
ለተከበሩ ዶ/ር ይልቃል ከፋለ
የአማራ ክልል ርእሰ መስተዳድር
ጉዳዩ:- የአማራ ህዝባዊ ኃይል (ፋኖ) መሪ አርበኛ ፋኖ ዘመነ ካሴ በአስቸኳይ እንዲፈታ የቀረበ ጥያቄ
ዓለም አቀፍ የአማራ ሕብረት እንዲሁም ስማችን ከታች የተዘረዘረው ድርጅቶች በአርበኛ ፋኖ ዘመነ ካሴ ላይ መንግሥት የወሰደው የእስር እርምጃ አሳዝኖናል፣ አጥብቀንም እንቃወማለን:: አርበኛ ፋኖ ዘመነ ካሴ የአማራው መከታና የቁርጥ ቀን ልጅ መሆኑን በተደጋጋሚ በተግባር አሳይቷል:: ወጣቱን በፋኖ በማደራጀት እንዲሁም ከፋኖ ባሻገር የአማራው ወጣት በልዩ ኃይልም ሆነ በመከላከያ ገብቶ አገሩን ከጠላት እንዲከላከል ከፍተኛ ቅሳቀሳ በማድረግ በአማራው ላይ የመጣውን ጠላት ለመፋለም ማዘጋጀቱ እና ጠላትን ማሳፈሩ የሚያሸልመው እንጅ የሚያሳስረው አልነበረም::
አገራችን ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት የተከሰተባትን እጅግ የሚዘገንን ከሃዲነት፤ ወረራ፤ የሴቶች መደፈር፤ እልቂትና የማህበረሰባዊ ኢኮኖሚ ውድመት ቀን በቀን እንከታተላለን፤ በበኩላችንንም ድርሻችንን ለመወጣት ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ እንገኛለን። በእኛ እይታ ትህነግና ግብረ አበሮቹ በአማራው ሕዝብ ላይ በተከታታይ ባለፉት ዐራት ዓመታት የፈጸሟቸውና አሁንም በመፈጸም ላይ የሚገኙትን ግፍና በደሎች ለመከላከል የአማራው ሕዝብ የአላማ አንድነት፤ የድርጅት ብቃት፤ የአመራር ብልሃት ሊኖረው ይገባል። የአማራው ሚሊሽያ፤ ልዩ ኃይልና ፋኖው ከኢትዮጵያ መከላከያ ኃይል ጋር በጥምር እጅና ጓንት ሆነው የአማራውንና የአፋሩን ብሎም የኢትዮጵያን ህልውና ለማስከበር የሚከፍሉትን መስዋእትነት እናደንቃለን፤ እናከብራለን፤ እንደግፋለን። ይህ ጥምር ኃይል የዜጎችን ያልተቆጠበ ድጋፍ ሊያገኝ የቻለው የአላማ አንድነት ስላለው መሆኑን አንጠራጠርም። የአማራውን ህብረተሰብ፤ በተለይ ወጣቱን እየሰበሰበና እያደራጀ ለአማራው ብቻ ሳይሆን ለኢትዮጵያም ህልውና ደጀን ከሆኑት የአማራ ፋኖ መሪዎች መካከል አርበኛ ዘመነ ካሴ ታሪክ የዘገበው፤ ተከታታይ ትውልድ የሚያስታውሰው እንደሆነ እናረጋግጣለን።
ክቡር ዶ/ር ይልቃል፦
በዚህ ቀውጢ ወቅት አርበኛ ዘመነ ካሴንና እሱን የመሰሉትን የአማራ ሕዝብ የፈተና ወቅት ታጋዮች ማሳደድ፤ ማዋከብና ማሰር እጅግ በጣም የሚያሳዝን፤ ተቀባይነት የሌለው፤ የአማራውን ሕዝብ የሚከፋፍልና ለባሰ አደጋ የሚያጋልጥ መሆኑን በፅኑ እናምናለን:: የአማራ ህዝብ በሁሉም አቅጣጫ በጦርነት እየተወጋ ባለበት ሰዓት ይህን የወጣቶች የቆራጥነት ምልክት የሆነ የፋኖ መሪ ለእስር መዳረግ የአማራ ክልል አመራሮችንም ሆነ የፌደራል መንግሥቱን የታሪክ ተጠያቂ ያደርጋቸዋል፡፡ በጎጥ መከፋፈል፤ በፖለቲካ ልዩነትም ሆነ በሌላ ሴራ በአማራው ተቆርቋሪዎች፤ መሪዎችና ታጋዮች ላይ በተደጋጋሚ የሚካሄደው ግፍና በደል ለአማራው ክልል መሪዎችም ጭምር አስጊ ሁኔታዎችን ያስከትላል። የዚህ ብልሹ የአመራር ሂደት ዋና ተጠቃሚ ትህነኛ እንደ ኦነግ/ሼኔ ያሉት መሰል ድርጅቶች እንደሚሆኑ ከቶ አያጠራጥርም፡፡
በዘመነ ካሴ ላይ የተወስደው አላስፈላጊና አደገኛ የእስር ውሳኔ በአገር ውስጥና ከአገር ውጭ ያለውን የአማራውን ማኅበረሰብ በአገር ቤት በተለይ ወጣቱን፤ ፋኖውን፤ ልዩ ኃይሉን፤ ምሁሩን ወዘተ እንዳስቆጣው ተረድተናል:: መሆን ያለበትም ይህ ነው ብለን እናምናለን:: ይህ ሁኔታ ከቀጠለ ለክልሉና ለፌደራሉ መንግሥት የሚሰጠው ፋይዳ የለም፤ እንዲያውም ውጭ ከሚኖረው የአማራ ማህበረሰብ ብሎም አገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን የሚያገኘው ልዩ ልዩ ድጋፍ ቀጥ ብሎ እንደሚቆም ጥርጥር የለውም::
ስለሆነም እኛ ስማችን ከዚህ በታች የተዘረዘረው ለአማራ ክልል መንግሥት የሚከተሉትን ጥያቄዎች እናቀርባለን 1. ህግ የያዘው ጉዳይ ነው ፍርድ ቤት ይወስን የሚሉት ተቀባይነት የሌላቸው ምክንያቶች በመሆናቸውን በመተው አርበኛ ዘመነ ካሴ ነገ ዛሬ ሳይባል በአስቸኳይ እንዲፈታ፤
2. በህግ ማስከበር ዘመቻ ስም የታሰሩ ፋኖዎች፤ የልዩ ኃይልና ሚሊሽያ አባላት፣ ምልስ የመከላከያ አባላት፣ ጋዜጠኞች፤ የፖለቲካ ፓርቲ መሪወችና አባላት፣ ማህበራዊ አንቂወችና ደራሲወች በአስቸኳይ እንዲፈቱና ማንገላታቱም እንዲቆም፣ 3. በወለጋ በሚኖሩ አማራዎች ላይ የሚደረገውን ማቆሚያ ያጣውን የዘር ጭፍጨፋ ለማስቆም ህዝብ ሊያየው የሚችል አስቸኳይ እንቅስቃሴ እንዲደረግ፣
4. ከትህነግ ግፍ ነፃ ያልወጡ የአማራ አካባቢዎች በፍጥነት ነፃ እንዲወጡ የተጠናከረ ዘመቻ እንዲደረግ፣ 5. በማንኛውም ከትህነግ ጋር በሚደረግ የድርድር ሂደት የጦርነቱ ገፈት ቀማሽ የሆነው የአማራ ማህበረሰብ በዋናነት እንዲሳተፍ እንዲደረግ፣
6. ትህነግ በከፈተው ጦርነት እንዲሁም ከወለጋና መተከል የዘር ጭፍጨፋ ምክንያት የተፈናቀሉ አማራወች ተገቢ መንግሥታዊ ድጋፍ እንዲያገኙ፣
7. የአማራ ክልል አመራር የክልሉ ህዝብ የተጋረጠበትን የህልውና አደጋ ለመከላከል የሚያስችል የአላማ አንድነት፣ ጠንካራ ህዝባዊ አደረጃጀትና ድርጅታዊ ብቃት ላይ ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ እንዲሰራ ጥሪ እናቀርባለን::
አማራ የጀመረውን የህልውና ትግል በአሸናፊነት ይወጣል!
ኢትዮጵያ በልጆቿ ትግልና መስዋዕትነት ታፍራና ተከብራ ትኖራለች!
1. Global Amhara Coalition
2. Adwa Great African Victory Association (AGAVA)
3. All Shewa Ethiopian People Multipurpose International Association 4. The Amhara Association in Queensland, Australia
5. Amhara Dimtse Serechit
6. Amhara Well-being and Development Association
7. Communities of Ethiopians in Finland
8. Concerned Amharas in the Diaspora
9. Ethio-Canadian Human Rights Association
10. The Ethiopian Broadcast Group
11. Ethiopian Civic Development Council (ECDC)
12. Freedom and Justice for Telemt Amhara
13. Global Alliance for Justice – The Ethiopian Cause
14.Gonder Hibret for Ethiopian Unity
15.Major Lemma Woldetsadik Memorial Foundation
16.Network of Ethiopian Scholars (NES)
17.Radio Yenesew Ethiopia
18.Selassie Stand Up, Inc.
19. Vision Ethiopia
20. Worldwide Ethiopian Civic Associations Network (WE-CAN)
__
በዚህ ድረ ገጽ ላይ መጣጥፍ ለማውጣት ከፈለጉ ጽሁፍዎትን በሚከተለው አድራሻ በኢሜይል ይላኩልን info@borkena.com
የቴሌግራም ቻናላችን ፡ t.me/borkena
ትዊተር ፡ @zborkena
ፌስቡክ ፡ Borkena
የቦርከና ቻናልን ስብስክራይብ ለማድረግ እዚህ ይጫኑ