
ከሃያ ኢትዮጵያውያን ድርጂቶች የተሰጠ መግለጫ
ጥቅምት 28 ቀን 2015 ዓ.ም
የኢትዮጵያ ሕገ-መንግሥታዊና ሥርዓታዊ የሆነው የዘውግ ፖለቲካ የግፍና የእልቂት አዝመራን አፍርቷል። ኢትዮጵያውያን የጅምላ ዝርፊያ፣ የፖለቲካ ጥቃት፣ የጥላቻ እና የጭካኔ ወንጀሎች (የዘር ማጥፋት፣ የዘር ማጽዳት፣ ሰብዓዊነትና የጦርነት ወንጀሎች) ሲፈጸምባቸው ቆይቷል። በኦሮሚያ ክልል በሠላማዊ ዜጎች (በተለይም በዐማራ ተወላጆች) ላይ ዘግናኝ ጥቃት በየጊዜው እየተፈጸመ ነው። መንግሥትም ተገቢዉን እርምጃ አይወስድም።
ሕዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ሕወሓት) የጀመረውና ሁለት ዓመታትን ያስቆጠረው ማዕበላዊ የዕልቂት ጦርነት ዐማራና አፋር ድረስ ዘልቆ የሽዎችን ህይወት ቀጥፏል፣ በብዙ ሚሊዮኖች የሚቆጠር ሕዝብ ከቀየው ተፈናቅሏል፣ ሃብቱም ተዘርፏል ወይንም ወድሟል። ብዙ እናቶችና እህቶች ተደፍረዋል። ሕወሓት በቀሰቀሰው ጦርነት የዐማራና የአፋር ህዝብ ለዓመታት የማያገግም የኢኮኖሚ ውድመት ደርሶበታል።
በጥቅምት 24፣ 2015 ዓ.ም በኢትዮጵያ ፌዴራላዊ መንግሥትና በሕወሓት መካከል ፕሪቶሪያ የተፈረመው የሠላም ስምምነት በተግባር ከዋለ ለጊዜውም ቢሆን ሲካሄድ የነበረውን ጦርነት እና እልቂት ሊያስቆም ይችላል። ነገር ግን ስምምነቱ ችግሩን ከሥር መሠረቱ ሊፈታ ቀርቶ እንዳውም የችግሩ ምንጭ የሆነዉን የጎሳ አፓርታይድ ሕገ-መንግሥት መፍትሄ አድርጎ የሚያቀርብ ነው። ስለሆነም ስምምነቱን አስመልክቶ ብዙ ስጋቶች አሉን።
ስምምነቱ ሠላም ለማስፈን መሰናክል የሚሆኑ ስፍር ቁጥር የሌላቸው የአገሪቱን መዋቅራዊ ችግሮች ለመፍታት የሚያስችል ግልጽ ፍኖተ ካርታ የለውም፤ ሕወሓት በሠራቸው አሰቃቂና አረመኒያዊ ወንጀሎች በሽግግር ፍትህና የመቀጣጫ ፍርድ ሳያገኝ፣ ከአሸባሪነቱና ከወንጀሉ ነጻ የሚያደርግና ተመልሶ ወደ ፖለቲካ ሥልጣን የማምጣት አዝማሚያ ያለው ስምምነት ነው። እንዲሁም ሕወሓት ሥልጣን ከመያዙ በፊት ዐማራውን በማፈናቀልና በማጥፋት ቀጥሎም ትግሬዎችን ጦር መሳሪያ አስታጥቆ በማስፈር፣ በጉልበት ከጎንደርና ወሎ የነጠቃቸውን ወልቃይትና ራያ የመሳሰሉ ለም ቦታዎችን፣ ዐማራውን ሳያሳትፉ ራሳቸው ሕወሓትና ኦነግ በጻፉት ሕገ-መንግሥት ይፈታል ብሎ አልፎታል። በዚህም ለኢትዮጵያ ተጨማሪ ስጋት ደቅኗል። እንዳውም የተፈረመው የሠላም ስምምነት ገና ቀለሙ ሳይደርቅ ስምምነቱን የፈረሙት የፈደራል መንግሥቱ ወኪል የትግራይ የጎሳ ልዩ ኃይል በድጋሚ እንደሚቋቋም እየተናገሩ ነው። ጦር ይፈታል የተባለው እና ብዙ የጦር ወንጀል የፈጸመው የሕወሓት ወታደርም ወደዚህ አድስ ወደሚቋቋመው ልዩ ኃይል ሊደለደል ይችል ይሆናል የሚል ፍራቻን ያስከትላል።
በእኛ እምነት፣ ለዘላቂ ሠላምና እድገት ኢትዮጵያን ከዘውግ ፖለቲካ አዙሪት የሚያወጣ የሽግግር ሂደትያስፈልጋል። የአፓርታይዱ ሕገ-መንግሥት ዋናው የሃገሪቱ ችግር ፈጣሪ እንጂ መፍትሄ ሊሆን ፈጽሞ አይችልም። እልባቱም ሁሉንም ኢትዮጵያዊ እኩል ተጠቃሚ የሚያደርግ ዴሞክራሲያዊ ሕገ-መንግሥት ነው። የተገለለውን የዐማራና በጎሳ ፖለቲካ የሚሰቃየውን ኢትዮጵያዊ ሁሉ ጥቅም ለማስክበር ብቸኛው አማራጭ በፍትህ፣ በእኩልነትና በነጻ ዜግነት ላይ የተመሠረተ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓትን መገንባት ነው። መንግሥት ከፖለቲካ ቁማርና ከተመርጫለሁ ግብዛዊነት አባዜ ተላቆ የሕዝብ ቅቡልነትንና ተሳታፊነትን ያቀፈ የድህረ-ግጭት ፍኖተ-ካርታ በአስቸኳይ እንዲዘጋጅ መተባበር ይገባዋል፣ ይጠቅመዋልም።
ማንኛውም ዜጋ በትብብር ለመብቱ ዘብ በመቆም ግፊት ካላደረገ አምባገነኖች እንደሚፈራርቁበት መሆኑን ተገንዝቦ ሉዓላዊነቱን ማስከበር ወቅታዊ ግዳጁ ነው፣ የሠላምና የአንድነት መቋጫው የፍትህ መስፈን ነውና። ነጻነት በመራር ትግል እንጂ በስጦታ አትገኝምና!
ፈራሚ ድርጂቶች:
1. Adwa Great African Victory Association (AGAVA)
2. All Shewa Ethiopian People Multipurpose International Association
3. The Amhara Association in Queensland, Australia
4. Amhara Dimtse Serechit
5. Amhara Well-being and Development Association 6. Communities of Ethiopians in Finland
7. Concerned Amharas in the Diaspora
8. Ethio-Canadian Human Rights Association
9. The Ethiopian Broadcast Group
10. Ethiopian Civic Development Council (ECDC)
11. Freedom and Justice for Telemt Amhara
12. Global Alliance for Justice – The Ethiopian Cause 13. Global Amhara Coalition
14. Gonder Hibret for Ethiopian Unity
15. Major Lemma Woldetsadik Memorial Foundation 16. Network of Ethiopian Scholars (NES)
17. Radio Yenesew Ethiopia
18. Selassie Stand Up, Inc.
19. Vision Ethiopia
20. Worldwide Ethiopian Civic Associations Network (WE-CAN)
__
በነጻ አስተያየት መድረክ የሚቀርቡ ሃሳቦች የጸሃፊውን እንጂ የግድ የቦርከናን ድረገጽ ሃሳብ ላያንጸባርቁ ይችላሉ፡፡ በዚህ ድረ ገጽ ላይ መጣጥፍ ለማውጣት ከፈለጉ ጽሁፍዎትን በሚከተለው አድራሻ በኢሜይል ይላኩልን info@borkena.com
የቴሌግራም ቻናላችን ፡ t.me/borkena
ትዊተር ፡ @zborkena
ፌስቡክ ፡ Borkena
የቦርከና ቻናልን ስብስክራይብ ለማድረግ እዚህ ይጫኑ