
ሰገነት ብዙአየሁ
ሀምሌ 2 ቀን 2017 ዓ.ም
ባለፈው አርብ ከምሽቱ 10፡30 ሰዓት አካባቢ ሲኒማ ፊት ለፊት በሚገኘው ዘላለም ጃምቦ ሐውስ ውስጥ አስደንጋጭ ግድያ በመፈፀሙ ከተማዋ አሁን ላይ ከፍተኛ በሀዘንና ቁጣ ውስጥ ትገኛለች።
አራት ጓደኛማቾች ምንም በማያውቁት ሁኔታ ለመዝናናት ተሰብስበው ምግብ ለመብላት በጃምቦ ቤቱ ተቀምጠው በነበረበት ሰአት ከጎናቸውም ሶስት ክላሽ የታጠቁ ሚሊሻዎች ድራፍት እየጠጡ ተቀምጠው እንደነበር የአይን እማኞች ተናግረዋል ።
ወጣቶቹ ባህላቸውን ጠብቀው እንብላ ብለው ሲጋብዟቸው ሚሊሻዎቹ ግን የወጣቶቹን ንግግር እንደ ንቀትና መደፈር ቆጥረውባቸዋል።
ከሚሊሻዎቹ መካከል ዓባይነህ እናውጋው የተባለው ግለሰብ ሕዝብ አገር አማን ብሎ በሚዝናናበት ስፍራ ምንም ዓይነት ጥፋት ባልፈጸሙ ወጣቶች ላይ የጥይት ናዳ እንዳወረዱባቸው ነው የአይን እማኞች የተናገሩት ።
በተፈጠረው የተኩስ እሩምታ አማኑኤል እና ብሥራት የተባሉት ወጣቶች ወዲያውኑ ህይወታቸው አልፏል።
ሁለቱ ሌሎች ጓደኞቻቸው ደግሞ ቆስለዋል። አንደኛው ጉዳቱ ቀላል ስለነበር ወደ ቤቱ የተመለሰ ሲሆን፣ ሌላኛው ግን ከባድ ጉዳት ደርሶበት አሁንም በደብረ ማርቆስ ሪፈራል ሆስፒታል ውስጥ ህክምና እየተከታተለ ይገኛል ነው የተባለው።
ገዳዩ ሚሊሻ እጁን ከሰጠ በኋላ ወጣቶቹ መሳሪያየን ሊነጥቁኝ ሲሉ ነው የመታኋቸው የሚል ቃል መስጠቱ ተገልጿል ።
ይህ አሰቃቂ ግድያ የተፈጸመው በደብረ ማርቆስ ከንቲባ ተሾመ ዋለ የሠላም እና ደህንነት ኃላፊው ይኽነው አበባው፣ እና የከተማው ፖሊስ ኃላፊ ቢምረው አሰፋ ባሰለጠኑት እና ባሰማሩት ኃይል መሆኑ ተጠቁሟል።
የከተማ አስተዳድሩ እስካሁን ድረስ ስለተፈጸመው የጭካኔ ግድያ ምንም ዓይነት ይፋዊ መግለጫ አልሰጠም።
ገዳዩ ሚሊሻም ለህግ አለመቅረቡ ሲታወቅ ከእርሱ ጋር የነበሩት ሁለት ሚሊሻዎችም በህግ አልተጠየቁም።በግፍ ለተገደሉት ወጣቶች አማኑኤል እና ብሥራት ህብረተሰብ ፍትህ እንዲሰጣቸው እየጠየቀ ይገኛል።
__
ድጋፍ ያድርጉ :- ቦርከና ከ13 ዓመታት በላይ ነጻ መድረክ በመሆን አገልግሏል ፤ ወደ ፊትም በተሻለ ሁኔታ ለማገልገል ጥረት እያደረገ ይገኛል፡፡ ከፍተኛ የሆነ የሰው ኃይል እጥረት ስላለበት እና አስቸጋሪ በሆነ ሁኔታ ውስጥ እየሰራ ስለሆነ ችግሩን ለመቅረፍ በዓመት $5 ወይንም $10 የገንዘብ ድጋፍ የማድረግ አቅም ካለዎት እዚህ ገጽ ላይ በመሄድ ድጋፍ ያድርጉ፡፡ https://borkena.com/subscribe-borkena/
የቴሌግራም ቻናላችን ይቀላቀሉ ፡ t.me/borkena
ፌስቡክ ገጻችንን ላይክ ያድርጉ ፡ Borkena
Ethiopian News – Borkena English
ኤክስ ፡ @zborkena
የቦርከና ቻናልን ስብስክራይብ ለማድረግ እዚህ ይጫኑ






