
ጀማል ሰይድ
ቦርከና
የአማራ ክልል መንግስት የምዕራብ ጎጃም ዞንን ለሁለት የሚከፍለውን ውሳኔ ተግባራዊ ሊያደርግ ነው ።
በአማራ ክልል ስር የሚገኘው የምዕራብ ጎጃም ዞንን ለሁለት ለመክፈል የሚያስችሉ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች መጀመራቸው ተገለጸ። ውሳኔው ተግባራዊ ሲደረግ በምዕራብ ጎጃም ዞን ስር የሚገኙ ሰባት ወረዳዎች እና ሶስት የከተማ አስተዳደሮች ራሱን የቻለ አዲስ ዞን ይመሰርታሉ።
የምዕራብ ጎጃም ዞን በአሁኑ አወቃቀሩ 14 ወረዳዎች እና ስምንት የከተማ አስተዳደሮችን በስሩ ያቀፈ ነው። 1.2 ሚሊዮን ሄክታር የሚሸፍን የቆዳ ስፋት ባለው በዚህ ዞን ስር ከሚተዳደሩ ወረዳዎች እና የከተማ አስተዳደሮች ውስጥ የተወሰኑት፤ “የአገልግሎት እና የልማት ተደራሽነት ችግርን” በማንሳት “የዞን ይከፈልልን” ጥያቄ ለዓመታት ሲያቀርቡ ቆይተዋል።
“አስር ዓመት ገደማ ያስቆጠረ ነው” የተባለውን ይህን ጥያቄ፤ ባለፈው ሰኔ ወር መጨረሻ ባደረገው መደበኛ ስብሰባው ላይ የተመለከተው የአማራ ክልል መስተዳድር ምክር ቤት የዞን መከፈሉን ጥያቄ ተቀብሎ ውሳኔ አሳልፏል። ምክር ቤቱ ውሳኔውን ያሳለፈው፤ ጉዳዩን እንዲያጠና የተዋቀረው የቴክኒክ ኮሚቴ ያቀረበውን የውሳኔ ሃሳብ ከመረመረ በኋላ መሆኑ ተገልጿል።
የአማራ ክልል የኮሚዩኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ግዛቸው ሙሉነህ፤ የምዕራብ ጎጃም ዞን ለሁለት እንዲከፈል የተደረገው “ከስፋቱም አንጻር ትልቅ ዞን ስለሆነ እና ብዙ ህዝብ ስለሚኖርበት” እንደሆነ ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ተናግረዋል። “የዞን ይከፈልልን” ጥያቄ ሲያቀርቡ የቆዩት የምዕራብ ጎጃም ዞን ወረዳዎች እና የከተማ አስተዳደሮች፤ በባህር ዳር ከተማ አቅራቢያ የሚገኙ መሆናቸውን አቶ ግዛቸው ጠቅሰዋል።
__
በዚህ ድረ ገጽ ላይ መጣጥፍ ለማውጣት ከፈለጉ ጽሁፍዎትን በሚከተለው አድራሻ በኢሜይል ይላኩልን info@borkena.com
የቴሌግራም ቻናላችን ፡ t.me/borkena
ትዊተር ፡ @zborkena
ፌስቡክ ፡ Borkena