
ጀማል ሰይድ
ቦርከና
የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ሲጠናቀቅ ለምስራቅ አፍሪካ አገሮች የሃይል አቅርቦት የላቀ ድርሻ ይኖረዋል ሲሉ በኢትዮጵያ የደቡብ ሱዳን አምባሳደር ጀምስ ሞርጋን ተናገሩ።
አምባሳደር ጀምስ፤ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንዳሉት የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የልማት ትስስሩን እውን ለማድረግ እየተገነባ ያለ አህጉራዊ ፋይዳ ያለው የልማት ፕሮጀክት መሆኑን ገልጸዋል። የግድቡ መጠናቀቅ ከኢሌክትሪክ ሃይል አቅርቦትም ባለፈ ለአህጉራዊ ልማትና የጋራ ተጠቃሚነት የላቀ ትርጉም አለው ያሉት አምባሳደሩ ግድቡ ወደ መጠናቅቅ እየተቃረበ በመሆኑ ለሁላችንም ተጠቃሚነት ተስፋ እንድንሰንቅ አድርጎናል ብለዋል።
ኢትዮጵያ የግድቡን ሶስተኛ ዙር የውሃ ሙሌት እና ሁለተኛውን ተርባይን የኤሌክትሪክ ሃይል ማመንጨት እንዲችል ማድረጓ በስኬት በመጓዝ ላይ መሆኗን የሚያረጋግጥ መሆኑን ገልጸዋል።
የሃይል ማመንጫው የቀጠናውን የኢኮኖሚ ልማት ከሚያግዙ መሰረተ ልማቶች አንዱ ስለመሆኑም አምባሳደር ጀምስ ጠቅሰዋል። የግድቡ ግንባታ ከተጠናቀቀ በኋል በአካባቢው በቂ የኤሌክትክ ሃይል አቅርቦት የሚኖር በመሆኑ ችግሮች እየተቃለሉ ይሄዳሉ ብለዋል።
የኤሌክትሪክ አቅርቦቱ ከኢትዮጵያም ባለፈ ለሱዳን፣ ደቡብ ሱዳን፣ ኬንያ፣ ጅቡቲ፣ ሶማሊያ፣ ኤርትራ እና ሌሎችም አገራት የላቀ ጠቀሜታ የሚኖረው የጋራ ተጠቃሚነትን እውን የሚያደርግ ፕሮጀክት መሆኑን ገልጸዋል።”የኤሌትሪክ ኃይል ለቀጠናው የኢኮኖሚ እድገት ልማት አንዱ አካል ነው ሱዳን፤ ደቡብ ሱዳን፤ ኬንያ፤ጅቡቲ፤ ሶማሊያና ኤርትራ ቀጠናውን በሙሉ የሚረዳ ነው።”
የደቡብ ሱዳን ፕሬዝዳንት የብሔራዊ ደህንነት ጉዳዮች አማካሪ ኮንግ ቲፕቲፕ ጋትሏክ፤ሰሞኑን በህዳሴ ግድብ ባደረጉት ጉብኝት የግድቡ መገንባት በተፋሰሱ አገራት ምንም አይነት ጉዳት እንደማያደርስ መግለፃቸው ይታወሳል።
የፕሬዚዳንቱ አማካሪ ግድብ ለተፋሰሱ አገራት ጭምር የልማት ፕሮጀክት መሆኑንና የጎረቤት አገራትን በኃይል የሚያስተሳስር ፕሮጀክት መሆኑን አረጋግጠናል ማለታቸውም የሚታወስ ነው።
__
በዚህ ድረ ገጽ ላይ መጣጥፍ ለማውጣት ከፈለጉ ጽሁፍዎትን በሚከተለው አድራሻ በኢሜይል ይላኩልን info@borkena.com
የቴሌግራም ቻናላችን ፡ t.me/borkena
ትዊተር ፡ @zborkena
ፌስቡክ ፡ Borkena