
ጀማል ሰይድ
ቦርከና
አሸባሪው ህዋሃት በራያ ግንባር የጀመረው ጦርነት እንዳሰበው ባይሳካለትም፤ ትንኮሳውንና ወረራውን በተለያዩ አቅጣጫች አጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ ጁንታው ከራያ ግንባር በተጨማሪ እንደከዚህ ቀደሙ በሰቆጣና ወልቃይት የተለመደ ጸብ አጣሪነቱን እየተገበረ ይገኛል፡፡
የሀገር መላከያ ሰራዊት፤ የአማራ ልዩ ሃይል ሚሊሻና ፋኖ ጥምር ጦር በሁሉም ግንባሮች የወራሪውን ጥቃት ለመመከትና ለመደምሰስም ጭምር ከፍተኛ የጀግንነት ተጋድሎ በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡
በራያ ቆቦ ግንባርም የወራሪው ሃይል ያሰለፈው ጦር ሲያልቅበት ሌላ ሀይል እየተካ ዛሬም በጎብዬ አካባቢ ውጊያው ቀጥሏል፡፡ ዛሬ ከንጋት ጀምሮ በስፍራው ከፍተኛ ውጊያ መኖሩም ተሰምቷል፡፡ ወራሪው ሃይል በወርቄ በኩል ሰብሮ ለመግባት የሚያደርገውን ሙከራ አላቆመም፡፡ የወልዲያና አካባቢው ማህበረሰብ ዛሬም ለጥምር ጦሩ የሚያደርገውን እገዛ አጠናክሮ መቀጠሉ ተሰምቷል፡፡
በሌላ በኩል ሰኞ ምሽት ወልዲያ በጁንታው ሃይሎች ተይዛለች በሚል ፕሮፖጋንዳ ምክንያት ሸሽተው ወደ ደሴ የተጓዙ የወልዲያና መርሳ አካባቢ ተፈናቃዮች ትናንት ከሰአት ጀምሮ ወደ ቀያቸው እየተመለሱም መሆናቸው ተነግሯል፡፡
በሰሜን ወሎዋ የወልዲያ ከተማም እስካሁን ድረስ የመብራት ስልክና የባጃጅ ትራንስፖርት አገልግሎት እንዳልተቋረጠና ሰላማዊ እንቅስቃሴ መኖሩን የቦርከና ዘጋቢ በከተማው ከሚገኙ ሁለት ነዋሪዎች ደውሎ አረጋግጧል፡፡
በደሴ ከተማም ትናንት ጧት ከፍተኛ ተፈናቃዮች መግባታቸውን ተከትሎ ተፈጥሮ የነበረው አለመረጋጋት ከሰአት በኋላ ጀምሮ ተስተካክሏል፡፡ በዛሬው እለትም በከተማዋ በርካታ ተፈናቃዮች ይገኛሉ፤ ምንም እንኳን ከትናንቱ ጋር ሲነጻጸር ቁጥራቸው አነስተኛ ቢሆንም፡፡ የከተማ አስተዳደሩም እስካሁን ለተፈናቃዮች መጠለያ አልሰጠም፡፡
__
በዚህ ድረ ገጽ ላይ መጣጥፍ ለማውጣት ከፈለጉ ጽሁፍዎትን በሚከተለው አድራሻ በኢሜይል ይላኩልን info@borkena.com
የቴሌግራም ቻናላችን ፡ t.me/borkena
ትዊተር ፡ @zborkena
ፌስቡክ ፡ Borkena
የቦርከና ቻናልን ስብስክራይብ ለማድረግ እዚህ ይጫኑ