
ቦርከና
ጀማል ሰይድ
ከሰሞኑ ከተለያዩ የምስራቅ አማራ አካባቢዎች ወደ አዲስ አበባ የሚሄዱ ተጓዞች አዲስ አበባ እንዳይገቡ በኦሮሚያ ክልል ከተሞች የሚደርስባቸውን እንግልት በተመለከተ የኢትዮጵያ ሰብኣዊ መብቶች ጉባኤ ጋዜጣዊ መግለጫ አውጥቷል፡፡
ጋዜጣዊ መግለጫው እንደሚከተለው ቀርቧል፡፡
መንግስት የሰወችን በአገር ውስጥ የመዘዋወር መብት ያክብር!
መግቢያ፡
ከአማራ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች ወደ አዲስ አበባ ከተማ የሚመጡ ትራንስፖርት ተጠቃሚ የሆኑ መንገደኞች በአዲስ አበባ ዙሪያ በሚገኙ ከተሞች ውስጥ ባሉ የፍተሻ ጣቢያዎች በዋናነት በሸኖ፣ አለልቱ፣ በኪ፣ ሰንዳፋ እና ለገጣፎ አካባቢ የሚገኙ የፍተሻ ጣቢያዎች መታዎቂያቸው እየታየ ወደመጡበት እንዲመለሱ በማድረግ ከፍተኛ የሆነ እንግልት እየደረሰባቸው መሆኑን የሚያሳዩ መረጃዎች ለኢሰመጉ ደርሰውታለ፡፡ ይህ ህገ-ወጥ የሆነ ድርጊት አንድ ወር የሆነው ሲሆን በአንዳንድ የፍተሻ ኬላዎች ላይ ለማለፍ ተገቢ ያልሆነ ገንዘብ መንገደኞች እየተጠየቁ እንደሆነ፣ የአዲስ አበባ ወይም የኦሮሚያ መታወቂያ የሌለው ማለፍ እንዳልቻለ ከዚህም ጋር ተያዞ ለተለያዩ ጉዳዮች ህክምናንም ጨምሮ ወደ አዲስ አበባ የሚመጡ መንገደኞች ያለ አግባብ እየተንገላቱ መሆኑን ኢሰመጉ ካሰባሰባቸው መረጃዎች መረዳት ችሏል፡፡ይህንን አስመልክቶ ኢሰመጉ ለሰላም ሚኒስቴር እና ለትራንስፖርት ሚኒስቴር በደብዳቤ ቁጥር ERI-m41/59/22 በቀን 03/12/2014 ዓ.ም የጽሁፍ ማብራሪያ የጠየቀ ሲሆን በ04/12/2014 ዓ.ም የወልዲያ ደሴ አዲስ አበባ መስመር ከደብረ ብርሃን ወደ አዲስ አበባ የሚወስደው መንገድ መዘጋቱን እና ምንም አይነት ትራንስፖርት ማለፍ አለመቻሉን ነገር ግን መንገዱ ሙሉ ለሙሉ በ05/12/2014 ዓ.ም መከፈቱን ኢሰመጉ ካሰባሰባቸው መረጃዎች ለመረዳት ችሏል፡፡ ስለሆነም ከችግሩ አሳሳቢነት አንጻር ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶቹን ምላሽ ሳያካትት ይህንን መግለጫ መንግስት ፈጣን ማስተካከያ እንዲያረግ ለማሳሰብ አውጥቷል፡፡ ኢሰመጉ ወደፊት ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶቹን ምላሽ በማካተት በጉዳዩ ዙሪያ ሰፋ ያለ ዘገባ እንደሚያዘጋጅ በዚሁ አጋጣሚ ለመግለጽ ችለሏል፡፡
ተያያዥ የህግ ድንጋጌዎች፡
ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብቶች መግለጫ(UDHR) አንቀጽ 13 ማንም ሰው በአገሩ ክልል ውስጥ በነጻ የመዘዋወርና የመኖር መብት አለው ሲል ይደነግጋል፡፡ ሲቪል እና የፖለቲካ መብቶች አለም አቀፍ ቃል-ኪዳንም(ICPR) በአንቀጽ 12(1) በአንድ አገር ግዛት ክልል ውስጥ በህጋዊ መንገድ ያለ ማንኛውም ሰው በዚህ አገር ውስት በነጻነት የመንቀሳቃና የመኖሪያ አካባቢን በነጻነት የመምረጥ መብት አለው ሲል ይደነግጋል፡፡ አፍሪካ ሰዎችና ህዝቦች መብቶች ቻርተር አንቀጽ 12 ማንኛውም ሰው በሚኖርበት አገር ህግ በማክበር መንቀሳቀስና በፈለገው ቦታ መኖር መብት አለው ሲል ይደነግጋል፡፡ የኢፌድሪ መንግስት አንቀጽ 132(1) ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በህጋዊ መንገድ ሃገሪቱ ውስት የሚገኝ ዜጋ በመረጠው ሃገሪቱ መዘዋወር መብት አለው ሲል ይደነግጋለ፡፡
ከአለም አቀፍ፣ አህጉር አቀፍ እና ሃገር አቀፍ ሰብአዊ መብቶች ድንጋጌዎች እንደምንረዳው መንግስት ሰዎችን ሰብአዊ መብቶች ማክበር፣ ማስከበር የሟሟላት ሃላፊነት አለበት፡፡ ይህ ሳይሆን ሲቀር በመንግስት ቸልተኝነት ህጎች፤ ሰብአዊ መብቶች ሳይከበሩ ሲቀሩ ዋነኛ ተጠያቂ ሊሆን የሚገባው መንግስት ነው፡፡
የኢሰመጉ ጥሪ፡
- መንግስት ከተለያዩ የአማራ ክልል ክፍሎች ወደአዲስ አበባ በህጋዊ መንገድ ለሚንቀሳቀሱ የመንቀሳቀስ መብት እንዲያከብር እና እንዲያስከብር ፣
- ጉዳዩ የሚመለከተው የመንግስት አካል በአፋጣኝ ለዚህ ችግር ዘላቂ መፍትሄን በማበጀት ሰወች በሃገራቸው የመንቀሳቀስ መብታቸውን እንዲያከብር እንዲሁም እንዲያስከብር ፣
- በተለያዩ በአዲስ አበባ ዙሪያ በሚገኙ የፍተሸ ጣቢያዎች ላይ መንገደኖችን የሚያጉላሉ፣ አላግባብ ገንዘብ የሚቀበሉ፣ የሚደበድቡ እና የሚያስሩ ጸጥታ አካላትን ተገቢውን ምርመራ በማድረግ በህግ ተጠያቂ እንዲደርግ፡፡
__
በዚህ ድረ ገጽ ላይ መጣጥፍ ለማውጣት ከፈለጉ ጽሁፍዎትን በሚከተለው አድራሻ በኢሜይል ይላኩልን info@borkena.com
የቴሌግራም ቻናላችን ፡ t.me/borkena
ትዊተር ፡ @zborkena
ፌስቡክ ፡ Borkena