
በላይነህ አባተ
አውቀንም ሆን ሳናውቀው የሰራነውን ስህተት ሊያጠራ፣
ፀጸፅት ንስሀን ዘርግቷል እግዚአብሔር ወይም ህሊና፡፡
“ሙሴና ኢያሱ” መጡ እያልን ካድሬ ጥሩንባ የነፋን የአዘናጋንም አማራ፣
ምሁር መምህር መካሪ ለምመሰል ከመጣር በፊት ዛሬም እንደ ታች አምና፣
ሕዝብ በማሳሳታችን ከልብ ይቅርታ እንጠይቅ በቅድሚያ ንስሀ እንግባ!
የቆሸሸ እጁን ሳያጥብ ተነጀርሙ አብሮ የሚቀርብ ገበታ፣
ማድ የቀረበውን ጤነኛ ሁሉ ስለሚበክል ሊገል በሚችል በሽታ፣
ቅድሚያ እድፋችንን እናራግፍ እውነት ተራስ ቅል ታለን ህሊና፡፡
በሰማእታት መቃብር አረም በትንነን እርግፍ አርገን እረስተን በአንድ አፍታ!
በገዳዮቻቸው ስብከት ተሟዘን ሕዝብ አሳስተን ሚሊዮኖችን ያስፈጀን በተርታ፣
እውነት ተስህተታችን ከተማርን ሳንውል ሳናድር ዛሬውን ንስሀ እንግባ!
በበደኖዎች ሰማእታት መቃበር በአርባ ጉጉዎች ከፈንና ግነዛ፣
በጋምቤላዎች ጭፍጨፋ በሶማሌዎች አስከሬን መሬት ጉተታ፣
በወልቃይት ራያ ሰቆቃ እንደ ዘፅዓት በፈለሱቱ ወለጋ በጉራ ፈርዳ፣
ከአርባ አምስት ዓመታት በላይ በአማራ በተፈጠመው ወደር የሌለው መከራ፣
ቀዝቃዛ ውሀ ቸልዘን የሰበክን ሕዝብ እንዲከተል ወንጀለኞችን ታች አምና፣
እውነት ሰው ተሆን አርባ ቀን ጦመን አልቅሰን አንብተን ንስሀ እንግባ!
በወህኒ ኮረንቲ በጠበሷቸው ዘቅዝቀው በሰቀሏቸው በሚዘገንን ሰቆቃ፣
ብልታቸውን ተሰልበው ዓለም በቅቷቸው መንነው ገዳም በገቡት መከራ፣
አመድ ጥላሸት ነስንሰን ሕዝብን ያሳሳትን ሙሴ መጣ እያልን ጧት ማታ፣
እንደ ጲላጦስ እጅ አጥበን ከደም ንጡህ ነኝ ለማለት ተምንሽከረከር ዳርዳርታ!
የተበከለ ህይወት ታሪካችንን እናድስ ቀኑ ሳይጨልም በቀን ንስሀ እንግባ!
ሰማእታትን ዘንግተን የሰዋቸውን ወንጀለኞችን ያልደገፍን ለመምሰል ስንዳዳ፣
የምንሰጠው ሰበብም ሆነ የምንወሸክተው የማያቋርጥ ከንቱ እሰጥ አገባ፣
ተእግዚአብሔር ደጃፍ ከቶ አይደርስ እውነትን ተሚሻ ሕዝብ ማጌትም አይገባ!
ትውልድ ሲወቅሰን እንዳይኖር ብዕር ሲወጋን ጧት ማታ!
ታሪክ ጠርዞ ሳያስቀምጠን ሕዝብን በማሳታችን እንዲከተሉ ይሁዳ፣
የፍጣሜው ቀን ሳይመጣ ከእነ ጉዳችን ወደ እማይቀረው መቃብር ሳንገባ፣
እንደ ባህል ሃማኖታችን ከአንጀትና ልብ አልቅሰን ንስሀ እንግባ!
የሰማይ ዳኛ ይቅር እንዲለን በምድርም ለመትረፈ ክታሪክ ብዕር ዝንቆላ፣
ህሊናችንን እንጠብ ፍንትው አድርገን በሱባኤ እንዶድ ሳሙና፣
ልፍስፍስ ሰበብ ተመደርደሩ ታቅበን በመጀመርያ ንስሀ እንግባ!
በላይነህ አባተ (abatebelai@yahoo.com)
ህዳር ሁለት ሺ አስራ ስድስት ዓ.ም.
__
የቴሌግራም ቻናላችን ይቀላቀሉ ፡ t.me/borkena
በነጻ አስተያየት መድረክ የሚቀርቡ ሃሳቦች የጸሃፊውን እንጂ የግድ የቦርከናን ድረገጽ ሃሳብ ላያንጸባርቁ ይችላሉ፡፡ በዚህ ድረ ገጽ ላይ መጣጥፍ ለማውጣት ከፈለጉ ጽሁፍዎትን በሚከተለው አድራሻ በኢሜይል ይላኩልን info@borkena.com
የንግድ ድርጂትዎትን እና አገልግሎትዎትን በቦርከና የቢዝነስ ዳይሬክተሪ ላይ ያስመዝግቡ ፤ እግረ መንገድዎን የቦርከናን ስራ ይደግፉ ያበረታቱ፡፡ እዚህ ጋር፡፡
ትዊተር ፡ @zborkena
የፌስቡክ ገጻችንን ላይክ ያድርጉ፡ Borkena
የቦርከና ቻናልን ስብስክራይብ ለማድረግ እዚህ ይጫኑ