ኤልያስ አበበ
እንደሚታወቀው እርሶ ወደ ስልጣን ከመጡበት ጊዜ አንስቶ በርካታ መልካም ተግባራት የተከናወኑ ቢሆንም፤ በኢትዮጵያ ታሪክ የዜጎች ሞት፤ መፈናቀል እና እንግልት በተለይም በአማራ ሕዝብ ላይ የተነጣጠረ የዘር/ብሔር ተኮር ጥቃት የዘር ማጥፋት ወንጀል እርሶ በሚመሩት መንግስት እየተፈፀመ ይገኛል፡፡ የዜጎች ደም ያለማቋረጥ በምድራችን ላይ እየፈሰሰ በመሆኑ፤ በዚህ ጉዳይ እግዚአብሔር የሚበቀል መሆኑ መዘንጋት የለበትም፡፡
እርሶ ወደ ስልጣን በመጡበት ወቅት ቃል ገብተው ከነበሩት ጉዳች ውስጥ የዜጎች በአገራቸው ሰርተው የመኖር፤ ሐሳባቸውን በነፃነት የመግለፅ እና የመደራጀት/የመሰብሰብ መብቶች ወዘተ. የሚገኙበት ቢሆኑም፤ አሁን ግን የጋዜጠኞች አፈና እና ድብደባ (በተለይም የሴት ጋዜጠኞች እና ሰብኣዊ መብት ተሟጋቾች ተደጋጋሚ ሰብኣዊ መብት ጥሰት) አስከፊ ደረጃ ላይ ለመድረሱ የጋዜጠኛ መስከረም አበራ በአንድ ዓመት ለ3ኛ ጊዜ መታሰር በቂ ማስረጃ ነው፡፡
በተጨማሪም የጀነራል ተፈራ ማሞ የውጭ አገር ህክምና መከልከል በእንድ ፈጣሪ ኢትጵያን ይባርክ የሚል ቡራኬ በተደጋጋሚ ከሚሰጥ መሪ የሚጠበቅ አይደለም፡፡ ጀነራሉ በቅርቡ እርሶ ባቀረቡላቸው ጥሪ መሰረት የአገር ሕልውና ዘመቻውን ተቀላቅለው ሰራዊት በመምራ አኩሪ ተጋድሎ እና ውጤት ማስመዝገባቸው ከእርሶ የተሰወረ እይደለም፡፡ ጀነራሉ በውል በማያውቁት ምክንያት የውጭ አገር ሕክምና ተከልክለው በመሰቃየት ላይ መሆናቸው የአደባባይ ሚስጥር ነው፡፡
በመሆኑም፡ –
- የአማራ ልዩ ኃይልን ትጥቅ ለማስፈታት እየተወሰደ ያለው የኃይል እርምጃ በቶሎ እንዲቆም፤
- የታሰሩ ጋዜጠኞች እና የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች በሙሉ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲፈቱ፤
- ጀነራል ተፈራ ማሞ የውጭ አገር ሕክምና ክልከላ ተነስቶላቸው ቶሎ ሕክምና እንዲያገኙ እንዲደረግ፤
በአጠቃላይ እርሶ ያቋቋሙት የብልፅግና ፓርቲ ከሕዝብ ፍላጎት ውጪ የሚያደርጋቸውን ኢትዮጵያን የሚያፈርሱ ተግባራት በአስቸኳይ በማቆም ከሁሉ አስቀድሞ አገራዊ ምክክሩ እንዲቀድም፤ ቤተ-ክርስቲያንም አገራዊ የንሰሐ ጾም ፀሎት በማወጅ ለምድራችን የእግዚአብሔር ጉብኝት እዲመጣ በታላቅ አክብሮት አሳስባለሁ፡፡
መንፈስ ለኢትዮጵያ የሚለውን ጆሮ ያለው ይስማ!
ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች!
__
በነጻ አስተያየት መድረክ የሚቀርቡ ሃሳቦች የጸሃፊውን እንጂ የግድ የቦርከናን ድረገጽ ሃሳብ ላያንጸባርቁ ይችላሉ፡፡ በዚህ ድረ ገጽ ላይ መጣጥፍ ለማውጣት ከፈለጉ ጽሁፍዎትን በሚከተለው አድራሻ በኢሜይል ይላኩልን info@borkena.com
የቴሌግራም ቻናላችን ፡ t.me/borkena
ትዊተር ፡ @zborkena
ፌስቡክ ፡ Borkena
የቦርከና ቻናልን ስብስክራይብ ለማድረግ እዚህ ይጫኑ