ቦርካና
የካቲት 9 2010 ዓ ም
የመንግስት ዜና አውታር የሆነው የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት እንደገለጸው በማህበራዊ ድረ ገጹ ከጥቂት ደቂቃዎች በፊት እንዳስታወቀው የሚኒስትሮች ምክር ቤት ባካሄደው አስቸኳይ ስብሰባ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጂ አውጇል።
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ዛሬ እንደሚጀመር ከማሳወቁ በስተቀር የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መቸ እንደሚያበቃ የተጠቆመ ነገር አልነበረም። ሆኖም ቆየት ብሎ በተሰጠ ማብራሪያ መጀመሪያ ለስድስት ወር ያህል ይቆይና የጸጥታው ሁኔታ የማይሻሻል ከሆነ ለተጨማሪ አራት ወር ሊራዘም እንደሚችል ተገልጾአል።
“በህገ መንግስቱ ላይ የተጋረጠውን አደጋ በመደበኛው የህግ ማስከበር ስርዓት መቆጣጠር የማይቻልበት ደረጃ ላይ ስለተደረሰ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጂ ማወጂ አስፈላጊ ሆኗል።” ብሏል መንግስት ያወጣው መግለጫ።
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መንግስት በይፋ ካሳወቀበት ቀን ጀምሮ በስራ ላይ ይውላል ቢልም ፤ በሁለት ሳምንታት ጊዜ ውስጥ በፓርላማ ቀርቦ እንደሚጸድቅም ታውቋል።
ለሳምንታት ያህል የአስቸኳይ ጊዜ አዋጂ እንደሚታወጂ ውስጥ አዋቂ ምንጮች በማህበራዊ ሚዲያ መረጃ ሲያጋሩ እንደሰነበቱ አይዘነጋም። ባለፉት ሁለት አመታት ኢትዮጵያ ለአንድ ዓመት በሚጠጋ ጊዜ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጂ ስር መቆየቷ ይታወሳል።