህይወታቸውን ላጡት ወገኖቻችን የተሰማውን ጥልቅ ሃዘን ለመግለጽ ይወዳል።
በዚህ ተጠንቶና ታስቦበት በተቀነባበረ የፖለቲካ ግድያ ተካፋይ የሆኑት የተለያዩ ግን አንድ ዓላማ ማለትም የኢትዮጵያ መፈራረስና የሕዝብ እርስ በርስ እልቂት ያስተሳሰራቸው የውጭ ሃይሎች አጀንዳ ፈጻሚዎች እንደሆኑ ምልክቶችና ማስረጃዎች እዬወጡ ነው።
እነዚሁ የጥፋት ሃይሎች በጭቁን ሕዝብ ስም ላለፉት ሃምሳ ዓመታት ለአገራችን አንድነትና ነጻነት ለሕዝቡ አብሮነትና ዘላቂ ሰላም እንቅፋት በመሆን በተለይም ላለፉት ሃያ ዘጠኝ ዓመታት በፌዴራል፣ በክልልና በከባቢ ደረጃ ባሉት በተለያዩ የሥልጣን እርከኖች ላይ ተቀምጠው የፈጸሙትና ያስፈጸሙት ፣ የግድያ፣የዘረፋ አያሌ ወንጀል ሳያንሳቸው ሃይላቸውን አስተባብረው ያገራችንን ግብአተመሬት ለማረጋገጥ ወጣቱን አጫሉን ገለው በሌላ ወገን ላይ ለማላከክ የሄዱበት መንገድ ባይሳካላቸውም ቀላል ነው የማይባል ጉዳት አድርሰዋል፤አሁንም የበለጠ ጉዳት ለማድረስ ደፋቀና እያሉ ይገኛሉ።ያሰቡት ግን አይሳካላቸውም።ሆኖም ግን የሚፈጽሙት ተግባር ምን ያህል ጨካኞች፣ለሰው ልጅ ህይወትና ለአገር ክብር ደንታቢሶች እንደሆኑ በግልጽ የታዬበት ድርጊት ነው።
ግድያ መፈጸማቸው ብቻ ሳይሆን የአጫሉ ሁንዴሳ አስከሬን ላይ የተፈጸመው ክብረቢስ አድራጎት ማንኛውንም የሰው ልጅ ክብር የሚወድ ፍጡር የሚያሳዝን ነው።በቤተሰቦቹም ሆነ በወዳጆቹ ላይ የደረሰው ጥቃት ሲታይ ምን ያህል ለኦሮሞው ማህበረሰብ ንቀት እንዳላቸው ያመላክታል።በአገር ውስጥ ብቻ ሳይሆን የሰለጠነ ሕዝብ በሚኖርበት አገር ለምሳሌም ለንደንና ሜኖሴታ ከተማ ውስጥም በስደት ስም የሚኖሩ የሴራው አቀነባባሪ የሆኑት ደጋፊዎቻቸውና ቤተሰቦቻቸው ቦዘኔ ወጣቶች የፈጸሙት አውዳሚና ዃላቀር አድራጎት እንወክለዋለን የሚሉትን ማህበረሰብ ብቻ ሳይሆን የጥቁርን በተለይም የአፍሪካን ሕዝብ የሚያሳፍርና የሚያስገምት ነው።
የጥቁር ዘር በዘረኛ ነጭ ፖሊሶች የሚደርስበትን ግፍና በደል፣ግድያ በመኮነንና በመቃወም ለመብቱ በሚጮህበት በዚህ ወቅት የጥቁር ዘር የሆኑትየኦሮሞ ተወላጅ የሆኑት ኢትዮጵያውያን መሰል ያገራቸውን ልጅ ሲገሉና ንብረቱን ሲያወድሙ ላዬ ዘረኛ ለሚፈጽመው አድራጎት የሞራል ድጋፍ እንደሚሆነው ጥርጥር የለውም።ጥቁርን የምጠላው እንደሰው ስለማያስብ ነው፤ለራሱ ወገን የማይራራ የነጩን ዘር ሊያጠፋ የሚችል ከአውሬና እንስሳ ያልተሻለ ፍጡር ነው፤ብሎ ለሚያቀርበው ምክንያት ይህ አድራጎት ማስረጃ ሊሆነው ይችላል።
አገራችንን ለቀውስና ብጥብጥ በመዳረግ የፖለቲካ ትርፍ እናገኛለን፤የሥልጣኑ ባለቤት እንሆናለን ብለው የሚያስቡ ጭፍኖች ዓይነህሊና የላቸውም እንጂ ካላቸው ከፈት አድርገው እንዲያዩ የምንመክረው ቢኖር የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚታገለው ለተሻለ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት እንጂ በጎሳ ማንነቱ ሲገሉት፣ሲያስሩት ሲገርፉት ያገሩንም ሃብትና ጥሪት ሲዘርፉት ለኖሩ ፋሽስቶች ለሚመሩትና ለሚወክሉት የጎሰኞች ሥርዓት እንዲቀጥልና እንዲያንሰራራ በመሻት እንዳልሆነ እንዲገነዘቡት ነው።
በተለይም በአሁኑ ጊዜ፣የአባይን ግድብ ለማጠናቀቅ ጥረት በሚደረግበትና አገር ወዳዱ ሕዝብ በሚረባረብበት ጊዜ ግብጽንና ግብረአበሮቿን የመሰሉ የውጭ ጠላቶች ግድቡን ለማሰናከል አሰፍስፈው ዘመቻ በከፈቱበት ወቅት የነሱ አጀንዳ አስፈጻሚ ሆኖ መገኘቱ በታሪክና በትውልድ የሚያሶቅስና የሚያሳፍር ተግባር ከመሆኑም በላይ ይቅርታ የማይሰጠው ያገር ክህደት ነው።
በስሙ የሚነገድበት በተለይም የትግራይና የኦሮሞ እንዲሁም የሌላውም ጎሳ ተወላጅ የሆነው ኢትዮጵያዊ አያት ቅድመአያቶቹ ተባብረው የገነቧትን አገሩን አፍርሶ የሌላ አገር ባለቤት መሆን እንደማይቻል አውቆ አስመሳይ ባንዳዎች ከሚጎነጉኑት የጥፋት መረብ እራሱን እንዲጠብቅና እንዲያርቅ እዬመከርን፤እስካሁን ድረስ በስሙ ለፈጸሙት ወንጀል ሕጋዊ እርምጃ እንዲወሰድባቸው ለፍትህ አካል አጋልጦ እንዲሰጥ ጥሪ እናቀርባለን።
አጫሉን የገደለው አጫሉን በማሳሳት እጠቀምበታለሁ ብሎ ያሰበው ቡድን ለመሆኑ ማስረጃዎች እዬወጡ መሆናቸው ይሰማል።ያም ሆነ ይህ የማይካደው ነገር ህወሃት፣ኦነግና የኦነግ ቤተሰብ የሆኑ የፖለቲካ ቡድኖች ከግድያው ቅንብርና አፈጻጸም የራቁ ላለመሆናቸው እስከአሁን የተራመዱበት መንገድና አሰላለፍ ያረጋግጣል።
በሥልጣን ላይ ያለው አካል ለአገር አንድነትና ሰላም፣ለሕዝብ አብሮነት፣ለፍትህ የቆመ ከሆነ በዬጊዜው የተፈጸሙ ወንጀሎችንና ፈጻሚዎቹን ሳይሸፋፍን በይፋ ለሕዝብ ገልጾ ሕጋዊ እርምጃ መውሰድ ይጠበቅበታል።የሕግን የበላይነት በተግባር ሊያረጋግጥ ይገባል።በጎሰኞች ገንዳ ውስጥ ከመዋኘት ወጥቶ በቁርጠኝነት የኢትዮጵያንና የኢትዮጵያውያኑን ጥቅም ሊያስከብር ይገባል እንላለን።ይህንን ለማድረግ ቁርጠኛ ከሆነና በተግባርም ካሳዬ የኢትዮጵያ ክፍላተሃገር ህብረት ከጎኑ ይሰለፋል።
ለችግሩ መንስኤ የሆነው ሕገመንግሥት፣ የጎሳ ፖለቲካና የክልል አወቃቀር ተወግዶ በሰለጠነና በዘመነ ስርዓትና የክፍላተሃገር አወቃቀር መተካቱ ለዘለቄታው መፍትሔ ይሆናል ብለን እናምናለን።
በተጨማሪም በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ በሚል ስልት ለኢትዮጵያ አንድነት፣ለፍትህ፣ ለእውነተኛ ለውጥና ለዴሞክራሲ ስርዓት የሚታገሉትን ድርጅቶችና ግለሰቦች ጨምሮ ለማጥቃት የሚደረግ እንቅስቃሴ ቢኖር የምንቃወም መሆናችንን ለመግለጽ እንወዳለን።መንግሥት ከዚህም አይነቱ ድርጊት እንዲርቅ እናሳስባለን።
በአገር ውስጥና በውጭ አገር የምንኖር ኢትዮጵያዊያን፣የፖለቲካ ድርጅቶችና የሲቪክ ማህበራት ያለንን ጥቃቅን ልዩነት ወደጎን አድርገን ለአደጋ የተጋለጠችዋን አገራችንን ለመታደግ፣የአባይን ግድብ ለማስፈጸምና የኮሮናን ወረርሽን ለመዋጋት የሚያስችል የጉልበት ፣የእውቀትና የገንዘብ አስተዋጽኦ እንድናበረክት ጥሪ እናደርጋለን።
ይህንን የጋራ ፈተና ማለፍ የምንችለው በህብረት ስንቆም ነው። አገርና ሕዝብ ሳይኖር ሥልጣን አይታሰብም!!
የሙታንን ነፍስ ይማር!ለተጎዱት ቤተሰቦች፣ወዳጅ ዘመዶችና ለጠቅላላው የኢትዮጵያ ሕዝብ መጽናናትን እንመኛለን!!
ኢትዮጵያዊነት ይለምልም፤ጎሰኝነት ይክሰም!!
የኢትዮጵያ ክፍላተሃገር ህብረት