
ቦርከና ዜና
ለከፍተኛ የጤና ችግርና ለኢኮኖሚያዊ ቀውስ እየተዳረግን ነው ብለዋል።
በጅቡቲ የሚገኙ የነዳጅ ጫኝ ቦቴ አሽከርካሪዎች ” ነዳጅ ለመጫን ለወራት ተሰልፈን ብንቆይም ነዳጅ መጫን አልቻልንም ፤ በዚህም ምክንያት ለከፋ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ተዳርገናል ” ሲሉ ቅሬታቸውን አቅርበዋል።
የቦቴ ባለቤቶች ” ትጭናላችሁ ” ብለው ወደ ጅቡቲ እንደሚልኳቸው የሚናገሩት አሽከርካሪዎቹ ፤ ጅቡቲ ከደረሱ በኋላ ግን በሁለትና ሦስት የተለያዩ ቦታዎች ተከማችተው እንደሚገኙ ተናግረዋል።
አሽከርካሪዎቹ እንደሚሉት ለቀናት ተጉዘው ወደ ጅቡቲ ቢደርሱም እስካሁን በግልፅ በማያውቁት ምክንያት ነዳጅ መጫን እንዳልቻሉ አብራርተዋል።
የተለያዩ አሽከርካሪዎች በሰጡት መረጃ ድሬዳዋ መገንጠያን ጨምሮ በሶስት የተለያዩ ቦታዎች ተከማችተው እንደሚገኙና በአንድ ቦታ ብቻ በሺዎች የሚቆጠሩ ቦቴዎች እንደቆሙ ገልፀዋል።
ይህ ቃለመጠየቅ በተደረገላቸው ወቅት በበረሃማው የጅቡቲ አከባቢ ውስጥ ከአንድ እስከ ሦስት ወራት ለሚጠጉ ጊዜያት ሌትና ቀን ቆመው መቆየታቸውንም አስረድተዋል።
ነዳጅ ላለመጫናቸው ዋነኛው ምክንያት ጦርነቱ ግጭቱ ሳይጀምር በፊት ተሰልፈው የነበሩ ስለመኖራቸው ገልፀዋል።
እየደረሰብን ያሉ ኢኮኖሚያዊ ቀውስና የጤና ጉዳት በመግለፅ በቦታው ላሉ አስተባባሪዎችና የነዳጅና ኢነርጂ ባለሥልጣን ባለሙዎችን ብንጠይቅም ‘በቴሌብር ምክንያት ነው’ የሚል ምላሽ ነው የሚሰጡን ” ያሉት አሽከርካሪዎቹ፤ ” ቴሌብር ምን ሆነ ? ” የሚለውን ጥያቄ የሚያብራራም ሆነ ምላሽ የሚሰጥ አካል ማጣታቸውን ገልጸዋል።
አንዳንድ አሽከርካሪዎችም በሀገር አቀፍ ደረጃ በርካታ ማደያዎች ያሏቸው ቶታል፣ ኖክ፣ ኦይል ሊቢያና ታፍን ጨምሮ ቀደምት እና ስመ ጥር የነዳጅ ድርጅች ቦቴዎች ጭነት እያገኙ እንዳልሆነ ጠቁመዋል።
በርካታ አሽከርካሪዎች በቆይታቸው ምክንያት ለተለያዩ የጤና እክሎች እየተጋለጡ ስለመሆኑ ያነሱ ሲሆን ስኳርና ደም ግፊትን የመሳሰሉ በሽታ ያለባቸው አሽከርካሪዎች እንዳሉና ቦቴዎቹን ጥሎ መውጣትም ሆነ እዚያው መቆየት ባለመቻላቸው በከፍተኛ የጤና ችግር ውስጥ ስለመሆናቸው ተናግረዋል።
በተጨማሪም በጅቡቲ በረሃ የውሃ እጥረት ስላለ ሁለት ሊትር ውሃ እስከ 300 ብር ገዝተው ለመጠቀም መገደዳቸውንና ለከፍተኛ ኢኮኖሚያዊ ቀውስ መዳረጋቸውን አስረድተዋል።
ከሚመለከተው የመንግስት አካል ችግሩን ተመልክቶ በአስቸኳይ መፍትሄ እንዲሰጣቸው አሽከርካሪዎቹ ጠይቀዋል።
አንዳንድ አሽከርካሪዎች የቴሌብር ፕሮሰስ ተስተካክሎላቸው ቢወጡም በርካቶች እዛው እንደሆኑና ሌሎችም እየተጨመሩ እንዳሉ ጠቁመዋል።
የነዳጅና ኢነርጂ ባለሥልጣን፣ በጉዳዩ ላይ የሰጡት ማብራሪያ የለም።
__
የቦርከና ቻናልን ስብስክራይብ ለማድረግ እዚህ ይጫኑ
የቴሌግራም ቻናላችን ይቀላቀሉ ፡ t.me/borkena
ፌስቡክ ገጻችንን ላይክ ያድርጉ ፡ Borkena
Ethiopian News–Borkena English
ኤክስ ፡ @zborkena






